Site icon ETHIO12.COM

“የኦሮሞ ህዝብም ሆነ ክልሉ ትግስታቸው አልቋል” ሲል ህጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ ኦሮሚያ አስታወቀ

“ቆሞ ቀሮች” ይላል የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት መግለጫ። ሁሉም ጉዳይ በውይይት እንዲቋጭ ፍላጎቱን ገገለጸ በሁዋላ። የኦሮሞ ህዝብም ሆነ የክልሉ መንግስት መሰላቸቱንና ትዕግስታቸው እንዳለቀ ያስታወቀው አክርሮ ነው። በከፍተኛ ደረጃ በሆደ ሰፊነት በርካታ ጉዳዮችን ማለፉን ዘርዝሯል።

“በኦሮም ህዝብ ላይ በርካታ የጥላቻና የማጥላላት ዘመቻ ሲያጎርፉ ለሀገረ መንግስቱ አንድነት መፅናት ሲባል በሆደሰፊነት ያለፍን ሲሆን ከዚህ ቦኋላ ህዝባችንም ሆነ የክልሉ መንግስት ትግስቱ ያለቀ በመሆኑ የፌዴራል መንግስት ህገ መንግስታዊ ሥርዓቱን ለማስከበር የፌደራል የፀጥታና ድህንነት የጋራ ግብረ ሃይል ያወጣውን መግለጫ በመደገፍ ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለመታደግ አስፈላጊውን ህጋዊ እርምጃ የምንወስድ መሆኑን እንገልፃለን” ሲል መግለጫውን ያጠቃለለው መግለጫው፣ “የክልላችን ሰላምና ደህንነት ለማናጋት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን በማጋለጥ ህብረተሰቡ የበኩል ሚና እንዲጫወት” ሲል ጥሪ አቅርቧል።

” አኩልነትን እንደ በደል የሚያዪ ጥቂት ቆሞ ቀሮች የኢትዮጵያን የሀገረ መንግስት ግንባታ ታራካዊ ዳራን ያላገናዘቡ አሮጌ ትርክቶችን በማፀባረቅ ዛሬም እንደ ትላንቱ እኔ ካልወሰንኩልህ በማለት ለራሳቸዉ የሰፉትን ጥብቆ ሁሉንም ለማልበስ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ። እነዚህ ሃይሎች በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋህዶ የዕምነት አባቶች መካከል የተፈጠረውን ክፍፍል ሽፋን በማድረግ እኩይ የፖለቲካ አላማቸውን ለማስፈፀም በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡ የሃይማኖት ጭምብል ለብሰው የሚንቀሳቀሱ የድሮ ስርዓት ናፋቂ ቡድኖች ህገ መንግስታዊ ሥረዓትን በሚፃረር መልኩ ሰፊዉን ሕዝብ በተለይም ደግሞ የኦሮሞ ህዝብን ላይ ከፍተኛ የጥላቻ ዘመቻ በማድረግ ላይ ይገኛሉ”

ዘመናትን ባስቆጠረዉ የኢትዮጵያ ሀገረ መንግሰት ግንባታ ሂደት በርካታ የምንኮራባቸዉን የአብሮነት፣ የጀግንነት፣ ለጋራ ሀገራዊ ህልውና እና ሉአለዊነት አብሮ መቆምን፣ አብሮ መዋደቅን በተግባር ያሳየንበትን እሴት ገንብተናል። እነዚህ በጎ ገፅታዎች እስካሁንም በሰፊዉ ሕዝብ ዘንድ የዕለት ተዕለት ሕይወት አካል ሆኖ እናገኘዋለን። በተቃራኒዉ ብዘሀነትን በአግባቡ አለማስተናገድ፣ ኢትዮጵያ ህብር የብዘሃ ማንነት ባለቤት መሆንዋን የዘነጉ አስተዳደራዊ ሥረዓቶችና ትርክቶች መዘዛቸው እስከ ዛሬም ዋልታ ረገጥ ፅንፈኝነትን ወልደው ብሔራዊ ፈተና ሆነዉ ይታያሉ። እነኚህ ትርክቶችና አስተዳዳራዊ በደሎች የእኩልነት፣ ነፃነትና የፍትሃዊ ተጠቃሚነት ጥያቄዎችን ከመጫር አልፈው ከፍተኛ ለሆነ የዕርስ በርስ ጦርነት ዳርገውን አላስፈላጊ መሠዋትነትንም ከፍለንበታል።

ዛሬ እየተመራንበት ያለነዉ ህገመንግስታዊ ህብረብሔራዊ ፌዴራላዊ ሥረዓት ለዘመናት መልስ አልባ ሆነዉ ለእርስ በርስ ጦርነት የዳረጉንን የማንንነት፣ እራስን በራስ የማስተዳደር የሀይማኖት እኩልነት ወዘተ ጥያቄዎችን ህጋዊ እና ህገ መንግስታዊ መሠረት ባለዉ መልኩ ምላሽ ሰቷል።

ምንም እንኳ በፌዴራለዊ ሥረዓታችን ውስጥ የአተገባበር ችግሮች በተለይም ደግም በሀገራዊ እና በብሔር ማንነት መካከል ሚዛን ያለመጠበቅ፣ ጣልቃ ገብነት፣ እዉነተኛ ዴሞክራሲ እና ከተቋማት ግንባታ ጋር ክፍተቶች ቢኖሩም የኢትዮጲያ ብሔር ብሔረሰብችና ሕዝቦች እራስን በራስ የማሰተዳደር መብት እስከመገንጠል በቋንቋቻው የመጠቀም የመማር በቋንቋቸው የመዳኘት ባህልና ማንነታቸውን የማሳደግ የማበልፀግ እና የሐይማኖት እኩልነት መብታቸውን ተጎናፀፈዋል። እነኚህ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ወደ ኋላ ላይመለሱ ተከባብረውና ተቻችለዉ አንድ የፖለቲካና ኢኮኖሚ ማህበረሰብ ለመገንባት ቃል ኪዳናቸውን ባፀኑበት ህገ መንግስት ዋስትና አግኝቷል።

ባለፉት አራት እና አምስት አመታት ደግሞ በፌዴሬሽኑ አተገባበር ሲስተዋሉ የነበሩ የአፈፃፀም ችግሮች በሪፎርም ምላሽ አግኝተዋል። በተለይም አለመግባባትና ሐገራዊ እንድነትን የሚገዳደሩ ዋልታ ረገጥ አስተሳሰቦችን ለማረቅ ከፍተኛ ጥረት የተደረገ ሲሆን ያለፈውን በይቅርታ ዘግተን ለመጪው የጋራ ብልፅግናችን እንደመር በሚል አዲስ ሀገር በቀል አስተሳሰብ በጀመርነዉ እርምጃ እምርታን ማሳየት ችለናል።

በተለይም ለዘመናት የቆዩ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ስብራቶችን ለመጠገን ዘርፈ ብዙ ለውጦች በማድረግ ላይ እንገኛለን፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት መንግስት ማህበራዊ ስብራቶቻችን ለመጠገን የሚረዱ ተቋማትን ህገ-መንግስታዊ መርሆዎችን በጠበቀና በተከተለ መልኩ ለሃይማኖት ተቋማት አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ ብቻ ሳይሆን ለብዙ ዓመታት ተለያይተው የቆዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሲኖዶሶችን በማስታረቅ፤ ፍትሃዊ የህዝበ ሙስሊሙን ጥያቄዎች በመመለስ የበኩሉን አውንታዊ ሚና ተጫውቷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የመሬት አቅርቦት በማድረግ ለዘመናት የቆየ የዕምነት ተቋማት ጥያቄን መልሷል፤ በመመለስ ላይም ይገኛል፡፡ ይህ መንግስታዊ ግዴታችን መሆኑን በቅጡ ተረድተን ያደረግነው ስለሆን እንኮራበታለን አጠናክረንም እንቀጥላለን፡፡

ይህ ሆኖ ሳለ አኩልነትን እንደ በደል የሚያዪ ጥቂት ቆሞ ቀሮች የኢትዮጵያን የሀገረ መንግስት ግንባታ ታሪካዊ ዳራን ያላገናዘቡ አሮጌ ትርክቶችን በማፀባረቅ ዛሬም እንደ ትላንቱ እኔ ካልወሰንኩልህ በማለት ለራሳቸዉ የሰፉትን ጥብቆ ሁሉንም ለማልበስ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ። እነዚህ ሃይሎች በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋህዶ የዕምነት አባቶች መካከል የተፈጠረውን ክፍፍል ሽፋን በማድረግ እኩይ የፖለቲካ አላማቸውን ለማስፈፀም በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡ የሃይማኖት ጭምብል ለብሰው የሚንቀሳቀሱ የድሮ ስርዓት ናፋቂ ቡድኖች ህገ መንግስታዊ ሥረዓትን በሚፃረር መልኩ ሰፊዉን ሕዝብ በተለይም ደግሞ የኦሮሞ ህዝብን ላይ ከፍተኛ የጥላቻ ዘመቻ በማድረግ ላይ ይገኛሉ።

እነዚህ ቡድኖች በክልሉ መንግስት በአመራሩና በኦሮም ህዝብ ላይ በርካታ የጥላቻና የማጥላላት ዘመቻ ሲያጎርፉ ለሀገረ መንግስቱ አንድነት መፅናት ሲባል በሆደሰፊነት ያለፍን ሲሆን ከዚህ ቦኋላ ህዝባችንም ሆነ የክልሉ መንግስት ትግስቱ ያለቀ በመሆኑ የፌዴራል መንግስት ህገ መንግስታዊ ሥርዓቱን ለማስከበር የፌደራል የፀጥታና ድህንነት የጋራ ግብረ ሃይል ያወጣውን መግለጫ በመደገፍ ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለመታደግ አስፈላጊውን ህጋዊ እርምጃ የምንወስድ መሆኑን እንገልፃለን፡፡ ስለሆነም የክልላችን ሰላምና ደህንነት ለማናጋት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን በማጋለጥ ህብረተሰቡ የበኩል ሚና እንዲጫወት ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት

የካቲት 3/205

ፊንፊኔ

Exit mobile version