Site icon ETHIO12.COM

ትህነግ “ህጋዊ ሰውነቴ ይመለስ” ሲል ያቀርበውን ጥያቄ ምርጫ ቦርድ ውድቅ አደረገ

ምርጫ ቦርድ ህወሓት ሕጋዊ ሰውነት አግኝቶ ለመንቀሳቀስ የሚችለው በተደነገገው አዋጅ መሠረት በድጋሚ የምዝገባ ጥያቄ ሲያቀርብ እና ቦርዱ ሕጉን መሠረት አድርጎ ሲፈቅድ መሆኑንም ዛሬ ግንቦት 5/ 2015 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

ህወሓት ለምርጫ ቦርድ የሕጋዊ ሰውነት ስረዛና የፓርቲው ንብረት እገዳ ይነሳልኝ ጥያቄ ያቀረበው ፕሪቶሪያ የተደረሰውን ግጭትን በዘላቂነት ለማስቆም የተደረሰውን ስምምነት በመጥቀስ ሚያዝያ 28/2015 ዓ.ም በጻፈው ደብዳቤ ነው።

ደብዳቤው ምርጫ ቦርድ የፓርቲውን ሕጋዊ ስረዛ አስመልክቶ ጥር 10/ 2013 ዓ.ም ያስተላለፈውን ውሳኔ ጠቅሷል።

ምርጫ ቦርድ ያስተላለፈው ውሳኔ ፓርቲው ኃይልን መሠረት ያደረገ የአመጻ ተግባር ላይ መሳተፉን ተረጋግጧል በሚል የፓርቲው ሕጋዊ ሰውነት እንዲሰረዝ፣ የፓርቲው ኃላፊዎች በፓርቲው ስም መንቀሳቀስ እንዳይችሉ፣ እንዲሁም የፓርቲው ንብረት ፓርቲው ዕዳ ካለበት ለዕዳው መሸፈኛ እንዲውል፣ ቀሪው ገንዘብና ንብረትና ደግሞ ለሥነ ዜጋ መራጮች ትምህርት እንዲውል የሚደነግግ ነው።

በትግራይ ክልል የነበረው ጦርነት በሰላም በመቋጨቱና በፌደራል መንግሥቱና በህወሓት መካከል የተደረሰውን ስምምነትም በመጥቀስም ፓርቲው የአመጻ ተግባር ላይ ተሰማርቷል የሚለው ድምዳሜ አሁን ላይ መለወጡን ታሳቢ በማድረግ ቦርዱ ከዚህ ቀደም ያስተላለፋቸውን የፓርቲውን ሕጋዊ ሰውነት ስረዛና ሌሎች ብያኔዎች እንዲነሳ ሲል መጠየቁንም ምርጮ ቦርድ አስፍሯል።

ቦርዱ ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ አስተላለፍኩት ባለው ውሳኔ ህወሓት በላከው ደብዳቤ እንደተገለጸው ለቦርዱ ውሳኔ ምክንያት የሆነው ኃይልን መሠረት ያደረገው የአመጻ ተግባር አሁን የለም ብሏል።

ነገር ግን እንደገና የፓርቲውን ሕጋዊ ሰውነት ለመመለስ የሚያስችሉ ድንጋጌዎች በአዋጅ 1162/ 2011 ተደንግጎ እንደማይገኝ ጠቅሷል። በዚህም ምክነያት ቦርዱ በህወሓት የቀረበለትን የሕጋዊ ሰውነት ጥያቄ የማስመለስ ጉዳይን በሕግ የተደገፈ ሆኖ ባለማግኘቱ አንዳልተቀበለው ጠቅሷል።

ስለዚህ በአዋጁና በተከታዮቹ ድንጋጌዎች መሠረት ህወሓት ሕጋዊ ሰውነት አግኝቶ ለመንቀሳቀስ የሚችለው በድጋሚ የምዝገባ ጥያቄ ሲያቀርብ እና ቦርዱ ሕጉን መሠረት አድርጎ ሲፈቅድ መሆኑን መወሰኑን አመላክቷል።

የፓርቲው አመራሮች እና ንብረትን በተመለከተ የቀረበውን ጥያቄ ቦርዱ ፓርቲው የሰጠው የስረዛ ውሳኔ ውጤቶች በመሆናቸው እንደ አዲስ ሊጠየቁ የሚችሉ ሆነው ባለመገኘታቸው እግዱ እንዳልተነሳ ጠቅሶ የቀረበውን ጥያቄ ቦርድ ውደቅ ማድረጉ ተጠቅሷል።

ጥር 10/2013 ዓ.ም. ደግሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይን (ህወሓት) ሕጋዊ ሰውነት መሰረዙን ማስታወቁ ይታወሳል።

ቦርዱ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ህወሓት በአመጽ ተግባር ላይ መሰማራቱን በተለያዩ መንገዶች ማረጋገጡን በመግለጽ፣ ሕጋዊ ሂደቶችን በመከተል የፓርቲውን ሕጋዊ ሰውነት በመሰረዝ ማንም በህወሓት ስም መንቀሳቀስ እንደማይችል ውሳኔ አሳልፎ እንደነበር ይታወሳል።

በፕሪቶሪያ የተደረሰውን ግጭት የማቆም ዘላቂ ስምምነት ተከትሎ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሽብር ቡድንነት ተሰይሞ የነበረው ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ፍረጃው መነሳቱ ይታወሳል።

በትግራይ ተከስቶ ወደ አማራ እና አፋር ክልሎች የተዛመተው ደም አፋሳሽ የእርስ በርስ ጦርነት የመቶ ሺዎችን ሕይወት ቀጥፏል እንዲሁም ሚሊዮኖችን ለሰቆቃ ዳርጓል።

በመቶ ሺዎች በተቀጠፉበት ጦርነት መደፈር፣ ወሲባዊ ጥቃቶች፣ የዘፈቀደ ግድያ፣ ረሃብ በጦር መሣሪያነት ጥቅም ላይ መዋላቸውን የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት ሪፖርት ያሳያል ሲል ቢቢሲ የምርጫ ቦርድን ደብዳቤ ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።

Exit mobile version