Site icon ETHIO12.COM

አባ መልዓከ ሰላም ምስክርነት ሰጡ – የኤሊያስ ወረዳ አስተዳዳሪ ” ተማርከዋል፣ አብቅቷል” አሉ

ላለፉት አምስት ቀናት በከፍተኛ ደረጃ መነጋገሪያ የሆነውና የፌደራልና የክልል መንግስት ምንም መረጃ ያልሰጡበት የደብረ ኤሊያስ ገዳም በርካቶችን አስጨንቆ ከርሟል። ገዳማቱ ወታደራዊ ማስለጠኛ፣ የሚፈለጉ ሰዎች መመሸጊያና የወንጀለኞች መከማቻ እንደሆነ ቢገለጽም፣ ይህን የማይቀበሉ አባባሉን ሲኮንኑ ከርመዋል።

“ግራኝ አብይ አህመድ” በሚል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገዳማት እንዲወድሙ መመሪያ እንደሰጡ ተደርጎ በስፋትና በቅብብሎሽ የተሰራጨው ዜና “ኦሮሞን እንደ ብሄር” ቀዳሚ ጠላትና አውዳሚ አድርጎ ያቀርባል። የኢትዮጵያ መከላከያ ህግ ለማስከበር በሚል የጀመረውን ዘመቻ ” የኦሮሞ ኦነግ ወራሪ ሰራዊት” በሚል ስም የሚጠሩ እንዳሉት ይኸው ጦር ክፉኛ ጉዳት ደርሶበታል።

“የአማራ ደደቢት” ሲሉ የደብረ ኤሊያስ ገዳምን የሚጠሩት ክፍሎች በሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ የሚመራው የአማራ ሕዝባዊ ግንባር ድል መቀዳጀቱን፣ የወረዳው ህዝብም ሙሉ በሙሉ ከግንባሩ ሃይል ጋር እየተፋለመ መሆኑንን ይገልጻሉ። መልሰው ደግሞ በውጊያው የመከላከያ ሃይል የሚሰጠውን ምላሽ ወይም ማጥቃት ሲያወግዙ መሰማቱ መረጃውን ግራ የሚጋባ አድርጎታል። ከሁሉም በላይ ግንባሩ ማጥቃቱን ድል ማስመዝገቡን እየገለጸ፣ የትጥቅ ትግል ላይ መሆኑንን እያወጀ መከላከያ ውጊያ መክፈቱን የሚኮንን መግለጫ ደጋግሞ ማውጣቱ አነጋጋሪ ሆኗል።

ይህ በንዲህ እንዳለ ነው አቶ መልካሙ አዲስ የወረዳው አስተዳዳሪ በድምጽ መረጃ የሰጡት። እሳቸው እንዳሉት ግጭቱ ከሽፍቶች ጋር ነበር። አሁን እጅ ሰጥተው አብቅቷል። ” በገዳሙ ላይ የደረሰ ምንም ጉዳት የለም። እጅ ሰጡ በቃ” ሲሉ የተደመጡት አስተዳዳሪው ” በቃኝ ካሁን በሁዋላ” ሲሉ ማህበራዊ ሚዲያው ባሰራጨው ዘገባ ላይ ግርምታቸውን አስቀምጠዋል።

እየሳቁ ” የሚዲያውን ዕውነት አየነው። እንዳናዳምጠው ነው ያደረገን” ያሉት አቶ መለኩ፣ አርሶ አደሩ ተረጋግቶ እርሻውን እያረሰና እየኖረ በሬ ውለደ ወሬ ዝም ብሎ መልቀቅ … “ሚዲያ እዲህ ከሆነ ጥርቅም ይበል” በማለት የተባለው ሁሉ ሃሰት መሆኑንን ገልጸዋል። አስፈላጊ ከሆነ ገለልተኛ ሰዎችን መጠየቅ እንደሚቻል አመልክተው ” የከፋቸውና ቅር ያላቸው የሚነግሯቸውን በሙሉ ያሰራጫሉ” ሲሉም ገዳሙ ወደመ የሚል መረጃ ሲያስተላለፉ የነበሩትን ከሰዋል። የስምንት ደቂቃ የድምጽ ቅጂውን ከአባ

ስለገዳሙ ወቅታዊ ሁኔታ አገረ ስብከቱ ምን አለ?

የምስራቅ ጎጃም ዞን አገረ ስብከት ዋና አስተዳዳሪ አባ መላከ ሰላም፣ በጦርነቱ ምክንያት ግብተው ማጣራት እንዳልተቻለ ገልጸው፣ ኮሚቴ አቋቁመው የደረሰውን ጉዳት ካለ ለማጣራት ዕቅድ መያዛቸውን አስታውቀዋል። ጠያቂውን ማራቱ ከተደረገ በሁዋላ ቢደውልላቸው መልካም እንደሆነ አስታውቀው ለዞኑ አስተዳደርና ለመንግስት ገዳማቱና አብያተ ክርስቲያኑ ጉዳት እንዳይደርስባቸው ማስታወቃቸውን አመልክተዋል። ምንም አይነት ችግር በተቋማቱ ላይ እንደማይደስ ማረጋገጫ እንደተሰጣቸውም ገልጸዋል።

አባ መልአከስ ሰላም “በወሬ ደረጃ ስንሰማ ግን አብያተ ክርስቲያናቱ ምንም ጉዳት አልደረሰባቸውም” ብለዋል። ሄደው ለማረጋገጥ ዕቅድ መያዛቸውን በድጋሚ አመልክተው፣ ሚዲያ ላይ የሚቀርብ በመሆኑ የሃይማኖት አባት እውነታውን መናገር እንዳለበት በመጠቆም ገዳማቱን ሊቀጳጳሱ አስቀድመው ጠርተዋቸው እንደነበር ይፋ አድርገዋል። ወደፊትም ቤተክርስቲያኑም፣ ገዳማቱም፣ ሰዎቹም የእነሱ በመሆናቸው ንግግር እንደሚደረግ አመልክተዋል። ይህ ከሆነ በሁዋላ የጠራ መረጃ እንደሚሰጥ አስታውቀዋል።

ከሁሉም ወገን እንደሚሰማው በገዳማቱ አካባቢና ጦርነት ተካሂዷል። ችግሩ የተፈጠረውና መረጃውን ያዛባው ጦርነቱ ገዳማትን ማውደሙና መነኮሳቱን፣ እዛ የሚኖሩ ሴቶችን ማጥፋቱ የተገለጸበት አግባብ ነው። በዚህ ቪዲዮ የተነበበው የጀርመን ድምጽ የባህር ዳር ዘገባቢ የመንግስት ሃይል ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት፣ ከባድ መሳሪያ ገዳማቱ ላይ መውደቁን እማኞች ነገሩን ሲል አመልክቷል። ዋና አስተዳዳሪው “፡ ሚዲያ እንዲህ ከሆነ” ሲሉ ትዝብታቸውን ከገለጹበት ሚዲያ መካከል አንዱ የጀርመን ድምጽ ይሁን አይሁን በይፋ ባይገልጹም ሚዲያው ይህ እስከተባለ ድረስ ማስተባበያም ሆነ ማስተካከያ አላደረገም።

ከመንግስት ጋር በትብብር ሲሰራ ከርሞ ምክንያቱ ግልጽ ሳይሆን የተቃዋሚ ሃይሎች መድረክ የከፍተው መሳይ መኮንን ” ደብረ ኤሊያስ ገዳም ለአምስተኛ ቀን እየተደበደበ ነው” ሲል ባሰራጨውና በስፋት በተበተነው መረጃ ” ቤተ ክርስቲያን እንዴት ዝም ትላለች” ሲል ወቅሷል።

” የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በጉዳዩ ላይ ለምን ዝም እንዳለች አልገባኝም። ያለችበት ወቅታዊ ሁኔታን በሚገባ የምረዳው ቢሆንም እንደደብረ ኤሊያስ አይነት ጥንታዊና የሀገር ሀብት የሆነን ገዳም የአብይ ሰራዊት እስኪያጠፋው መጠበቅ ያለባት አይመስለኝም። በጉዳዩ ዙሪያ የምዕመናን ድምጽምም አይሰማም። የቤተክርስቲያኒቱ የተለያዩ ማህበራት፡ አደረጃጀቶች ድርጊቱን ማውገዝና ጠቅላይ ሚኒስትሩ እጃቸውን እንዲሰበስቡ ጫና መፍጠር ያለባቸው ይመስለኛል” በሚል መረጃውን ካሰራጨ በሁዋላ፣ የወረዳው አስተዳዳሪ በድምጽና በመግለጫ፣ የምስራቅ ጎጃም አገረ ስብከት ዋና አስተዳዳሪ በድምጽ ” የሃይማኖት አባት ነን፣ እውነት መናገር አለብን፣ ለሚዲያ የሚቀርብ ነው” ሲሉ ከቅርብ ሆነው የሚያውቁትን ገልጸዋል። አስተዳዳሪውም ” ተማርከዋል በቃ” ሲሉ ኦፕሬሽኑ ማለቁን አስታውቀዋል። እንደሚሰማው ከሆነ የጋዜጠኞች ቡድን በስፍራው ተገኝቶ መረጃ እያሰጋጀ ነው።

መሳይ መኮንን ያሰራጨው ዜና ከስር ያለው ነው

ደብረ ኤሊያስ ገዳም ለአምስተኛ ቀን እየተደበደበ ነው። ዛሬ በዙሪያ የሚገኙ ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ላይም ጥቃት ተከፍቷል። ፋኖዎች ተጠልለውበታል በሚል በተጀመረው ጥቃት ለጊዜው ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች ተገድለዋል። አብይ ተጨማሪ ሃይል ወደ ስፍራው መላኩንም የአይን እማኞች ነግረውኛል። በቤተ እምነቶች ላይ ተደጋጋሚ ጥቃት በመከላከያ ሰራዊቱ እየተፈጸመ ነው። ባለፈው በሰሜን ሸዋ እንዲሁ በአንድ ገዳም ላይ ጥቃት መፈጸሙ የሚታወስ ነው።

ፋኖን አጠፋለሁ ብሎ የገባው የአብይ ሰራዊት መጠነ ሰፊ ሰብዓዊ ቀውስ እያስከተለ ነው። መከላከያ ሰራዊቱ ታሪኩን እያበላሸ ነው። በአንድ ቀበሮ ጉድጓድ አብረው በተዋደቁት የአማራ ልጆች ላይ ጥቃት ከፍቷል። ሰውዬው ከህወሀት ዘመንም በከፋ ሁኔታ መከላከያውን የግሉ ጦር አድርጎታል። ህወሀትን በሰፊው እያስታጠቀ የአማራውን ማህበረሰብ መሳሪያ ለመንጠቅ የከፈተው ጦርነት በታሪክ ይቅር የማይሉት ትልቅ ጥፋት ሆኖ ይመዘገባል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በጉዳዩ ላይ ለምን ዝም እንዳለች አልገባኝም። ያለችበት ወቅታዊ ሁኔታን በሚገባ የምረዳው ቢሆንም እንደደብረ ኤሊያስ አይነት ጥንታዊና የሀገር ሀብት የሆነን ገዳም የአብይ ሰራዊት እስኪያጠፋው መጠበቅ ያለባት አይመስለኝም። በጉዳዩ ዙሪያ የምዕመናን ድምጽምም አይሰማም። የቤተክርስቲያኒቱ የተለያዩ ማህበራት፡ አደረጃጀቶች ድርጊቱን ማውገዝና ጠቅላይ ሚኒስትሩ እጃቸውን እንዲሰበስቡ ጫና መፍጠር ያለባቸው ይመስለኛል።

Exit mobile version