Site icon ETHIO12.COM

ከሶማሊ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት የተሰጠ ወቅታዊ የአቋም መግለጫ

የሶማሊ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በሀገራችን እና በክልላችን ሰላምና መረጋጋት እንዳይኖር ከቅርብ ግዜ ወዲህ እየታዩ እና እያቆጠቆጡ ያሉ አካሄዶችን በአፅንኦት ሲመለከት ቆይቷል።

በተለይም ፅንፈኛ በሆኑ አካላት በሃይማኖት ሽፋን ከውጭ ሃይሎች ጋር በመስራት አብሮ ተዋልዶና ተጋብቶ በኖረ ህዝብ መካከል መከፋፈልን እና ብጥብጥን ለመፍጠር እየተሰሩ ያሉ እኩይ ተግባራትን የክልላችን መንግስት እና ህዝብ አጥብቆ የሚኮንነው እና የሚያወግዘው ተግባር ነው።

የክልላችን መንግስት በተለይም ብሄር እና ሃይማኖትን ሽፋን በማድረግ ክልላችንን የሁከትና ብጥብጥ መናኸሪያ ለማድረግ የሚሞክሩና በህጋዊ ፖለቲካ ፓርቲ ሽፋን ለውጭ አካላት የሚላላኩ ሃይሎችን ጭምር ለይቶ በማውጣት እስፈላጊውን ጥብቅ እርምጃ እንደሚወስድ ለማሳሰብ ይወዳል።

በመሆኑም ሁሉም ኢትዮጵያዊና የክልላችን ነዋሪ ከውጭ አካላት በሚወረወር ፍርፋሪ ሀገር ለማፍረስ የሚንቀሳቀሱ ተደርጎ ተቀባዮቻቸውን ነጥሎ በማውጣት ለህግ በማቅረብ እንዲሁም ኢትዮጵያን ለመበታተን እያሳዩ ያሉትን ጥረት በንቃት በመከላከል ከመንግስት ጎን በመቆም በሃይማኖትም ሆነ በብሄር ሽፋን የሚፈፀም ሽብርተኝነትንና ፅንፈኝንትን በጋራ እንዲመክትና አምርሮ እንዲታገል ልናሳስብ እንወዳለን።

የሶማሊ ብሄራዊ ክልላዊ መንግሥት
ሚያዚያ 24/2014
ጅግጅጋ

Exit mobile version