Site icon ETHIO12.COM

የጌታቸው ረዳ ሹመት ጉድ አፈላ? ሚዲያዎች፣ አተራማሽ ግለሰቦችና ድርጅቶች ተደናግጠዋል

ከአደዋ አክሱም ወደ ራያ የዞረው የትግራይ አስተዳደር አዲስ መሪና አዲስ ከመሪው ጀርባ የሚያጦዝ ስብሃት ነጋን አግኝቷል። አዲሱ የስብሃት ነጋ ምትክ ጄነራል ጻድቃን ሲሆኑ፣ የትግራይ ቲቪ ይፋ እንዳደረገው የትግራይ መሪ የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ ናቸው። ሁለቱም ከራያ!!

አብይ አህመድን መንደብና እሳቸው ላይ ያነጣጠረ ዘመቻ ሲመሩ የነበሩት አቶ ጌታቸው ናቸው። ዩቲዩብ፣ ማህበራዊ ገጾች፣ አክቲቪስቶች በብሄር ስም ጠብ መንጃ ያነሱ፣ የደቡብ ክልል ውዝግብ፣ የሶማሌ ክልል ላይ የተጀመረው ዘመቻ … ሁሉም በተለይ አሁን አሁን አማራ ክልል ላይ ያለው ጽንፈኛና እንቅስቃሴ የሚመሩ በውጭና በአገር ውስጥ ያሉ ድርጅቶችና ግለሰቦች ግንኙነታቸው ከጊታቸው ረዳ ጋር ከመሆኑ አንጻር የአሳቸው ሹመት ይዞት የሚመጣው የአቋም ለውጥና መክሰም በጉጉት የሚጠበቅ ነው

በይፋ በሚታዩ መረጃዎች ጌታቸው ረዳ በትግራይ ታጋይ ሳይሆኑ ትግራይን የመሩ ብቸኛ ካድሬ ሆነው ይመዘገባሉ። ጌታቸው ረዳ ሌላ የሚያስመዘግቡት ሪኮርድ ደግሞ በጥላቻና “እረኛውን ምታ በጎቹ ይበተናሉ” መርህ የተፈለፈሉ ሚዲያዎች፣ አክቲቪስቶች፣ በአማራና ኦሮሚያ ክልል የብሄራቸው ተቆርቋሪ መስለው ሲንቀሳቀሱና ጥላቻን ሲያሰራጩ የነበሩ ሁሉ በርሳቸው ስር ስለነበሩ ቆጣሪያቸው ይነቀላል።

ሃይለማሪያም ጥበቡ ጌታቸው ረዳ የትግራይ መሪ እንደሚሆኑ ከተሰማ በሁዋላ የጥላቻውና የሁከቱ ስርጭት መቀነሱን ይናገራሉ። ስማቸው እንዳጠቀስ የጠየቁ አንድ የሰሜን አሜሪካ ነዋሪ አስቀድመው ” ሃብታሙና ሌሎቹን ኮተቶች ተዋቸው ይላሉ” ምክንያቱም እንደ በርሜል ተራ ጩኸት ይመስሏቸውና ” ባዶዎች ናቸው” ይላሉ። አክለው “ኤርሚያስ ሰግቷል” በማለት ከጌታቸው ረዳ ጋር ጥብቅ ግንኙነት እንዳለው ይገልጻሉ። እሱ ብቻ ሳይሆን ” ቴዎድሮስ ጸጋዬ፣ ጃዋር መሀመድ፣ ጃል መሮ፣ አድፋጩ ኦነግና አማራ ክልል ሴራ የሚያመርቱት ሁሉም በጌታቸው ስር ናቸው” በማለት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይን ማድነቅ አለመቻል ተራ ምቀኝነት እንደሆነ ያሰምሩበታል።

ከትህነግ ቅርብ ሰዎች እንደተሰማው ከሆነ ቀደም ሲል የእነ ዶክተር ደብረጽዮን ቡድን ለጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ የሹመት ዝርዝር አቅርበው ነበር። ይህን ዝርዝር ለሪፖርተር ቅርበት ያላቸው የእነ ደብረጽዮን ቡድን አቀብሎ ” ውስጥ አዋቂዎች ነገሩኝ” ሲል ጋዜጣው ዘግቦ ነበር።

ሌተናል ጄነራል ጻድቃንና አቶ ጌታቸው ግን ከሰላም አማራጭ የፕሪቶሪያው ስምምነት ውጭ የተደረገ መሆኑንን ገልጸው ዜናው ውሸት እንደሆነ ቢገልጹም ዜናውን የለኮሱትም ሆነ የተከፋፈሉት ይቅርታም ሆን ማስተባበያ ሳይሰሩ የአሁኑን ሹመት በነካ እጃቸው አቶ ጌታቸው የትግራይ መሪ መሆናቸውን በቀድሞው የእውሸት ዜና ላይ ደርበው አቅርበውታል።

ጌታቸው ረዳ ጭልጥ ያሉ ካድሬ ናቸው። ይህ ካድሬነታቸው በዚህች ሁለትና ሶስት ዓመታት በሰሩት ሰርከሶች የታየ በመሆኑ ዝርዝር ማብራሪያ አይጠይቅም። በአጭሩ ካድሬ ናቸው። “ከወር በሁዋላ ብልጽግና ወይም ሞት” ሲሉ ቢሰሙ እሳቸው ሳይሆን የሚሳቀቁት አድማጮችና ተመልካቾች ናቸው። ከዚ በዘለለ አሁን አጓጊ የሆነው የሳቸው ብልጽግና መሆን ሳይሆን፣ እሳቸው የሚመሯቸው የተቃውሞ ሚዲያዎችና በማሸበር ተግባር የተሰማሩ ተከፋይ አክቲቪስትና እዛም እዚህም ጥይት የሚተኩሱ ወረበሎች ናቸው።

የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ትናንት አርብ መጋቢት 08/2015 ዓ.ም. ባካሄደው ምርጫ አቶ ጌታቸው ረዳን የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳዳር ፕሬዝዳንት እንደሆኑ ይፋ ሲያደርግ ሁለት አበይት ጉዳዮች ወደ ፊት ብቅ ብለዋል። አንደኛው ስልጣን ወደ ራያ ማምራቱና የትህነግ ተፈጥሯዊ ሞት መሞቱ ነው።

“ለሰላም ያለንን የማያወላውል ቁርጠኝነት አረጋግጠናል። ሰላሙን ለማደፍረስ የተነሱ ኃይሎችን ጨምሮ በሕዝባችን ላይ እየደረሰ ያለውን ስቃይ ለመቅረፍ በሚደረገው ጥረት ያሉትን እንቅፋቶችን ለመፍታት ጊዜያዊ አስተዳደር መመሥረትን ጨምሮ የበኩላችንን ለመወጣት ዝግጁ ነን” ጌታቸው ረዳ

ትህነግ መንግስት ነበር። ከአራት ኪሎ ሲወጣ “እኔም ጌታቸው አሰፋ ነኝ” ብሎ ወደ መቀለ ሄደ። ከመቀለ ወደ ተፈጠረበት በረሃ ሸሸ። ከዛም አንሰራራና ተመልሶ እንዳይድን ሆኖ ተመታ። መመታቱ ብቻ ሳይሆን ህዝቡን መከራና ስቃይ ውስጥ ከተተ። ጨለማ ውስጥ ገባ። ወታቱን አስጨረሰ። ሲመሽበት ድሮ በ2018 እምቢ ያለውን ሁሉ ትቶ ” ያሻችሁን ሁሉ እሺ” ብሎ ህይወት አትርፍ ስምምነት ፈረመ። “በሂደት አብቦ ጠወለገና እንደ ቅጠል ወይቦ ሞተ” ሲሉ ከስምምነቱ በሁዋላ አቶ ሃይሉ ጽፈው ነበር። አሁን የታየውም ይኸው ነው።

አቶ ጌታቸው መመረጣቸው ይፋ ከመሆኑ በፊት የፌደራሉ መንግስት የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ነበር። የኢትዮ 12 መረጃ ምንጮች እንዳሉት መንግስት በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ባስቸኳይ ጊዚያዊ አስተዳደር የማይቋቋም ከሆነ ለኢትዮጵያ ህዝብ ሁኔታውን አሳውቆ፣ ለትግራይ ህዝብ አስረድቶ ራሱ የሚያምንበትን ጊዜያዊ አስተዳደር ለማቋቋም እንደሚገደድ ነግሯቸው ነበር። መንግስት ለዚህ እርምጃ ያደረሰው በጀት ለቆ የመነግስት ሰራተኞች ያልተከፈላቸው ደሞዝ ተከፍሎ ወደ መደበኛ እንቅስቃሴ ለመለስ በሚል ነው።\

መንግስት ይህ የማይሆን ከሆነ ጥይት ሳይተኩስ እምቢ ያሉትን በአውሮፕላን አሳፍሮ ወደ ማረፊያ እንደሚያስገባቸውም አስተንቅቆ እንደነበር የገለጹት የመረጃው ባለቤቶች ” የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን አዲስ አበባ የትህነግ ሰዎችን ሰብስቦ ‘ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የሚሎአችሁን አክብሩ። ከዚህ ውጭ የምናደርገው ነገር የለም’ ብለዋቸዋል። ያደረጉትም ያንን ነው” ሲሉ ነግረውናል። አዲሱ ሹመት የሚጸናው በፌደራል መንግስቱ ቅቡል ሲሆን ብቻ እንደሆነ የፕሪቶሪያው ስምምነት ያስረዳል። እናም መንግስት ሹመቱን ሲያጸድቀው የጌታቸው ረዳ ወንበር ይጸናል። እንደሚሰማው ከሆነ ሁሉም ነገር የመንግስት ቅርብ ክትትል ያለበት በመሆኑ በትግራይ መንግስት ከሚያውቀው ውጭ የተለየ ፍላጎት ይስተናገዳል ተብሎ አይገመትም።

ሌላው አጓጊ ጉዳይ ትህነግ በሌላ ሰው ወይም በዶ/ር ደብረጽዮን እንዲመራ የሚደረግ ከሆነ ነው። አስተያየት ሰጪዎች እንደሚሉት ትህነግን ከትግራይ አስተዳደር ለመገንጠልና በቀደመው አካሄድ እንዲቀጥል ከተመረጠ እድሉ ልክ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ ወይም ሊሎች የቤተሰብ ፓርቲዎች መሆን ነው። በስም አስተያየት ለመስጠት ጊዜው ገና እንደሆነ የገለጹ ለኢትዮ12 የአዲስ አበባ ተባባሪ ” ትህነግ አሸባሪነቱ አልተነሳም። ምርጫ ቦርድ ሰርዞታል። ህጋዊ ዕውቅና የለውም። እዚህ ላይ ቆሞ ከትግራይ አስተዳደር ልነጠል ካል ሞቱን ሳይሆን ራሱን ተረት ወደ ማድረግ ወዷል ማለት ነው። ብዙ ማስረጃዎች ማቅረብ ይቻላል” ሲሉ ገልጸዋል። እኚህ የቀድሞ የትህነግ አባል ሰሞኑንን ሲጠራ ዝርዝር አሳብ እንደሚሰጡም ገልጸዋል።

ሌተናል ጻድቃን ወታደራዊ ክንፉን የሚመሩና የቀድሞውን የስብሃት ነጋን ቦታ በመያዝ ከጀርባ ሆነው የጌታቸው ረዳን አስተዳደር አባላት እንደሚያቋቁሙ ተወርቷል። በጻድቃን አጋዥነት ከአዲስ አበባ የቢሮ ሃላፊ ሆነው የሚሄዱ የተቀናቃኝ ፓርቲ አመራሮች እንደሚኖሩ ተሰምቷል። በትግራይ ያሉ ተቃዋሚ ድርጅቶችም ይወከላሉ ተብሏል። ወታደሩም ይገባል።

ቢቢሲ ጥቂት ስለ አቶ ጌታቸው ረዳ ብሎ የሚከተለውን ጽፎላቸዋል።

ትግራይ ውስጥ ለሁለት ዓመታት ከተካሄደው ጦርነት ጋር በተያያዘ ስማቸው በተደጋጋሚ ሲጠቀስ ከነበሩ ሰዎች መካከል ጌታቸው ረዳ አንዱ ናቸው። አቶ ጌታቸው የትግራይ ኃይሎችን በመወከል በጦርነቱ ሂደት ውስጥ በዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ላይ በተደጋጋሚ ሲቀርቡ ቆይተዋል።

ጌታቸው ረዳ በፓርቲ፣ በክልል እንዲሁም ፌደራል መንግሥቱ ውስጥ በከፍተኛ የኃላፊነት ቦታ ላይ ሰርተዋል። የትግራይ ክልል ገዢ ፓርቲ ሆኖ በቆየው ህወሓት ውስጥ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል፣ የፕሬዝዳንቱ ረዳት እና የፓርቲው ቃል አቀባይ ሆነው ሲሰሩ ቆይተዋል።

አቶ ጌታቸው ረዳ በፌደራል መንግሥቱ ውስጥ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት እና በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ ከፍተኛ አማካሪ ሆነው ከመሥራታቸው በተጨማሪ፣ የመንግሥት ኮምዩኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትርም እና በሌሎች የኃላፊነት ቦታዎችም ሠርተዋል።

ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በሕግ የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው አቶ ጌታቸው ከአሜሪካው የአላባማ ዩኒቨርስቲ ደግሞ በሕግ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል። በዚሁ ዘርፍ በመቀለ ዩኒቨርስቲ መምህር ሆነው ሠርተዋል።

አቶ ጌታቸው በፌደራል መንግሥቱ እና በህወሓት መካከል ያለው ልዩነት እየሰፋ ሄዶ ወደ ጦርነት ከተጀመረ በኋላ በተለያዩ የትግራይ አካባቢዎች ተሰማርተው ከነበሩት የቡድኑ ፖለቲካዊ አመራሮች መካከል አንዱ ሆነው ቆይተዋል።

በጦርነቱ ወቅት የትግራይ ኃይሎችን የተመለከቱ መረጃዎችን ለዓለም አቀፉ የመገናኛ ብዙኃን እና በማኅበራዊ ሚዲያ በትግርኛ፣ በአማርኛ እና በእንግሊዝኛ ሲያርቡ፣ ሲወያዩ እና ሲከራከሩ በስፋት ይታወቃሉ።

ከዚህ ባሻገርም ደም አፋሳሹን ጦርነት ለማስቆም ያስቻለው በፌደራል መንግሥቱ እና በህወሓት መካከል በተደረገው ድርድር ወቅት የትግራይን ወገን በመወከል የተሳተፉ እንዲሁም የፈረሙ አቶ ጌታቸው ረዳ ናቸው

Exit mobile version