Site icon ETHIO12.COM

የመንግስት ማጅራት መቺዎች ፈተና ሆነዋል – ሃላፊዋ አምነዋል

እጅ መንሻ የሚያቀርቡትም ሆነ በህግ አግባብ ጉዳያቸው እንዲፈጸምላቸው የሚጠይቁ ነዋሪዎች በአንድ ነገር ይስማማሉ። ” የመንግስት ማጅራት መቺዎች” በሚለው። እነዚህ ” ማጅራት መቺዎች” የመንግስት መዋቅር ውስጥ የተጠቀጠቁና ጠቅላይ ሚኒስትሩ “አታቆላምጧቸው” ሲሉ በገሃድ ” ሌቦች” የሚሏቸው ናቸው።

በሀገራችን በተለይ በአዲስ አበባ እጅግ በጣም ሙስና ስር ከሰደደበት አንዱ የመሬት ዝውውር ጉዳይ ነው። በዚህ ሂደት አንዳንድ የአስተዳደሩ አመራሮችና ባለሙያዎች ደላላ ሆነው መገኘታቸውን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ አስተዳደር የፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሂክማ ከይረዲን ለኢፕድ ተናግረዋል። ጉዳይ አዲስ ዜና ባይሆንም በግልጽ ይህንኑ ችግር አምኖ መቀበሉ ዜናውን ዜና አድርጎታል።

” በመሬት ጉዳይ ብልሹ አሰራሮች በከተማው ተስፋፍቷል፣ በተለይ ደላላ የበዛበትና ለሙስና የተጋለጠ የመሬት ዝውውር ስርዓት በከተማዋ ታይቷል ” በሚል ወይዘሮ ሂክማ ተናግረዋል። አክለውም “አንዳንድ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና ባለሙያዎች ከባለሃብትጋር በመመሳጠር መሬትን በህገወጥ መንገድ ለማስተላለፍ የሚደረጉ ሙከራዎች በተደጋጋሚ ታይተዋል” ብለዋል። በመረጃ በተደገፈ ሁኔታ የተያዙ አመራሮችና ባለሙያዎች ወደ ሕግ እንዲቀርቡ መደረጉንም ለኢፕድ አመልክተዋል። ይሁን እንጂ ዝርዝሩ አላብራሩም።

የከተማው አስተዳደር ፤ የመሬት አገልግሎትን በተመለከተ በቀጣይነት ሁለት አይነት አሰራር እንደሚተገበር የተጠቆመ ሲሆን ፥ መሬትን ዲጂታላይዝ በማድረግ የግልጸኝነት አሰራርን ማስፈን እና የመረጃ አያያዝ ሥርዓቱን በማጠናከር ሕዝብ እያንዳንዱን መረጃ እንዲያገኝ ማድረግ የትግበራው አካል መሆኑን እንደ አማራጭ መፍትሄ ሃላፊዋ አስታውቀዋል። መሬት ለሌላ አካል የሚተላለፍበት መንገድ ህዝብን እንዲያሳትፍ አቅጣጫ መቀመጡንም ተነግሯል።

አዲስ አበባ ብቻ ሳትሆን ድፍን አገሪቱ ከመሬት ጋር በተያያዘ ሌብነት ፈተና መሆኑንን ህዝብ እየተናገረ ነው። ባለስልጣናትም ይህንኑ እየደገሙ ነው። ይህ ስር የሰደደ የሙስና በሽታ በዘመቻ እርምጃ ይጀመርበታል በሚል በተደጋጋሚ ቢገለጽም በሚፈለገው ደረጃ ሲፈጸም አልታየም። ለዚህም ይመስላል “የጸረ ሙስና ኮሚሽን ራሱ ሌላ ኮሚሽን ሊቋቋምበት ይገባል” ሲሉ ጥርስ አልባ የፖለቲካ አጀንዳ ማስፈጸሚያ ተቋም መሆኑንን ዜጎች ሲተቹት መስማት የተለመደ ነው።

ውህዳን የሚባሉትን የትህነግ አመራሮች ለማሰር በአንድ ለሊት እንደተቋቋመ የሚነገርለት ይህ ኮሚሽን ራሳቸው በጉቦ መሬት የተመሩ መሆናቸውን ያመኑ ኮሚሽነር ተመድበውለት የነበረ ተቋም እንደነበር ይታወሳል። ከተቋቋመ ጀምሮ ያዝ ለቀቅ በማድረግ ስራውን ሲሰራ የኖረው ኮሚሽኑ ሌባ ማደኑን አቁሞ ” የአሰራ ጥናት ማከናወኛ ተቋም” እስከ መባል ደርሶ ነበር።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከፌደራል ፖሊስና ከኢኮኖሚ ደህነት ጋር ተቆራኝቶ መንቀሳቀስ የጀምረው የጸረ ሙስና ኮሚሽን የወደፊት ሩጫው በግልጽ ባይታይም ዛሬም በተመሳሳይ መልኩ እንደ ቀድሞው ” በድዱ ያለ ጥርስ አልባ” ተቋም እንዳልሆነ ማሳየት እንዳልቻለ ይተቻል።

Exit mobile version