Site icon ETHIO12.COM

ኢትዮጵያ ሳታውቅ ድርድር የለም፤ መከላከያን መንካት “አትዋጉ” ማለት ነው

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከህወሓት ጋር እስካሁን ድርድር ተጀምሯል የሚባለው ወሬ መሰረተ ቢስ መሆኑን ተናገሩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ ከህወሓት ጋር ለመደራደር ኮሚቴ ተቋቁሞ አስፈላጊ ሁኔታዎችን እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ኮሚቴው ሥራውን ሲያጠናቅቅ ለሕዝብ ይፋ እንደሚሆንም ተናግረዋል፡፡ ህወሓት የአማራ ክልል ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ጠላት በመሆኑ ኢትዮጵያ ሳታውቅ ድርድር እንደሌለም አንስተዋል።

የጸጥታ ተቋማት ሁኔታን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ ተቋሞቻችን ለህወሓት ብቻ አይዘጋጁም፤ ኢትዮጵያን ለማስቀጠል ነው የሚዘጋጁት ብለዋል፡፡ በአሁናዊ ሁኔታውም ከህወሓት የስልጣን ዘመን ጊዜ 3 እና 4 እጥፍ በላይ በቴክኖሎጂም ሆነ በቁጥር ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምላሻቸው ከህወሓት ጋር የተፈጠረው ግጭት መንስኤ ህወሓት የፖለቲካ ክስረቱን መንግስትን ለማፍረስ የሄደበት የኃይል አማራጭ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይህን ለማሳካትም እስከ ሲኦል እንወርዳለን ማለታቸውን አስታውሰው፥ እኛ መዋጋት ሳይሆን እራሳችንን መከላከል ነው ያደረግነው ብለዋል።

በህወሓት አስተዳደር የትግራይ ሕዝብ ያተረፈው ጥላቻን ብቻ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ አሁንም ችግርና ስደት እንዳለና አመራሮቹ የራሳቸውን ኑሮ የተሻለ ሊያደርጉ ቢችሉም ለሕዝቡ አለመስራታቸውን አውስተዋል። ህወሓት ትግራይን ባስተዳደረበት ከሶስት ዓመታት በላይ ጊዜ ሕዝቡን እና አካባቢውን አለማልማቱን በመጥቀስም፥ ለልጆቻችን ሰላምን ማውረስ ይገባናል፤ ሀገር በጦርነት አታድግም ብለዋል በምላሻቸው።

ኢትዮጵያ በሀገራት መካከል ሰላም እንዲኖር አበክራ ትሰራለች ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፥ ኢትዮጵያውያን ሰላም ወዳድ መሆናችንን ዓለም መስክሯል ብለዋል በማብራሪያቸው። ውጊያ ከማንም ጋር አንፈልግም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ሰላም ነው የምንፈልገው፡፤ ሰላም ደግሞ ትርፋማ ነው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፍላጎት ግጭት እንዳይኖር ማድረግ መሆኑን በመጥቀስም፥ በሀገራት መካከል ሰላም ቢኖር ትርፉና ጥቅሙ ብዙ ነው ሲሉም አስረድተዋል፡፡ ለዚህም በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የነበረውን ግጭት በሰላም እንዲተካ መደረጉን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያም ከራሷ አልፎ ለቀጠናው ሰላም አበክራ ትሰራለች፤ እየሰራችም ነው ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፡፡

ከሳይበር ደኅንነት ጋር በተያያዘ 5 ሺህ 600 አካባቢ የቨርቹዋል ጥቃት መድረሱን ተናግረዋል፡፡ ሰላምን የሚያናጋ ሁኔታ እንዳይፈጠር እየሠራን ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በሰላም የሚገኝ ድል ካለ ሰላም ለማምጣት በትኩረት እንደሚሰራ አንስተዋል።

ከሕግ ማስከበር ጋር በተያያዘ በሰጡት ማብራሪያ ባለፈው ጉባኤ ሰላም፣ የዋጋ ግሽበት እና መልካም አስተዳደር ላይ በትኩረት እንደሚሠራ መግባባት ላይ መደረሱን አስታውሰዋል፡፡ ከ1 ሺህ በላይ የሸኔ አባላት በኦሮሚያ ክልል መደምሰሳቸውን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በአማራ ክልል የተወሰደው ሕግን የማስከበር ሥራ መቶ በመቶ በክልሉ ኃይል የተሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተሠራው የዘመቻ ሥራ የአማራ ክልልም ሆነ የምዕራብ ጎጃም ሕዝብ ደስተኛ መሆኑንም ነው የገለጹት።

በአማራ ክልል በተወሰደው ሕግ ማስከበር ዘመቻ 3 ሺህ 500 ያህል ሰው በቁጥጥር ስር መዋሉን ገልጸው÷ ሁሉም የከዱ ሠራዊት መሆናቸውን ነው የተናገሩት። ከእነዚህ መካከል ደግሞ ከ2 ሺህ በላይ ያህሉ የክልሉ ልዩ ኃይል አባላት መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

ብዙ ኩንታል ሀሽሽ፣ ሕገ ወጥ ገንዘብ ሁሉ ተይዟል ብለዋል፡፡ በሌሎች ክልሎችም በሰላም፣ የኑሮ ውድነቱን በመቀነስ ረገድ ሰፊ ሥራዎች ተሰርተዋል ነው ያሉት፡፡ ለአማራም ሆነ ለኢትዮጵያ የሚበጀው አንድነት መሆኑን መገንዘብ ይገባል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በተካሄደው ዘመቻ በስህተት የተያዘ እና አላግባብ የታሰረ ወይም የተጎዳ ሰው ካለ ምክር ቤቱ ኮሚቴ አቋቁሞ ማጣራት ይችላል ነው ያሉት፡፡

ከዘመቻው በኋላ በአማራ ክልል ሰላም መስፈኑን እና ዜጎች በሰላም እየኖሩ መሆኑን ገልጸው፥ የሕግ ማስከበር ሥራው በሁሉም ክልሎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አጽንኦት ሰጥተዋል፤ ሕግን ማክበር ግዴታ መሆኑን በመጥቀስ።

በዚህ መሐል የተከበሩ ሙያዎችን ለወንጀል መደቢቂያነት መጠቀም በሕግ ያስጠይቃል፤ ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት፡፡

ተረኝነትን በሚመለከት ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ÷ ኢትዮጵያ ለሁላችንም የምትበቃ ቤት ነች፤ የአንዱ ብቻ ልትሆን አትችልም ብለዋል፡፡

‹‹ሀገርን እንደ እቁብ የሚቆጥሩ ሰዎች አሉ፤ ቀጣይ አንተ ትመራለህ፤ ቀጣይ ደግሞ እከሌ ይመራል›› የሚል አስተሳሰብ እንደ ህወሓት የከሰረ አካሄድ ነው፤ ሁሉንም ያካተተ እንጅ የፈረቃ አካሄድ የለም ነው ያሉት በምላሻቸው፡፡

በአጠቃላይ ተረኝነት የለም፤ በካቢኔ አባላትም 6 አማራ፣ 6 ደቡብ እና 6 ኦሮሞ የሆነው በዚህ ጊዜ ነው ሲሉም ነው ያስረዱት።

በአዲስ አበባ ከተማ በኦሮሚኛ መዝሙር ተዘመረ ብሎ ቅሬታ ማቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡ በመዲናዋ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ቋንቋዎች ሲዘመር ምንም ያላለ ሰው፤ በኦሮሚኛ ተዘመረ ብሎ ሊከፋው አይገባም ኢትዮጵያዊነት ማለት የቋንቋ ብዝሃነትም ነው ብለዋል፡፡

ከተለያዩ አካባቢዎች የተወከሉ የሕዝብ ተወካዮችም ሕዝቡን የሚጠቅም ሥራ እንጅ የመበሻሸቅ ጉዳይ እያነሱ ማራገብ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡

ሁሉን አካታች ውይይትን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ÷ ኮሚሽን የማቋቋም ስልጣን፣ አጀንዳ ማዘጋጀት እና ተሳታፊዎችን የመወሰን ስልጣንን ያለ መንግሥት ጣልቃ ገብነት በኮሚሽኑ እንዲፈጸሙ ኃላፊነት መሰጠቱን አራርተዋል። ሥራው አድካሚ ቢሆንም÷ ኮሚሽኑ በርካታ ችግሮችን እንደሚፈታም ያላቸውን ዕምነት ገልጸዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ  ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 13ኛ መደበኛ ስብሰባው፥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሰጡትን ምላሽና ማብራሪያ አዳምጧል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እየሰጡት ባሉት ምላሽ÷ ባለፉት አራት ዓመታት የተከሰቱ ሰው ሰራሽ እና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ልናሳካው ያሰብነውን ዕቅድ በታሰበለት ልክ እንዳይሄድ አድርገውታል ብለዋል፡፡ ያልተገነባ ሰው ተቋም አይገነባም፤ ያልተገነባ ተቋም ደግሞ ሀገር አይገነባም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ÷ የሰው ልጅ ለሀሳብ ክብር ሊሰጥ እና ዘር የማያመክን ሊሆን እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

በተሰጠው ጊዜ የማይጠቀም አካል ትርፉ ጸጸት መሆኑን ገልጸው÷ ሁሉም አካላት የጊዜ አጠቃቀምን ሊገነዘቡ ይገባል ነው ያሉት፡፡ ለዚህም ሁሉም ጣት ከመቀሳሰር ይልቅ ወደ ራሱ በማየት በተሰማራበት መስክ ጊዜን በአግባቡ ሊጠቀም እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡

ሰው ራሱን ብሎን አካባቢውን ለማልማትና ለማሳደግ ቁርጠኛ ካልሆነ ለሀገር ልማት ተባባሪ ሊሆን አችልም ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ስለሆነም ችግርን ሲተነትኑ ከመኖር ይልቅ ሁሉም ሰው ለሀሳብ፣ ለጊዜ እና ከራሱ ጀምሮ እስከ ሀገር ባሉ የጋራ ጉዳዮች ላይ ቁርጠኛ እና ተባባሪ መሆን ይገባዋል ነው ያሉት፡፡ እንዲህ ሲሆን ችግሮቻችን ይቀላሉ፤ ዕድገታችን ይፋጠናል ብለዋል፡፡

የሚሠራ ሰው ጠዋት ቢወቀስም ማታ መሞገሱ እንደማይቀር ጠቁመው÷ የዛሬውን ወቀሳ ሳይሆን የነገውን ሙገሳ በማሰብ በትጋት መሥራት ይገባል ነው ያሉት፡፡

የለውጡን ጉዞ በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ማብራሪያ ያጋጠሙንን ተግዳሮቶች በትክክል መገንዘብና ታሳቢ ማድረግ እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው፥ ኮቪድ፣ የአንበጣ መንጋ፣ ጎርፍ፣ ድርቅ ተፈጥሯዊ ተግዳሮቶች እንቅፋት መሆናቸውን አንስተዋል።

ከዚህ ባለፈም በሀገር ውስጥ የገጠመን ውጊያ ከፍተኛ ሰብአዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ማስከተሉን ጠቅሰው፥ መፈናቀል እና ያልተገባ የውጪ ጫና እንዲሁም የሀገር ውስጡ ሁኔታ ጋብ ሲል የዩክሬን እና የሩሲያ ግጭት ያስከተለው ዓለም አቀፍ ጫና ተጋላጭ ሆነናልም ነው ያሉት በማብራሪያቸው።

ከዚህ አንጻርም “የገጠሙንን ፈተናዎች እንዴት አለፍናቸው የሚለውን ማየት” አስፈላጊ መሆኑን አውስተዋል። የተደረገው ውጊያ ኢትዮጵያ እንዳትፈርስ የመታደግ ሥራ እንደነበር ማስታወስ እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው ፥ ለብልጽግና መሰረቶችን ጥለናል ነው ያሉት።

“ይህ ሁሉ ፈተና እንደ መንግሥት፣ እንደ ፓርቲ በወጉ ሳንደራጅ የገጠመን ችግር መሆኑን ታሳቢ ማድረግ” እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል፡፡ ከመንገድ አውታር ጋር በተያያዘ በሰጡት ምላሽ ከለውጡ በፊት ሀገር አቀፍ ሽፋኑ 127 ሺህ ኪሎ ሜትር መሆኑን ገልጸው ከለውጡ በኋላ ግን 165 ሺህ ኪሎ ሜትር መድረሱን ተናግረዋል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ 60 ሜትር ስፋት ያለው 151 ኪሎ ሜት በአስፋልት ደረጃ መሰራቱን እና ከአስፋልት ውጭ ደግሞ 470 ኪሎ ሜትር መንገድ መሠራቱን ተናግረዋል፡፡

አትክልትና ፍራፍሬ ወደ ውጭ በመላክ ከ82 ነጥብ 5 ሚሊየን በላይ ዶላር እንዲሁም ከቡና በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ 1 ቢሊየን ዶላር ገቢ መገኘቱን አስረድተዋል፡፡

ከገበታ ለሀገር ጋር በተያያዘም÷ አራት አብያተ መጻሕፍት እየተገነቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አብርሆት ቤተ መጻሕፍት፣ የሳይንስ ሙዚየም፣ ፕላንት ቤተ መጻሕፍት እና የማዕድን ቤተ መጻሕፍት መሆናቸውንም ዘርዝረዋል፡፡

ይህም እኛ ያላገኘነውን ዕድል ልጆቻችን እንዲያገኙ ለማድረግ ያለመ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም ከሳይንስና ከዓለም ጋር ያላቸው ትውውቅ ይዳብራል ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዋጋ ውድነትን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ፥ ለኑሮ ውድነቱ በርካታ ምክንያቶች መኖራቸውን ጠቁመው÷ ችግሮቹን ለምፍታትም ብዙ ጥረት ተድርጓል ብለዋል፡፡

የኑሮ ውድነቱን የከፋ የሚያደርገውም መግዛት የማይችለውን ድሃውን የህብረተሰብ ክፍል ስለሚጎዳ ነው ብለዋል፡፡ የምርት እጥረት እና የፍላጎት ዕድገት፣ የንግድ ሥርዓት መዛባት፣ ምርቱ እያለ ማቅረቢያው ሎጅስቲክስ አለመኖር፣ ግጭት፣ መፈናቀል እንዲሁም የፋይናንስ አጠቃቀም በዋናነት እንደ ችግር የሚጠቀሱ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

በዓለም አቀፍ ደረጃም የኑሮ ውድነቱ ላይ ጫና ማሳደሩን ገልጸው÷ ቬንዙዌላ 1 ሺህ 198 ከመቶ፣ ሱዳን 340 ከመቶ፣ ሊባኖስ 201 ከመቶ፣ ሶሪያ 139 ከመቶ፣ አርጀንቲና 51 ከመቶ፣ ቱርክ 36 ከመቶ እንዲሁም በኢትዮጵያ 33 ከመቶ የዋጋ ግሽበት መኖሩን አብራርተዋል፡፡ ከሚቀጥለው ሀምሌ ወር ጀምሮ ለሕዝብ ትራንስፖርት መንግስት ድጎማ እንደሚያደርግም ነው ያስታወቁት፡፡

ዜናው የፋና ሪፖርት ነው

Exit mobile version