Site icon ETHIO12.COM

በአስር ዓመት 4.4 ሚሊዮን ቤቶች ይገነባሉ

በመንግስት ደረጃ የመኖሪያ ቤት ፍላጎትና አቅርቦት ችግርን በውል በመረዳትና ለዜጎቹም ተደራሽ ለማድረግ ባለፉት ዓመታት የተደረጉ ጥረቶች ያስገኙት ውጤት እንዳለ ሆኖ ያጋጠሙ ችግሮችንና ተግዳሮቶችን በመፈተሸ በተለይም በአሁኑ ወቅት ዘርፈ ብዙ አማራጮችንና ዕድሎችን ለመጠቀም በአዲስ ጉልበትና በአዲስ አቅጣጫ እየሰራ እንደሚገኝ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትሯ ክብርት ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ አስታወቁ ።

በዛሬው ዕለት በሪል ስቴት ልማት ዘርፍ ከባድርሻ አካላት ጋር ለመወያየት የተዘጋጀውን አገር አቀፍ የምክክር መድረክ ሲከፍቱ እንደተናገሩት በመኖሪያ ቤት ልማቱ የግሉን ዘርፍ ሚና ከፍ በማድረግና ፖሊሲዎችንም ጭምር በመከለስ “የቤት ልማት ስትራቴጂ” ሰነድ ማዘጋጀቱን ተናግረዋል። በዚህም የመኖሪያ ቤቶች ኪራይ አማራጭ እንደ አንድ አቅጣጫ መወሰዱን ተናግረዋል።

“ከባለፉት ዓመታት የልማት ውጤቶችና ልምድ በመነሳት በሃገራችን በመኖሪያ ቤት ልማትና አስተዳደር ዘርፍ መዋቅራዊ ለውጥ በማድረግ በቤት ልማት ዘርፍ የግል ሴክተሩ የአንበሳውን ድርሻ እንዲወስድ የሚያስችል ስራ እየተከናወነ ይገኛል” ያሉት ሚኒስትሯ በሚቀጥሉት አስር ዓመታታ በከተሞች ለመገንባት ከተያዘው 4.4 ሚሊዮን ቤት የግል ሴክተሩ 80 በመቶውን ይሸፍናል ብለዋል።

የግል ባለሃብቶች በመኖሪያ ቤቶች ልማት ውስጥ የሚኖራቸውን ተሳትፎ ትርጉም ባለው መልኩ በከፍተኛ መጠን ለማሳደግ ከመታቀዱ ጋር ተያይዞ በተለይም በመካከለኛ እና ከፍተኛ ገቢ ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎችን የመኖሪያ ቤት ዕጥረት ለመፍታት የሚያስችሉ አቅሞችና ዕድሎችን በሚገባ በመፈተሸ፣ በማገዝና በመደገፍም ጭምር ያለውን የአቅርቦት ችግር ለመፍታት መንግስት እየሰራ ይገኛል ሲሉ ገልፀዋል።

በዘርፉ አቅም ያላቸውን የሪል እስቴት አልሚዎች በሚፈለገውና በታቀደው መልኩ እንዲሰሩ የሪል ስቴት ልማቱ፤ ግብይቱም ሆነ የዋጋ ትመናው በቂ የህግ ስርዓት እንዲመራ እንሰራለን ሲሉ የገለፁት ክብርት ወ/ሮ ጫልቱ የሪል ስቴት አልሚዎች በተገቢው መንገድ እንዲደራጁ በማድረግ ከመንግስት የሚደረግላቸውን ድጋፍ መጠቀም እንዲችሉ ዘርፉን በህግ አግባብ መምራትና የትብብር መንፈስ መፍጠር ወሳኝ ጉዳዮች መሆናቸውን ገልፀዋል።

በምክክር መድረኩ ላይ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የከተማ ትራንስፖርትና መሰረተ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ ወ/ሮ ሸዊት ሻንካና የተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ሚኒስትር ዴኤታዎች እንዲሁም በዘርፉ የሚገኙ ባለድርሻ አካላት፣ የሪል ስቴት አመራሮችና ባለቤቶች ተገኝተዋል። ከአዲስ አድማስ ፌስ ቡክ ገጽ የተወሰደ

Exit mobile version