ETHIO12.COM

የሰሜን ወሎ ፋኖ ይቅርታ ጠይቆ ወደ መደበኛ ህይወት ተመለሰ

” ነገሮች ተበላሽተዋል” በሚል የፋኖ አሰባሳቢ ኮሚቴ ናቸው የሚባሉት ዶ/ር ወንድወሰን አሰፋ ከመስከረም ጋር በስልክ ያደረጉትን ንግግር ይፋ በሆነ ማግስት በሰሜን ወሎ ዞን አካባቢ ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ የፋኖ አባላት የመንግሥትን የሰላም ጥሪ በመቀበልና ይፋዊ ይቅርታ በማቅረብ ወደ መደበኛ ህይወታቸው መመለሳቸውን የአማራ ክልል አስታወቀ።

ክልለሉን ጠቅሶ የአማራ ማስ ሚዲያ ይፋ እንዳደረገው በሰሜን ወሎ ዞን አካባቢ ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ የፋኖ አባላት የመንግሥትን የሰላም ጥሪ በመቀበልና ይፋዊ ይቅርታ በማቅረብ ወደ መደበኛ ህይወታቸው ተመልሰዋል ብሏል። በዚህም ትናንት የዘገብነውን ይህን ዜና አጽንቶታል።

በዘገባችን መከላከያ “ተታለን ነው” በሚል ሽማግሌ የላኩትን የሰሜን ወሎ ፋኖዎች ጥያቄ ለመቀበል የአገር መከላከያ ሰራዊት አመራሮች

  1. ከዚህ በኋላ ምንም አይነት መንገድ እንዳይዘጋ፣
  2. ምንም አይነት የታጠቀ አካል ከተማ ውስጥ እንዳናገኝ እርቅም ይሁን ግጭት ከከተማ ውጭ ጫካ ላይ ይሁን፣
  3. አፈሙዝ ወደ መከላከያ ሰራዊት እንዳያዞሩ ሠራዊቱ የሚላቸውን ትዕዛዝ አክብረው ይቀመጡ፣
  4. የመከላከያን ጥቁር ክላሽ ሰብስበው ያስረክቡን በሚል ቅድመ ሁኔታ ካስቀመጠ በኋላ የሽምግልና ሂደቱን እንዲያስቀጥሉ ተስማምተው ሽምግልና ለመጡት ሽማግሌዎቹ ቅድመ ሁኔታ አስቀምጠው እንደነበር ማመለከታችን ይታወሳል

የአማራ ክልል መንግሥት ከዚህ በፊት በግላቸው ታጥቀው ሲንቀሳቀሱ የቆዩ ግለሰቦችን እና ቡድኖችን በማወያየት ወደ መደበኛ የጸጥታ አደረጃጀት እንዲገቡ ወይም ደግሞ ወደ መደበኛ ህይወታቸው እንዲመለሱ ጥረት ሲያደርግ መቆየቱ ይታወሳል። በዚህ ጥረቱም በርካታዎች ጥሪውን ሲቀበሉ ያፈነገጡና የተበተኑ መኖራቸውን አስታውቀው ነበር።

ነገር ግን በቅርቡ በሰሜን ወሎ ዞን አካባቢ የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች የመንግሥትን ጥሪ ባለመቀበል ከመከላከያ ጋር ወደ ግጭት የገቡ መሆኑም ይታወሳል። ሆኖም በቅርቡ የፋኖ አባላቱ ይፋዊ ይቅርታ በመጠየቅ የመንግሥትን የሰላም ጥሪ መቀበላቸውን በማሳወቅ ከክልሉ መንግሥት እና ከመከላከያ ሠራዊት አመራሮች ጋር ውይይት አድርገው ወደ መደበኛ ህይወት ለመመለስ መስማማታቸውን የክልሉ መንግሥት እንዳስታወቀ አሚኮ ዘግቧል።

ትናንት በአማራ ክልል የተከሰተውን ቀውስ በግንባር ቀደምትነት መርቷል የሚባለው የሰሜን ወሎ ፋኖ መሪ ምሬ ወዳጆ የባለወልድ አባቶችን ሽምግልና መላኩ ተሰምቷል። ምሬ ወዳጆ ከልዩ ኃይሉ እና ከህዝቡ ድጋፍ አገኛለው በሚል ወደ ግጭት ቢገባም ባሰበው ልክ ድጋፍ ማግኘት ባለመቻሉ ለመከላከያ ሰራዊት ሽምግልና መላኩን ከስፍራው መረጃ ያላቸው አመልክተዋል። በዚህ ሽምግልና የተሳትፉ የባለወልድ አባቶችም “ጦርነት በቃን፣ ከዚህ በላይ ጦርነት ውስጥ መቆየት አንፈልግም” ብለው ምሬን የገሰፁ መሆኑን እና መከላከያ ሰራዊትም ኢመደበኛ አደረጄጀቱ ትጥቁን ለመከላከያ አስረክቦ ወደ መደበኛ ህይወቱ ወይም በሚታወቅ መዋቅር እንዲካተት ስምምነት መድረሱን ጠቃሰን ዘግባን ነበር።

Exit mobile version