Site icon ETHIO12.COM

ደቡብ አፍሪካ የሚካሄደው የሰላም አማራጭ ንግግር ቀን ተቆረጠ

በአፍሪካ ሕብረት መሪነት የሚካሄደው የሰላም አማራጭ በመጪው ሰኞ ጥቅምት 14 በደቡብ አፍሪካ እንደሚካሄድ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ሚኒስትር አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ገለጹ። ነጻ በወጡ አካባቢዎች ሰብዓዊ እርዳታ በተሣለጠ መንገድ እንዲደርስ በቂ ዝግጅት መደረጉም ይፋ ሆኗል።

የአፍሪካ ህብረት የሰላም ንግግሩ የፊታችን ሰኞ ጥቅምት አስራ አራት በደቡብ አፍሪካ እንደሚካሄድ ማሳወቁን አቶ ሬድዋን አረጋግጠዋል።አክለውም የኢትዮጵያ መንግሥት በአፍሪካ ህብረት በኩል ለሚካሄደው የሰላም ንግግር ላይ ለመሳተፍ ያለውን ዝግጁነት በድጋሚ ማረጋገጡን አምልክተዋል። ሆኖም አሁንም መንግስት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስከበር የሚወስደውን የመከላከል ርምጃ ለማጠልሸት፤ የሃሰት ክስን ለመሰንዘርና የሰላም ሂደቱን ለማደናቀፍ በሚጥሩ አካላት ላይ ያለውን ቅሬታ ቅሬታም ይፋ አድርገዋል።

በተለይ በትግራይ፣ እንዲሁም በአማራና አፋር ክልሎች፣ በሌላም በኩል በውክልና በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች እየተካሄደ ካለው ቀውስና ችግር አንጻር ካለው ሰብአዊ ቀውስ የሰላም አማራጭ መፈለጉ በመላው ኢትዮጵያዊያን ዘንዳ የሚጠበቅ መልካም ዜና ነው።

ይህ በንዲህ እንዳለ

በትግራይ ክልል ከአሸባሪው ህወሃት ቡድን ነጻ በወጡ አካባቢዎች ሰብዓዊ እርዳታ በተሣለጠ መንገድ እንዲደርስ በቂ ዝግጅት መደረጉን ለሰብዓዊ ድጋፍ የተዋቀረው ኮሚቴ አስታወቀ።

ሰብዓዊ እርዳታን በተቀናጀ፣ በተፋጠነ እና በተሣለጠ መልኩ ማድረስ የመንግስት ፅኑ አቋም መሆኑም ተገልጿል።

ከአሸባሪው ቡድን ነጻ በወጡ አካባቢዎች ሰብዓዊ እርዳታ በተሣለጠ መንገድ እንዲደርስ ባለድርሻ አካላት በቂ ዝግጅት ማድረጋቸውን ለሰብዓዊ ድጋፍ የተዋቀረው ኮሚቴ ገለፀ።

የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦትን ለማሳለጥ ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት፣ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት፣ ከሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ እና የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚቴ ተዋቅሮ ወደ ስራ ገብቷል።

የኮሚቴው ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን፤ መከላከያ ሰራዊት በተቆጣጠራቸው አካባቢዎች ሰብዓዊ እርዳታውን በተሣለጠ መልኩ ለማድረስ መንግስት ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱንና ወደ ተግባር መግባቱን ገልፀዋል።

ኮሚቴው ዝግጅቱን አስመልክቶ ባደረገው ውይይት ከአሸባሪው ነጻ በወጡ የትግራይ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ሰብዓዊ እርዳታ እንዲደርስ ባለድርሻ አካላት በቂ ዝግጅት ማድረጋቸውንም አረጋግጧል።

የሽሬ አውሮፕላን ማረፊያን ተጠቅሞ ዕርዳታ ማድረስን እንደሚጨምር የጠቅላይ ሚኒስትሩ የብሄራዊ ደህንነት አማካሪ ሚኒስትርና የኮሚቴው ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ተናግረዋል።

ሰብዓዊ እርዳታን በተቀናጀ፣ በተፋጠነና በተሣለጠ መንገድ ማድረስ የመንግስት ፅኑ አቋም እንደሆነም ገልፀዋል።

ለዚህም ኮሚቴው በአጭርና በመካከለኛ ጊዜ የሚከናወኑ ተግባራትን ለይቶ በቅንጅት እንደሚሰራ ተናግረዋል።

ነጻ በወጡ አካባቢዎች የመንግስት መዋቅሩን መልሶ በማደራጀት የተቀናጀ የሰብዓዊ እርዳታ ተደራሽ እንዲሆን ይሰራል ብለዋል።

መንግስት ያስቀመጠው አቅጣጫ ተገቢና ትክክለኛ መሆኑን ያመለከቱት የኮሚቴው አባላት፣ ውሳኔውን ለመተግበር በየዘርፉ የሚመለከታቸው አካላት በቂ ዝግጅት ማድረጋቸውንም አስረድተዋል።

በዚህም ከአሸባሪው ህወሓት ነፃ በወጡ አካባቢዎች የእርዳታ አቅርቦቱ ሳይስተጓጎል ማድረስ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ በቅንጅት እንደሚሰሩም ተናግረዋል።

መንግሥት ከሰብአዊ የእርዳታ ተቋማት ጋር በመቀናጀት ሰብአዊ ዕርዳታ የሚደርስባቸውን መንገዶች እያስፋፋ መሆኑን የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በትላንትናው እለት መግለፁ ይታወቃል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።

Exit mobile version