Site icon ETHIO12.COM

አደገኛው ህግ ወደ መዝገብ ቤት በተላከ ማግስት፣ ዓለም ባንክ የ300 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ አጸደቀ

አፋር፣ አማራ፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ ኦሮሚያ እና ትግራይ የመልሶ ግንባታው አካላት መሆናቸው ተገልጿል

 “ኤችአር6600” የተሰኘውና “የኢትዮጵያን ሰላም፣ ዲሞክራሲና መረጋጋት መደገፍ” በሚል ሽፋን በኢትዮጵያ ሉዓላዊነትና ጥቅም ላይ ጥቁር ጥላ የሚያጠላል የተባለው ህግ በይደር እንዲቆይ በተደረገ ማግስት ዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የ300 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማጽደቁ ታላቅ የዲፖሎማሲ ድል ተደርጎ እንደሚወሰድ ተሰማ።

የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ በግጭት ምክንያት የተጎዱ አካባቢዎችን መልሶ ለመገንባት ለተዘጋጀ ፕሮጀክት የሚውል የ300 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ድጋፍ ማጽደቁ ነው የተሰማው።

ባንኩ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በላከው መግለጫ ይህ ዓለም አቀፍ የልማት ድጋፍ በኢትዮጵያ ግጭት በነበረባቸው አካባቢዎች የተጎዱ ሰዎችን መልሶ ለማቋቋም እና የወደሙ መሰረተ ልማቶችን መልሶ ለመገንባት እንደሚውል አስታውቋል።

በተለይም ድጋፉ የመሰረታዊ አገልግሎት አቅርቦትን ለማሻሸል እና ለዓየር ንብረት ለውጥ የማይበገር መሰረተ ልማት ለመገንባት እንደሚውል በመጠቆም፥ በግጭት የተጎዱ የህብረተሰብ ክፍሎችን እንደሚያስቀድም ነው ባንኩ ያመለከተው። በዚህም መሰረት አፋር፣ አማራ፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ ኦሮሚያ እና ትግራይ ክልሎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑም አስታውቋል።

በአጠቃላይ ድጋፉ ከ5 ሚሊየን የሚበልጡ ሰዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ነው ባንኩ በመግለጫው ያስታወቀው።

ውጤታማ እና ፈጣን ምላሽ ለመስጠትም በማሰብ የገንዘብ ድጋፉ በፌደራል መንግስት፣ በክልል መንግስታት እና በአካባቢዎቹ በሚንቀሳቀሱ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች በኩል እንደሚቀርብም ገልጿል።

የአለም ባንክ 300 ሚሊዮን ዶላር ልገሳ ምን ይነግረናል ? ሲሉ አቶ ሳምሶን ሚካሎቪች ይህን አሳብ በማህበራዊ አውዳቸው አስፍረዋለ።

የአለም ባንክ ለኢትዮጵያ መልሶ ማቋቋሚያ ዛሬ ለገስኩት ያለው ገንዘብ ከነዋያዊ ፋይዳው ይልቅ ፖለቲካዊ አንድምታው ያመዝናል።

፩. ይህ ልገሳ HR6000 ሳይወለድ መጨንገፉን ያሳያል። የዚህ የህግ ማዕቀፍ አርቃቂዎች ኢትዮጵያ ከባንኩና IMF የገንዘብ ድጎማ እና ብድር እንዳታገኝ ወትውተዋል። ከጅምሩ ምልጃቸው የተሳካ አይመስልም።

፪. አሜሪካ የአለም ባንክ ዋንኛ የገንዘብ ምንጭ ናት። ባንኩ ልገሳም ይሁን ብድር ሲሰጥ የአሜሪካ ይሁንታ ግድ ነው። እናም አሜሪካ ከልምጭ ይልቅ ኢትዮጵያን በካሮት ለማባበል ስትራቴጂ ይዛለች ማለት ነው። የአሜሪካ የስራ አስፈጻሚው ክፍል ከህግ አውጪው በተቃራኒ ሄዶ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ልዩነት በዲፕሎማሲ ለማስታረቅ የመወሰኑ ምልክትም አድርገን ልንወስደው እንችላለን።

፫ .የገንዘብ ድጎማው የሰሜኑ ጦርነት ወደ መቆሙና ኢትዮጵያ ወደ መልሶ ማልማት እየተመለሰች እንደሆነም ያሳያል። አንዳንድ ሰዎች መንግስት ጦርነቱን ማቆሙን ይተቻሉ መለስ ብለውም የኑሮ ውድነቱን ያማርራሉ። ጦርነት የሀገር ሀብት ይበላል ፣ ኢንቨስትመንት ይገድላል ፣ ኢኮኖሚ ይደቁሳል የውጭ እርዳታና ልገሳን ያዳክማል። መንግስት ጦርነቱን ለማቆም መወሰኑ እጅግ ብልህነት የተሞላበት ውሳኔ ነው ፖለቲካዊ ኪሳራ ቢኖረውም። ፖለቲካ ደግሞ ሁሌም calculated risk የምትወስድበት ሂደት ነው።

Exit mobile version