Site icon ETHIO12.COM

ሰርጌ ላቭሮቭ ለይፋ የስራ ጉብኝት ኢትዮጵያ ይገባሉ

የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ በመጪው ማክሰኞ ለይፋዊ የስራ ጉብኝት አዲስ አበባ አንደሚገቡና የሁለት ቀናት ቆይታ እንደሚኖራቸው ታውቋል።

በቆይታቸውም ከከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ ከአፍሪካ ህብረት ተወካዮች እና ከተለያዩ ሀገራት የዲፕሎማሲ ማህበረሰብ አባላት ጋር ውይይት እንደሚያደርጉ በአዲስ አበባ የሩሲያ ኤምባሲ ኣመልክቷል።

ላቭሮቭ ከአፍሪካ ሀገራት ዲፕሎማቶች ጋር በሚያደርጉት ውይይት በሩሲያ እና በአፍሪካ ሀገራት መካካል ያለውን ግንኙነት እና ትብብር ማጠናከር በሚቻልባቸው መንገዶች ዙሪያ ይመክራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ከዚህ ባለፈም በሁለተኛው የአፍሪካ-ሩሲያ ጉባኤ ዝግጅት ዙሪያ እንደሚመክሩም ከኤምባሲው ኡየተገኘው መረጃ ያመልክታል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ሞስኮን እንዲጎበኙ በሩሲያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ ግብዣ አንደ ቀረበላቸው አል-ዐይን ሲዘግብ ከሩሲያ-አፍሪካ የትብብር ጉባኤ ዋና ጸሐፊ ሚስተር ኦሌግ ጋር መወያየታቸውን ኣመልክቶ ነበር።

መሪዎቹ የተወያዩት በቀጣይ ዓመት በአፍሪካ ሊካሄድ ስለታሰበው ሁለተኛው የሩሲያ-አፍሪካ ጉባኤ ዙሪያ ሲሆን ኢትዮጵያ ጉባኤውን ለማዘጋጀት ዝግጁ መሆኗን ኣስታውቃ አንደነበር ይታወሳል።

መሪዎቹ ሁለቱ አገራት በቴክኖሎጂ ፣ በጸጥታ እና ደህንነት ፣ በግብርና ፣ በኑክሌር ቴክኖሎጂ እና ህክምና ዘርፎች ላይ በጋራ መስራት በሚችሉባቸው አጀንዳዎች ዙሪያ መወያየታቸው በወቅቱ መክረው ነበር።

የመጀመሪያው የአፍሪካ-ሩሲያ ጉባኤ ባሳለፍነው ዓመት በሩሲያ ሱቺ ከተማ የተካሄደ ሲሆን በዚህ ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ መገኘታቸው እና ከሩሲያ ፕሬዘዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር በሁለትዮሽ እና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ዙሪያ መወያየታቸው አይዘነጋም።

Exit mobile version