Site icon ETHIO12.COM

ቫለንት ፕሮጀክት – ኢትዮጵያን በመረጃ ጦርነት የወረረው ድርጅት

አሚል ካን የመሰረተው የመረጃ/ስነልቡና ጦርነት አዝማቹ Valent Projects የተባለ ድርጅት ስለራሱ ከሚገልፀው በተቃራኒው አሜሪካ እና ብሪታኒያ ላሰለጠኗቸው ብሎም በገንዘብ ለሚደግፏቸው የተለያዩ ታጣቂ ቡድኖች የፕሮፓጋንዳ ድጋፍ ሲያቀርብ ይታወቃል።


የዓባይልጅ

ኢትዮጵያ ላይ የደረሰውን የሀሰተኛ መረጃና የሰነልቦና ጦርነት የመራው ድርጅት በሶሪያው የርስ በርስ ጦርነት ተልእኮ በነበረው ሰው ነው የተቋቋመው። በሶሪያ የመረጃ ጦርነት አዝማች የነበረው ባስማ ፕሮጀክት መባሉን የምናውቀው ነው። በኢትዮጵያ የነበረውን ፕሮፓጋንዳ የመራው ልክ የባስማ አምሳያ ድርጅት መቋቋሙን እንጂ ስሙ ሳይገለጥ ነው የቆየው። ሆኖም በUSAID በኩል ከCIA የተሰጠውን ፀረ-ኢትዮጵያ ተልእኮ አስተግባሪ Valent Projects – ቫለንት ፕሮጀክትስ የሚባል ድርጅት መሆኑን በጥናታ ሪፖርቶች ይፋ ተደርጓል።
ይህ እኩይ ድርጅት ይጋለጥ ዘንድ የምእራባዊያን ጣልቃ ገብነትን የሚያነፈንፉ የተለያዩ ሀገራት ደህንነት መስሪያ ቤቶች የቴክኖሎጂ እና ምርምር ተቋማት ከእጃቸው ያስገቧቸው ሰነዶች ወሳኘ ግብአት በመሆን አገልግለዋል። ሰነዶቹ እየተፈተሹና እየተመረመሩ ቀጥለዋል። በተለይም ሚንት ፕሬስ ኢንስቲትዩት የተሰኘው የጥናት ማእከል በመሰል ስራዎቹ አንቱታን ያተረፈ ሲሆን ዛሬ ይፋ ባደረገው ጥናታዊ ሪፖርቱ የኢትዮጵያና ሱዳን ዜጎችን በዲጂታል የሚያሰሟቸው ድምፆችን ለማፈን በብሪታኒያ ማእከሉን ባደረገውና ቫለንት ፕሮጀክትስ በሚሉት ተቋራጭ በኩል ሲተገበር ይገኛል።
ከኢትዮጵያውያ በተጨማሪ የሱዳን ዜጎች በሀገራቸው ፖለቲካዊ ቀውስ ዙሪያ በኦንላይን የሚያሰሟቸውን ድምጾች ማፈን እንዲሁም የመረጃ ጦርነት ሰንሰለቱ ማዕከላዊ ዕዝ ከዚሁ ቫለንት ከተሰኘው ድርጅት መሆኑም ነው የተደረሰበት።
በአሜሪካው ሲአይኤ እና በእንግሊዝ ደህንነት ተቋም እንዲሁም በዩኤስአይዲ እና በተመሳሳይ አላማ ከተሰማሩ አጋሮች ጋር በመቀናጀት ነበር የፕሮፓጋንዳ ዘመቻው እየተከነወነ የሚገኘው።

ይህ ቫለንት ፕሮጄክትስ Valent Projects – በተለይም እንደ ፌስቡክ ካሉ የማህበራዊ ሚዲያ ኩባንያዎች ጋር በሚስጥር በመስራት ይታወቃል ይላል ሚንት ፕሬስ ኢንስቲቱዩት በጥናቱ። ቫለንት በአሜሪካ መንግስት የሚደገፉ የኦንላይን ፕሮፓጋንዳ ዘመቻዎችን በማማከር በየሚታወቅ ኮሙኒኬሽን ድርጅት ነው። ቫለንት በአንድ አጋጣሚ ብቻ የተደረገለትን ክፍያ ለአብነት የሚጠቅሰው የሚንት ፕሬሥ ፅሁፍ እንዳስቀመጠው “የሲአይኤ ተልእኮ አስተግባሪ የሆነው ዩኤስኤአይዲ “የሃሰተኛ መረጃ ካምፔይን እና ማስኬጃ በሚል 1.2 ሚሊዮን ዶላር ለቫለንት ፕሮጀክትስ ክፍያ ተፈፅሟል”። እነዚህ የስውር ተልእኮ ግንኙነቶች እስካሁን ይፋ አለመደረጋቸውን የጠቆመው ጥናታዊ ሪፖርቱ፣ ቫለንት ከተልእኮው አንፃር ያስቀመጠውን ድምዳሜ እና አቅጣጫ ተከትሎ ፌስቡክ ኩባንያ እጅግ በጣም በርካታ የሱዳን አካውንቶችን አግዷል። በተለይም ምዕራባዊያን በፕሮፓጋንዳና ዲፕሎማሲ የሚደግፉ በኃይል ስልጣን የተቆጣጠሩ መለዮ ለባሾችን የሚተቹ ገፆች የዲጂታል አፈናው ኢላማዎች ተደርገዋል። በዚህ አካሄዳቸውም በአልቡርሃን የተመራውን የጁንታ አስተዳደር ከነ አወዛጋቢነቱ ማስቀጠል ያለመ ዘመቻ ነበር።
በኢትዮጵያም በተመሳሳይ ከመንግስት የወገኑ ኢትዮጵያውያን የኦንላይን ድምጾች በጅምላ ማፈን ቫለንት ፕሮጀክትስ ከተሰጠው ተልእኮ መካከል ተጠቅሷል። በዚህም የአሜሪካን ጣልቃ-ገብ ፖሊሲ የሚቃወሙ ኢትዮጵያዊ የማህበራዊ ሚዲያ አካውንቶችን የማሳፈንና የማዘጋት ዘመቻ መክፈታቸው ነው ሚንት ፕሬሥ ኢንስቲትዩት በጥናታዊ ሪፖርቱ ያጋለጠው። በነገራችን ላይ ሚንት ፕሬሥ ኢንስቲትዩት ተራ የምእራባዊያን ተላላኪ ተቋም አይደለም። መሰረቱ በዚያው በአሜሪካ ይሁን አንጂ ተግባሩ ግን ፀረ ኢምፔሪያሊዝም ነው። የምእራባዊያን white helmet ገመና የገላለጠ፣ የበሺር አሳድ ኬሚካል ጥቃት ውንጀላ ትያትርን ከአደባባይ ያዋለ፤ በምእራባዊያን አይን አፍቃ ሩሲያ ብለው የሚፈርጁት፤ የክብር ሽልማቱን እነ ኒማ ኤልቢገር ከሚሸለሙበት የሿሿ ተቋም ሳይሆን እንደ ሴሬና ሺዋ ካሉ ተቋማት ነው ውድ ሽልማት የተበረከተለት…ወዘተ በርካታ ድንቅ ምርመራዎችን ያከናወነ ተቋም ነው – ሚንት ፕሬሥ።

ቫለንት ፕሮጄክትስ የተመሰረተው አሚል ካን በተባለ፤ ለቢቢሲ እና ሮይተርስ ይሰራ የነበረ አንጋፋ ጋዜጠኛ ሲሆን፤ ኋላ ላይ በብሪታንያው MI-6 የስለላ መስሪያ ቤት የመረጃ ጦርነት ክንፍ ባለሙያ ወደመሆን የተሸጋገረ ነው ይላል፤ ሚንት ፕሬሥ የሰውዬውን ዳራ በቃኘበት ዳሰሳው። የመረጃ ጦርነት Information warfare ባለሙያው አሚል ካን በሶሪያ ሚስጥራዊ የውጭ ጉዳይ ተልእኮ ፕሮጀክቶች ለበርካታ አመታት መስራቱንም ጥናቱ ገልጿል። በሶሪያ ተልእኮው የሀገር ውስጥ እንዲሁም ከሶሪያ ውጭ አለምአቀፍ ታዳሚዎች ላይ የተነጣጠረ ስውር የስነ-ልቦና ጦርነት Psychological operation – PSYOP ዘመቻዎች አካሂዷል። የ PSYOP [ስነልቦናዊ ጦርነት] ዘመቻውን ሲያስፈፅም የሚጠቀማቸው ገለልተኛ-መሰል ነገር ግን በሚስጥር ስውር ፖለቲካዊ ተልእኮ ያነገቡ ጋዜጠኞችና አክቲቪስቶችን ሲሆን የፕሮፓጋንዳ ብልጫውን ለመውሰድ መደበኛ ብዙሃን መገናኛዎች ጋር የሚቀናጁበትን ቅድመ ዝግጅት ትስስር እና ስልጠናዎች ተግባራዊ ያደርጋል።

አሚል ካን የመሰረተው የመረጃ/ስነልቡና ጦርነት አዝማቹ Valent Projects የተባለ ድርጅት ስለራሱ ከሚገልፀው በተቃራኒው አሜሪካ እና ብሪታኒያ ላሰለጠኗቸው ብሎም በገንዘብ ለሚደግፏቸው የተለያዩ ታጣቂ ቡድኖች የፕሮፓጋንዳ ድጋፍ ሲያቀርብ ይታወቃል።

#EslemanAbay #የዓባይልጅ

Exit mobile version