Site icon ETHIO12.COM

የድንቅ የሂሳብ ፈጠራ ባለቤት ሙሉጌታ ፈንታው የኢንሳ ባልደረባ ሆነ

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ( ኢንሳ) የድንቅ የሂሳብ ፈጠራ ባለቤት የሆነውን ሙሉጌታ ፈንታውን ተቀብሎ ምርምሩን ለማስቀጠል ወሰነ

የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ሹመቴ ግዛው(ዶ/ር) ዛሬ ማለዳ ተመራማሪ የሺ ፈንታውን ከኢሳት ተረክበዋል::

በዚህ ወቅት ባለ ምጡቅ አዕምሮው ሙሉጌታ የሀገርን ስም የሚያስጠራ በመሆኑ ድርጅቱ ሀላፊነት ወስዶ እንደሚሰራ ተናግረዋል::

በዚህም ሙሉጌታ ከዛሬ ጀምሮ የተቋሙ ባልደረባ ሆኖ ኢትዮ ሳይበር ታለንት ሴንተር ቦታ ተሰጥቶት ምርምሩን እንዲቀጥል ዶ/ር ሹመቴ ለስራ ክፍሉ መመሪያ ሰጥተዋል::

በቀጣይ የምርምር ስራዎቹ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲታወቁ ኢንሳ ሙሉ ሀላፊነት ወስዶ እንደሚሰራም ገልፀዋል::

ከዚህ ጎን ለጎን ለሙሉጌታ የቁሳቁስና የገንዘብ ድጋፍ ማድረግ የሚፈልጉ በራሱ በኩል ድጋፋቸውን አጠናክረው መቀጠል እንደሚችሉም አክለዋል::

ኢንሳ ግን የምርምር ስራውን በሙሉ ሀላፊነት አስፈላጊውን ሁሉ አሟልቶለት እንደሚያስቀጥል አረጋግጠዋል::

በርክክብ ስነስርዓቱ የኢሳት ተወካይ ጋዜጠኛ ጌራ ጌታቸው እንዲሁም የላሊበላና አካባቢው የፓርላማ ተወካይ ወ/ሮ ቅድስት አርዓያ እንዲሁም የአካባቢው ተወላጅና ከኢሳት ጋር በመነጋገር ለሙሉጌታ ማረፊያ ቤት በመስጠት ያስቀመጡት አቶ በረደድ ጌታነህ ተገኝተዋል::

ሙሉጌታ እስካሁን በኢሳት ክትትል ስር የቆየ ሲሆን የልጁን አቅም የተረዳው የኢሳት ማኔጅመት ለሙሉጌታ አካላዊና ስነ ልቦና ድጋፎችን በማድረግ እንደሚደግፈው ማስታወቁ ይታወሳል።

የኢንሳ ዳይሬክተር ሹመቴ ግዛው (ዶ/ር) ኢሳት ለሰራው ስራ ምስጋና አቅርበዋል::

ሙሉጌታ ፈንታው ተወልዶ ያደገው በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን መቄት ነው።

ከመቅደላ አምባ ዩኒቨርስቲ በአፕላይድ ማቲማቲክስ የመጀመሪያ ዲግሪውን አግኝቷል።

ሙሉጌታ ገና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እየተከታተለ እያለ ጀምሮ የሂሳብ ትምህርት ላይ የተለየ ተሰጥናኦ ፍቅር እንደነበረው ይናገራል።

በወቅቱ የነበሩት የትምህርት ቤቱ መምህራን ብዙም ትኩረት ባየሰጡትም እርሱ ግን በራሱ መንገድ በሂሳብ ላይ የሚያደርገው ጥልቅ ምርምር አላቋረጠም ነበር።

በዩኒቨርስቲ ገብቶም በአፕላይድ ማትስ ትምህርቱን በመከታተል ላይ እያለ በ2008 ዓመተ ምህረት ላይ ከኮምፒውተር አቅም በላይ የሆኑ ብዜቶችን በቀላሉ ለማግኘት የሚያስችል የሂሳብ ቀመርን ለመፍጠር ቻለ።

ሙሉጌታ በ2011 አመተ ምህረት የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ የፈጠራ ስራ ለሰሩ ወጣቶች ሽልማት በሰጡበት ወቅት በሰራው የሂሳብ ቀመር ስራ ልዩ ተሸላሚ ከነበሩት አምስት ወጣቶች ውስጥም አንዱ ነበር።

Via ESAT

Exit mobile version