Site icon ETHIO12.COM

ይድረስ ለኦሮሞ – ኦሮሞ ኦሮሞን እያጠቃ ነው፤ መዘዙ ያስፈራል

ኦሮሞ፣ አሊቢራ እንዳለው ” ሁሉም ኦሮም ኦሮሞ ነው” የጉጂ ኦሮሞ ኦሮሞ ነው። የሰላሌ ኦሮሞ ኦሮሞ ነው። የወለጋ ኦሮሞ ኦሮሞ ነው። አምቦ፣ ሀረርጌ፣ ጅባት፣ ባሌ፣ አርሲ፣ ጪሮ፣ሰላሌ፣ ኤሉአባቡር፣ ጅማ፣ ባሌ … ወረዳዎች፣ ቀበሌዎች … ሁሉም እኩል ናቸው። ማንም ሆነ ማን፣ ከየትኛውም ቀበሌና ወረዳ ይምጣ ኦሮሞ ነው። እኔም ኦሮሞ ነኝ።

“በኦሮሚያ በታጣቂዎች መስፋፋት እየተፈተነ ያለው የጉጂ ዞን” 25.02.2022 የጀርመን ድምጽ የነካካው ዜናና አምስት ወርዳዎች በከፊልና ሙሉ በሙሉ በሸኔ ቁጥጥር ስር መውደቃቸውን ዘገባው የዳሰሳቸውን ጉዳዮች ካነበብኩ በሁዋላ “ይድረስ ለኦሮሞ” በሚል መሰረታዊ ጥያቄዎችን በማንሳት ከልባችን ጋር እንድንመክር ወሰንኩ። ይህ በሚዲያ ስጽፍ የመጀመሪያዬ ሲሆን በዚህ ሚዲያ የላኩት በአቅራቢያዬ ስለሚገኝ ነው።

እስኪ ይህን እናንብብ ” ሰው በየትኛውም አቅጣጫ ሲወጣ እያገቱ ብር ይለቅማሉ፡፡ ሰው ያለውን ሁሉ ይዘረፋል፡፡ ከገጠር ቀበሌዎችም እየተነሱ ይሄው ወደ ከተማዋ እየተሰደዱ ነው፡፡ የመንግስት የፀጥታ ኃይሎች ሲወጡ በቦታው አያገኙዋቸውም፡፡ ከመንግስት አቅም በላይ ሆኗል ለማለትም ሆነ መንግስት አከባቢውን እያስተዳደረ ነው ለማለት ተቸግረናል። ” ይህ የጀርመን ድምጽ የጠቀሳቸው ሰለባ ያሉት ነው።

በሶማሌ አዋሳኝ የጉጂ ዞን ተብላ ከተጠቀሰችው አካባቢ ነኝ። አካባቢው ድርቅ አለ። ሕዝቡ በድርቅ ከብቶቹን እያጣ ነው። ድርቅ ያደከመውን ሕዝብ ደግሞ ከላይ የጀርመን ድምጽ ባለው መልኩ እየተዘረፈ ነው። ይህ ሕዝብ ከስማይ በዝናብ እጥረት፣ በምድር በወገኖቹ በደል እስከመቼ ነው የሚሰቃየው? ለምስ ነው የሚሰቃየው? ምንስ ስላጠፋ ነው ይህ ሁሉ የሚሆንበት? ይህ ለመላው አርቆ አሳቢ የኦሮሞ ሕዝብ ምን መልዕክት ያስተላልፋል? ምንስ ለማትረፍ ነው ይህ ሁሉ የሚፈጸመው? አሮጊቶች፣ ህጻናት ተፈናቅለው በየስርቻው መከራ ሲገፉ ምላሻሽን ምን ሊሆን ይገባል? ይህን ዜና የሰማነው ከመንግስት አይደለም። ከጀርመን ድምጽ ነውና ፕሮፓጋንዳ ነው ብሎ ማለፍ አይቻልም።

ወገን የኦሮሞ ሕዝብ በመራብ ሸዋና በወለጋ አካባቢ የሆነውንና እየሆነ ያለውን እናስብ። ለማን ሲባል እርስ በርስ እየተቋሰልን እንደሆነ እንረዳ። ይህ እየገፋ ከሄደ ወደ አካባቢያዊነት ስሜት መቀይሩ ጥርጥር የለውም። “ሁሉም ኦሮሞ አንድ ኦሮሞ ነው” እየተባለ አንድን አካባቢ ለይቶ ማጥቃትና በሰላም ከመሬት ጋር ተናንቆ የላቡን በሚበላ አርሶ አደር ላይ መዝመት ከሞራልም አንጻር አግባብ አይደለምና አንድ እንበል።

ይህን ተግባር ፈጽሟል የሚባለው ሸኔ ወይም ኦነግ ሸኔ (ስሙ ግልጽ ስላልሆነ ነው) አባላቱ ሕዝብን እንደማያሰቃዩ፣ አድርገውም ከተገኙ እስከ ሞት ድረስ እንደሚቀጡ ጃል መሮ መናገራቸውን ቢቢሲን ጠቅሶ የጀርመን ድምጽ አመልክቷል። ሞትን ምን አመጣው? ጃል መሮ ምን እቅድ እንዳላቸው? ለኦሮሞ ሕዝብ ምን እንደሚያመጡ፣ ለምን የትህነግ ጋር እንዳበሩ፣ ድል ቢየገኙ ምን አዲስ ፍልስፍና እንደሚያጎናጽፉን … እያስረዱን ደጋፊ በማብዛት፣ ሰራዊታቸው ደግሞ የትግል ዲሲፒሊን ያሎእው እንዲሆን በማሰልጠን መንቀሳቀስ ሲገባቸው እንዲህ ባለ መልኩ ለሰሚ ግራ የሚገባ መከራ በአንድ አካባቢ ምስኪን አርሶ አደሮች ላይ ማውረድ እንደ ኦሮሞነቴ አልቀበለውም። እንደ አንድ ሰውም እቃወመዋለሁ። ኦሮሞ ነን የምንል በዚህ ጉዳይ ላይ የከፋ መተራመስ ሳይፈጠርና መሳቂያ ሳንሆን አንድ ልንል እንደሚገባ ይሰማኛል።

መንግስትም “እኔ ያልዘመርኩት” ከሚል ግትር አመለካከት በመውጣት በክልል ደረጃ ነገ ዛሬ ሳትል የሰላም ጥሪ ለማቅረብ ተዘጋጅ። ወደ ተግባር ግባ። ሁሉንም አካተህ ክልሉን የሚያረጋጋ ስልት ለመከተል ወስን። ሰጥተህ ስትቀበል፣ የምትሰጠው በዝቶ የምትቀበለው ካነሰ ለሕዝብ ስትል “እሺ” በል። ወይም ጉልበት ካለህ የህዝብህን ሰላም አስጠብቅ።

እኔ ባለኝ መረጃና እዚሁ ከስር እንዳለ ገልብጬ ባስቀመጥኩት የጀርመን ድምጽ ሪፖርት የአካባቢው ነዋሪ እንዳሉት እንቅስቃሴው ከመንግስት ቁትትር ውጪ ነው። ወይም አይደለም ማለት አይቻልም። ይህ ማለት ችግሩ እውስጥም አለ ማለት ነው። የክልሉ መንግስት በዚህ ደረጃ ውስጣዊ መሰናክል ካለበት የፖለቲካም ይሁን ሌላ አካሄድ ተከትሎ እርምት መውሰድ ግድ ይለዋል።

የጀርመን ድምጽ የሕዝቡን ስቃይ በስም ጠርቶ በይፋ ላዘረዘረውም እንጂ ለመስማት የሚቀፉ፣ ለመናገርም የሚያሙ፣ ድርጊቶች በንጹህ ዜጎችና ቤተሰቦቻችን ላይ እየደረሰ ነው። ደርሷልም። ብዘርዝረው ቂምና የተራ የአካባቢ ስሜት ከመቀሰቀስ ውጪ ጥቅም የለውምና ትቼዋለሁ። ጃልመሮን የምታውቁ፣ ወይም የሱን አለቆች የምትቀርቡ፣ ወይም ለጊዜው ማንነታችሁን ያልገለጻችሁ አመራሮች ካላችሁ እባካችሁን የማንም ብሄርሰብ ይሁን፣ የየትናውም ኦሮሚያ አካባቢ ተወላጅ ይሁን ባልታጠቁ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚፈጸም ጥቃት እንዲቆም ተማጸኑ። እናቶች፣ አባቶች፣ ህጻናት ምን ባደረጉ መከራ ይገፋሉ? ይህ ድርጊትስ ለትግሉ ምን ይጠቅማል? መጨረሻ ግቡስ ምን ደስታ ይፈጥራል? ይድረስ ለኦሮሞ – በኦሮሚያ፣ ለኦሮሞ ሕዝብ ትግል ውስጥ ዝርፊያ፣ ማፈናቀል፣ ግድያና ልማት ማውደምን ምን አመጣው? ለምን?

ጸሓፊው ከአውሮፓ ናቸው። ለማሳያ የተጠቀሙበትን የጀርመን ድምጽ ዘገባ ከስር አትመነዋል።
በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን አምስት ወረዳዎች በከፊልና ሙሉበሙሉ ኦነግ ሸነ በተባሉት ታጣቂዎች ቁጥጥር ስር መሆናቸውን ነዋሪዎች እና ባለስልጣናት ገለጹ። በዞኑ ታጣቂዎቹ የተቆጣጠሯቸው አከባቢዎች አርሶ አደር ማምረት ማቆሙንና ሰዎች ለተለያዩ እንግልትና ሰቆቃ እንደሚዳረጉም ተነግሯል። የማህበራዊ አገልግሎትና የመንግስት ስራም በነዚህ አከባቢዎች ሙሉ በሙሉ በመቋረጡ ተማሪያች ከትምህርት ገበታቸው ተፈናቅለዋል፣ ጤና ጣቢያዎችም አገልግሎት አይሰጡም ተብሏል። 
ሳራ ጅብቻ በጉጂ ዞን የጉሚ ኤልዳሎ ወረዳ ነዋሪ ናቸው፡፡ አሁን ላይ ከአራት ወራት በፊት የሶማሌ ክልልን ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን የምታዋስነውን ይህቺን ወረዳ ሙሉ በሙሉ መንግስት ሸኔ በሚል ስም በሽብርተኝነት በፈረጀውና እራሱን የኦሮሞ ነጻነት ጦር በሚል በሚጠራው ሽምቅ ተዋጊዎች ቁጥጥር ስር በመግባቷ ተፈናቅለው በዞኑ መዲና ነጌለ ከተማ ተጠልለው ይገኛሉ። 
“ጉሚ ኤልዳሎ በሸማቂዎቹ ስር ከገባች አራተኛ ወር እያስቆጠረ ነው፡፡ እኛ ለዓመታት በጦርነት ውስጥ ነው ያሳለፍነው፡፡ አሁንም ሰላም እንደራቀን ነው፡፡ ባንድ በኩል ድርቅ በሌላው ደግሞ ግጭት ጦርነቱ እያሳደደን ግራ በተጋባ ህይወት ውስጥ ነን፡፡ ድርቁ ከብቶቻችንን እየገደ ለርሃብ ሲዳርገን፣ የፀጥታ ችግሩ ደግሞ ትራንስፖርት እንኳ እንዳይኖር በማድረግ የተራቡት ለሞት እየዳረገ ነው፡፡ ሰው በርሃብም በጥይትም በየቀኑ ነው የሚሞተው፡፡ ስቃይ ውስጥ ነን፡፡” 
ለደህንነታቸው ሲባል ስማቸውን እንዳይጠቀስ የጠየቁን ሌላው በዞኑ የዋደራ ከተማ ነዋሪ በበኩላቸው እሳቸው ከሚገኙበት ከተማ ውጪ ያሉ በርካታ የገጠር ቀበሌዎች በታጣቂዎች ቁጥጥር ስር ናቸው።


“ታውቃለህ ይህቺ ከተማ ዙሪያዋ በድን የተከበበ ነው፡፡ ሶስት አምስት ኪሎ ሜትር ወጣ ብትል እንኳ ታጣቂዎች ተሰግስገውበታል፡፡ ከዚህ ከተማ ሰው በየትኛውም አቅጣጫ ሲወጣ እያገቱ ብር ይለቅማሉ፡፡ ሰው ያለውን ሁሉ ይዘረፋል፡፡ ከገጠር ቀበሌዎችም እየተነሱ ይሄው ወደ ከተማዋ እየተሰደዱ ነው፡፡ የመንግስት የፀጥታ ኃይሎች ሲወጡ በቦታው አያገኙዋቸውም፡፡ ከመንግስት አቅም በላይ ሆኗል ለማለትም ሆነ መንግስት አከባቢውን እያስተዳደረ ነው ለማለት ተቸግረናል። ”
የጉጂ ዞን መንግስት ኮሚዩኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ ዮሓንስ ኦልኮ በቡላቸው ለዶይቼ ቬለ በሰጡት ማብራሪያ በዞኑ አምስት ወረዳዎች በከፊል እና ሙሉ በሙሉ በታጣቂዎች እጅ ስር በመውደቃቸው ከፍተኛ ቀውስ ተከስቷል፡፡ እንደ ኃላፊው ገለጻ ሰው በቁም ከመቀበር ጀምሮ በነዚህ አምስት ወረዳዎች አስከፊ ያሉት ሰቆቃዎች በህብረተሰቡ ላይ ይፈጸማል፡፡ በመንግስት መዋቅር የሚሰሩ ይገደላሉ፤ ተቋማቱም ይዘረፋሉ የሚሉት አቶ ዮሓንስ እየታገቱ ብር የሚጠየቅባቸውም ብዙ ናቸው ብለዋል፡፡ 
ይህ ሁሉ ሲሆን የመንግስት የፀጥታ አካላት ሚና ምን ነበር የተባሉት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ አሁን አሁን እየተወሰደ ነው ባሉት እርምጃ መሻሻሎች መኖራቸውን አውስተዋል፡፡ 
በነዚህ አከባቢዎች ትራንስፖርት ጨምሮ ምንም አይነት የማህበራዊ መገልገያዎች እንደሌሉም ተነግሯል፡፡ ከማህበረሰቡ የተዘረፉ ተሸከርካሪዎችን ታጣቂዎቹ እንደሚጠቀሙም እንዲሁ። ባለፈው ማክሰኞ ስለጉዳዩ ተጠይቀው ለህ/ተ/ም/ቤት ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በዓላማቢስነት የፈረጁትን ሸማቂ ቡድን ከሚከተሉት የጦር ስልት አንጻር ለጸጥታ ኃይላቸው ፈታኝ መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል። 
የኦሮሞ ነጻነት ጦር የምዕራብ ግንባር አዛዥ ኩምሳ ድሪባ (መሮ) ባለፈው ሳምንት ጦራቸው በህዝብ ላይ ያደርሳል ስለተባለው ሰቆቃ በቢቢሲ ተጠይቀው መሰል ተግባር የፈጸመ ታጣቂያቸው እስከ ሞት እንደሚቀጣ ነበር የመለሱት። 

Exit mobile version