Site icon ETHIO12.COM

የኤርትራው ፕሬዝደንት ሰጡት ተብሎ የተሰራጨ ሀሰተኛ መግለጫ።

“Wolkayt Tgedie Amhara Revolutio# ወልቃይትጠገዴ የአማራ ንቅናቄ” የሚል ስያሜ ያለው የትዊተር አካውንት በትናንትናው እለት አንድ አነጋጋሪ መረጃ አጋርቶ ነበር።

ይህ ከ5,400 በላይ ተከታታዮች ያሉት አካውንት “ታላቅ ሰበር ዜና” በሚል መረጃውን ይጀምርና “የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቅ የአማራ ልዩ ኃይልን መፍረስ የለበትም ሲሉ በ ERI TV መግለጫ ሰጥተዋል” የሚል መረጃ አጋርቷል።

አክሎም “በመግለጫቸው ከአማራ ልዩ ኃይልና ሕዝብ ጎን መሆናቸውንና አስፈላጊውን የሎጅስቲክ ድጋፍ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል” ይላል ይህ አሁን ላይ 520 መውደድ (like) እና 204 መልሶ ማጋራት (retweet) የተደረገ መረጃ።

ይህን መረጃ በመውሰድ (ኮፒ በማድረግ) እንደ Dessie Press፣ Tana Media Network፣ ወሎ ሚድያ ሴንተር (WMC)፣ ፩ አማራ… ወዘተ ያሉ የፌስቡክ ገፆች እና አካውንቶችም መረጃውን በስፋት አጋርተዋል።

ይህን መረጃ ተንተርሶ ኢትዮጵያ ቼክ ባደረገው ማጣራት የኤርትራው ፕሬዝደንት ምንም አይነት ንግግር በዚህ ዙርያ በኤርትራ ቴሌቭዥን (Eri TV) ላይም ሆነ በሌሎች ሚድያዎች እንዳላደረጉ መመልከት ችለናል።

ከዚህም በተጨማሪ በኤርትራ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር፣ በቃል አቀባይ፣ በኢትዮጵያ የኤርትራ ኤምባሲ… ወዘተ ላይ ባደረግነው ዳሰሳ ይህ መረጃ እንደሌለ አረጋግጠናል።

በመቀጠል ኢትዮጵያ ቼክ ያናገራቸው ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱ አንድ የኤርትራ ዲፕሎማት መረጃው የተሳሳተ መሆኑን በዛሬው እለት አሳውቀውናል።

ምንጫቸው ያልታወቀ እና ያልተረጋገጡ መረጃዎችን ባለመቀበል እንዲሁም ለሌሎች ባለማጋራት የሀሰተኛ መረጃ ስርጭትን እንከላከል።

FactCheck

Exit mobile version