Site icon ETHIO12.COM

አሁን በመተከል የስጋት ጩኽቶች ጠፍተዋል- ክብር ለሀገር መከላከያ ሰራዊት

መተከል በፈጣሪ ቸርነት በተፈጥሮ ሃብት የበለፀገ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚበቃ ሁሉንም የሚያጠግብ ለም ምድር ቢሆንም በተሳሳተ ትርክት ውስጥ ወጣቱን በማስገባት በልማት እና በእድገት ፈንታ ከድህነት እንዳይላቀቅ በማድረግ ስቃይና መከራ በዝቶበት ኖሯል።

ጊዜ ደጉ እንደ ነፋስ ሽውታ እንደ ሰማይ ደመና እየተገለባበጠ አመታቶች በወራት፣ ወራቶች በሳምንታት፣ ሳምንታት በቀናት፣ ቀናት__በሰዓታት እየተፈራሪቁ አሁን ወቅት ደርሰናል።

አሁን በመተከል የስጋት ጩኽቶች ጠፍተዋል። የተፈናቀሉ ዜጎች ወደ ቀያቸው ተመልሰዋል። የተጣሉ ታርቀዋል የተለያዩ ተገናኝተዋል የተራራቁ ተቀራርበዋል። መጠራጠር እና ፍርሃት የለም። የጥላቻ ልዩነት ተወግዶ ዘላቂ አንድነት እና አብሮነት ተገንብቷል። በአጠቃላይ በመተከል እነኛ ፍርሃት እና ስጋት የሚፈራረቅባቸዉ ሁኔታዎች ታልፈዋል። ክብር ለመከላከያ ሰራዊታችን ይሁንእና፡፡

ከድጥ ወደማጡ የነበረውን የመተከል የፀጥታ ችግር በሰከነ መንገድ በማጥናት እና በመከታተል የኢትዮጵያ ህዝቦች የሰላም ምሰሶ የሆነው ሰራዊታችን በቀጠናው ጉልበቱን አካሉን እና ህይወቱን ሳይሰስት በመስጠት ለዛሬዋ የመተከል ሰላም ገፀ በረከት ሁኗል። ጀግናው ሰራዊታችን ከሌሎች የፀጥታ ሃይሎች ጋር ተቀናጅቶ እና ተናቦ አስተማማኝ የግዳጅ ስምሪት በማድረግ ታሪክ የማይረሳው ዋጋ ከፍሎበታል።

ሰራዊታችን በመተከል ዞን የተሳለጠ ስምሪት በማድረግ የፀረ ሰላም ሃይሎችን የጥፋት እርምጃ እየተከታተለ በማክሸፍ ህብረተሰቡን በመሰብሰብ በማወያየት በማደራጀት ወደ ቦታው እንዲመለስ ያለ መታከት ሌትም ቀንም ውድ ህይወቱን እየገበረ በፅኑ የአገር ፍቅር ስሜት በመስራት የኢትዮጵያ ህዝብ የማይረሳው አንፃራዊ ሰላም ማምጣት ችሏል።

መተከል የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ መተላለፊያ ኮሊደር ነው። ለዚህም ነው ቀጠናው የአገራችን የውስጥ ቅጥረኛ ባንዳዎች እና የውጭ ታሪካዊ ጠላቶቻችን ዋና የትኩረት አቅጣጫ የሆነው። በፀጥታ ሃይሉ የአመራር ጥበብ በሰራዊቱ ድል አድራጊነት በመተከል ህዝብ አስተዋይነት አሁን የተገኘውን ሰላም በማይደበዝዝ መስዋዕትነት ማምጣት ተችሏል።

ሰላም የሁሉም መሠረት እና ገዥ ሃሳብ ነው። የአለፈውን በይቅርታ የወደፊቱን በአብሮነት ለመኖር በአካባቢው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ በርካታ የጥፋት ሃይሎች እጃቸውን ለጀግናው ሰራዊታችን በሰላም እየሰጡ ወደ ቀያቸው መመለስ ጀምረዋል። ይህ ደግሞ የሰላም አማራጭ አቅጣጫውን በመከተል የፀጥታ ሃይሉ እና የፖለቲካ አመራሩ የሚሰራው ውጤታማ ተግባር ነዉ ማለትም ይቻላል።

ሁሉም ኢትዮጵያዊ መተከልን ሲያስብ ቀድሞ የህዳሴው ብርሃን ላይ ያርፋል። በመተከል ሰማይ በጉባ ተራሮች ግርጌ ስር ተስፋ የሚያላብስ ድህነትን የሚያሰንቅ የዘመናት ኋላቀርነታችን የሚያድስ አንድነት እና አብሮነትን መደጋገፍ እና መተባበርን የሚሻ የኢትዮጵያውያን ህዝቦችና ብሔር ብሔረሰቦች የቃል ኪዳን ሰነድ ያረፈበት ታላቁ ኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ህዳሴ ግድብ ይገኛል።

የግድቡ የግንባታ ሂደት ያለ አንዳች መስተጓጎል እየተከናወነ እንዲቀጥል በማድረጉ ረገድ ጀግናው ሰራዊታችን የአካባቢውን ተፈጥሮአዊ ሁኔታ ተቋቁሞ አገራዊ አላፊነቱን በፍቅር እየተወጣ በስኬት እየተሻገረ አሁን እስካለበት ደረጃ ደርሷል።

ቀጠናው ከውስጥ ፀረ ሰላም ሃይሎች እስከ ውጭ ታሪካዊ ጠላቶቻችን ድረስ ጣልቃ ገብነት የሚዘወርበት መሆኑን በመገንዘብ ጀግናው ሰራዊታችን ሃያ አራት ሳዓት ሙሉ በሰማይ እና በምድር የቅኝት ምልከታዎችን እና የአሰሳ ስምሪት በማድረግ የግድቡን ሉዓላዊነት በጀግንነት አስከብሮ ይገኛል።ህዳሴዉ ሲያዪት የማይጠገብ አይተው የማይጨርሱት ታሪካዊ ፕሮጀክት ነው።ህዳሴዉ ለኢትዮጵያውያን ሲሳይ ነው።

ሰራዊታችን በማይናወጥ የዓላማ ፅናቱ በማይቀዘቅዝ የሞራል ግለቱ የቀጠናውን ዘላቂ ሰላም እያረጋገጠ የግንባታው ግባዓቶች ያለ አንዳች መቆራረጥ በፍጥነት ገብተው ጥቅም ላይ እንዲውሉ በማድረግ የህዳሴውን የብርሃን መባቻ በማፋጠን ላይ ይገኛል።

የህዳሴው የግንባታ ፕሮጀክት እየተከናወነ መብራት ሆኖ በርቷል።አሳ አፍርቶ ምግብ ሰጥቷል። አትክልት አሳድጎ ፍሬ ችሯል። ህዳሴዉ ከእንግዲህ ወዲሁ ለኢትዮጵያውያን የልማት ገፀ በረከቱን በተግባር ጀምሯል። ቃል በተግባር ማለትይሄ ነው።

ክብር ለሀገር ሰላም እና ልማት ዕዉን መሆን በፅናት ለቆመዉ መከላከያ ሰራዊታችን

በላይነህ ፈንቴ – የኢፌዴሪ መከላከያ ጥር 30 ቀን 2015 ዓ.ም

Exit mobile version