ETHIO12.COM

ኢትዮጵያዊው ድሮን ሰርቶ የተሳካ ሙከራ አደረገ

የሜካኒካል ምኅንድስና ምሩቅ የሆነው የደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ መምህሩ አማኑኤል ባልቻ ድሮን በመሥራት የተሳካ የሙከራ በረራ ማድረጉ ተገለጸ፡፡ የደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ለታ ተስፋዬ ÷ መምህሩ የሠራው ድሮን 250 ሜትር በተሳካ ሁኔታ በበረራ መሸፈን እንደቻለ ተናግረዋል፡፡ መምህር አማኑኤል ባልቻ፥ ሁለት ድሮን እና አንድ አውሮፕላን እየሠራ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ መምህሩ ከአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ በሜካኒካል ምኅንድስና ተመርቆ በደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ እያገለገለ ይገኛል።

ዩኒቨርሲቲው “የፈጠራ ቀን” በዓሉን በፓናል ውይይትና የተማሪዎቹን የተለያዩ የፈጠራ ሥራዎች በአውደ-ርዕይ በማሳየት እንዳከበረ ተገልጿል፡፡

በመርሃ-ግብሩም የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች እየሠሯቸው ላሉ የተለያዩ የፈጠራ ሥራዎች ድጋፍ እየተደረገ እንዳለ እና በፈጠራ ሥራዎቻቸው አርዓያ የሆኑ ተማሪዎች ሽልማትና እውቅና እንደተበረከተላቸው ተጠቁሟል።

ዩኒቨርሲቲው እንደ ድሮን፣ የቡና መፈልፈያ ማሽን፣ የእንጨት መላጊያ፣ የጨርቃ ጨርቅ መሥሪያ ማሽኖች፣ የተለያዩ መሣሪያዎች መለዋወጫ፣ የዶሮ ማስፈልፈያ ማሽን(ኢንኩቤተር)፣ የተለያዩ አይነት ተሽከርካሪዎች፣ የውሃ መሳቢያ ሞተር፣ የሕጻናት ንፅህና መጠበቂያ ዳይፐር እና የመሳሰሉት ላይ በመርሃ-ግብሩ አካቶ እየሠራ እና እያበለጸገ ይገኛልም መባሉን ከደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ያገኘነው መረጃ ጠቅሶ ፋና አመልክቷል፡፡

Exit mobile version