Site icon ETHIO12.COM

“በሆሮ ጉድሩ ህዝብ ጀብዱ ፈጸመ”

በሆሩ ጉዱሩ ወለጋ ዞን የጉደኔ ጫላ ሲበሬ ቀበሌ ነዋሪዎች በአሸባሪው ሸኔ ላይ ዘመቻ በመክፈት ጀብዱ ፈፀሙ። ነገሩ እንዲህ ነው። በኦሮሚያ ክልል በሆሩ ጉድሩ ወለጋ ዞን ጮማን ጉዱሩ ወረዳ ውስጥ ካሉት ቀበሌዎች መካከል በአንዲት ቀበሌ ውስጥ ታላቅ ጀብዱ ተፈፅሟል። ቀበሌዋ ጉደኔ ጫላ ሲበሬ ትባላለች። እንደወትሮው ሁሉ ህዝቡ ውስጥ ለመደበቅ የአሸባሪው ሸኔ ታጣቂዎች ወደዚህች ቀበሌ ዘልቀው ይገባሉ።

ነገር ግን የጉደኔ ጫላ ሲበሬ ቀበሌ አሁን በቃችሁን በማለት 07 ወጣቶች ከታጠቁት ሸኔ ታጣቂዎች ጋር በጦርና በገጀራ ጦርነት ገጠሙ። ከ7ቱ ሶስቱ የዩኒቨሪሲቲ ተማሪዎች ሲሆኑ አራቱ ደግሞ አርሶ ከደር ናቸው። ጩሃቱን የሰማው የቀበሌው ህዝብ በሙሉ በነቂስ ወጥቶ ከታጠቁት ሸኔዎች ጋር በባህላዊ ጦርና ገጀራ ገጠሙ።

ይህንኑ ያላሰቡትን የህዝብ ማዕበልና ቁጣ አይተው የተደናበሩት አሸባሪዎች እግር አውጪኝ ብለው እግራቸው ወደመራቸው አቅጣጫ መሸሽን መረጡ። ነገር ግን የህዝብ ማዕበሉ አንዱን በጦር በመግደል ሶስቱን ደግሞ ከእነትጥቃቸው ማርኮ ለወረዳው አስተዳደርና በአከባቢው ለተሰማራው ለመከላከያ ሰራዊታችን አስረክበዋል።

ይህንን ጀብዱ የሰሙ አጎራባች የወረዳው ቀበሌዎች በሙሉ በጋራ አደባባይ ወጥተው ለጀግናዋ ቀበሌ ህዝብ የጀግኖች አቀባበል አደረጉ።

በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ ጀብዱ ለፈፀሙት አባላትና ለቀበሌዋ ህዝብ ዕውቅና ተሠጠ። የዞን አመራሮችንና በአከባቢው የተሰማራውን የመከላከያ ሰራዊት አመራሮችም ተጋበዙ። ከታጠቁት ታጣቂዎች ጋር ገጥመው ሞትና ሞርኮ ላደረጉ የቀበሌው አባላት ሠንጋዎች ቀረላቸው።

በዝግጅቱ ላይ በመገኘት ለጀግኖቹ የዕውቅና ሽልማት በመስጠት ንግግር ያደረጉት የሆሩ ጉድሩ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ምሬሳ ፊጣ የሸኔ የሚደበቅበትን የማሳጣት ዘመቻ ማብቃቱን አብስረዋል። ከእንግዲህ ሆሩ ጉድሩ ዞን የሰላምና የልማት ዘመቻ እንጂ በቀመኞቹና ዘራፊዎች የመበደል ጊዜ አብቅተዋል። ማብቃቱን ደግሞ የጉደኔ ጫላ ሲበሬ ቀበሌ ህዝቦች በህዝባዊ ማዕበል ጀብዱ በመፈፀም በተግባር አሳይተችሁናልና የጀግንነታችሁ ችቦ ደግሞ በመላው ዞናችን ይቀጣጠላል ብለዋል።

ጀብዱ ለፈፀሙት ለዩኒቨርስቲው 3 ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው ሶስት ሶስት ሺህ የተበረከተላቸው ሲሆን ለቀሩት ለአራት አርሶ አደሮች ደግሞ ለእያንዳንዳቸው ጠመንጃና ሰርትፍኬት ተሸልመዋል።

በፕሮግራሙ ላይ የተገኙት በአከባቢው የተሰማራው ክፍለጦር ምክትል አዛዥ ደግሞ ከህዝባችን ጋር የጀመርነውን የአሸባሪው ሸኔን የማፅዳት ዘመቻ አጠናክረን በመቀጠል ዞኑንና መላውን ኦሮሚያን የሰላምና የልማት ቀጠና እናደርጋለን አትጠራጠሩ ብለዋል።

በሆሩ ጉዱሩ ወለጋ ዞን በአሁኑ ወቅት የክልሉ ልዩ ሃይል ፤ ህዝባዊ ፖሊስና ሚልሻ ፤ የፌደራል ፖሊስ አባለት በሙሉ በመከላከያ ኮማድ ፖስት ስር ሆኖ ዞኑን ከአሻባሪው ሸኔ በማፅዳት ላይ ይገኛሉ።

ታሪኩ ሻሜቦ

ፎቶግራፍ የሆሩ ጉድሩ ዞን መንግስት ኮሙኒኬሽን

Exit mobile version