Site icon ETHIO12.COM

“ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ሊመሰገኑ ይገባቸዋል” ዶ.ር ደብረፅዮን

የፌደራሉ መንግስትም የተጀመረውን የሰላም ጉዞ ለማስቀጠል እየሰራ ላለው ስራ እና እየፈፀማቸው ላሉ ሀላፊነቶች ምስጋና ይገባዋል ያሉት ዶ/ር ደብረፅዮን፤ በተለይም የሰላሙን ጉዳይ ከፊት ሆነው እያስተባበሩ እና እየመሩ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ሊመሰገኑ ይገባቸዋል

የሰላም ስምምነቱን ሙሉ ለሙሉ ለመተግበር ቁርጠኞች ነን


የፌደራል መንግስት ልኡካን ቡድን ከፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት በኋላ ያለ 3ኛ ወገን አደራዳሪ ለመጀመርያ ጊዜ ከህወሀት አመራሮች ጋር በመቐለ የገፅ ለገፅ ውይይት አካሂደዋል።

በውይይቱ የህወሀት ሊቀመንበር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ይህ ሰላም እንዲመጣ እና አሁን ላለንበት ደረጃ እንድንደርስ ላደረጉ አካላት ምስጋና ይገባል ብለዋል።

የፌደራሉ መንግስትም የተጀመረውን የሰላም ጉዞ ለማስቀጠል እየሰራ ላለው ስራ እና እየፈፀማቸው ላሉ ሀላፊነቶች ምስጋና ይገባዋል ያሉት ዶ/ር ደብረፅዮን፤ በተለይም የሰላሙን ጉዳይ ከፊት ሆነው እያስተባበሩ እና እየመሩ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ሊመሰገኑ ይገባቸዋል ብለዋል።

በጦርነቱ ምክንያት የትግራይ ህዝብ ለከፍተኛ ችግር ተጋልጧል ያሉት ዶክተር ደብረፅዮን፤ የሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦትና የመሰረታዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በፍጥነት በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች እንዲጀመር ጠይቀዋል።

የስልክ፣ የባንክና የኃይል አቅርቦት ስራዎች ደግሞ በፍጥነት ሊሰሩ እንደሚገባ ጠቁመዋል።

በፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት የተቀመጡ ሁሉም ነጥቦች ሊተገበሩ ይገባቸዋል ያሉት የህወሓት ሊቀመንበር፤ በትግራይ በኩል ስምምነቱን ሙሉ ለሙሉ ለመተግበር እንሰራለን ብለዋል።

ለዚህም ታጣቂዎችን ከግንባር ማስወጣትና ከባድ የጦር መሳሪያዎችን በአንድ ማእከል ማሰባሰብ ጀምረናል ብለዋል።

በመንግስት በኩልም ሁሉም የስምምነት ነጥቦች ይሰራባቸዋል ብለን እንጠብቃለን ብለዋል።

የዛሬው ግንኙነት ታሪካዊ ነው ያሉት ዶክተር ደብረ ፅዮን፤ ይህንን ግንኙነት ልናጠናክርና 3ኛ ወገኖችን አስወጥተን ችግሮቻችንን በራሳችን ልንፈታ ይገባናል ሲሉ ተናግረዋል።

Via ethio fm 107.8

Exit mobile version