Site icon ETHIO12.COM

የሚኒስትሮች ምክር ቤት በአማራ ክልል አስቸኳይ አዋጅ እንዲታወጅ ወሰነ

የሚኒስትሮች ምክር ቤት በአማራ ክልል ወቅታዊ ሁሌታና የክልሉ መንግስት የችግሩን ግዝፈት ጠቅሶ ለፌደራል መንግስት ባቀረበው ጥሪ መሰረት ተወያየቶ መንግስት በህገ መንግስቱ የተጣለበትን ሃላፊነት ለመወጣት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጅ ስላለበት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 6/2015 እንዲታወጅ በሙሉ ድምጽ መወሰኑ ተገለጸ።

የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 23ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን ዋናውና ቀዳሚ ያደረገው ግን የአማራ ክልልን ጉዳይ እንደሆነ ውሳኔዎቹን የዘገቡት የመንግስት ሚዲያዎች ዘገባ ጠቁሟል። በዩኒቨርስቲዎች የአካዳሚ ነጻነት አስመልክቶም ውሳኔ ተላልፏል።

23ኛ መደበኛ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ስብሰባ ውሳኔዎች፦

1. ምክር ቤቱ በቅድሚያ የተወያየው የሕዝብን ሠላምና ደህንነት ለማስጠበቅ በቀረበው የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 6 /2015 ላይ ነው፡፡

በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት የሚታየውን በትጥቅ የተደገፈ ህገወጥ እንቅስቃሴ በመደበኛ የህግ ማስክበር ስርዓት ለመቆጣጠር ወደ ማይቻልበት ደረጃ የተሸጋገረ በመሆኑ፤ ይህ እንቅስቃሴ የክልሉን ነዋሪ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ እንቅስቃሴ በከፍተኛ ደረጃ ያወከ እና ህገ መንግስታዊ ሥርዓቱን አደጋ ላይ የጣለ በመሆኑ፤ የሕዝብን ሠላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ እንዲሁም ህግ እና ስርዓት ለማስከበር የአስቸኳይ ጊዜ እርምጃዎችን መውሰድ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ፣ እንቅስቃሴው በሃገር ደህንነት እና በህዝብ ሰላም ላይ የደቀነው አደጋ ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ መጥቷል፡፡ መንግስት ትጥቅ አንስተው የሚንቀሳቀሱ ሃይሎች ሁሉ የሰላም እና ህጋዊ መንገድን እንዲከተሉ ተደጋጋሚ የሰላም ጥሪዎችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ የታጠቁ ፅንፈኛ ቡድኖች እየፈፀሙ ባለዉ ጥቃት ምክንያት የክልሉ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ ይገኛል፡፡

የክልሉ መንግስትም በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ያጋጠመው የፀጥታ መደፍረስ በክልሉ ከፍተኛ ሰብዓዊ፣ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት እያስከተለ የሚገኝ መሆኑን በመግለጽ፣ ሁኔታውን በመደበኛው የህግ ማስከበር ሥርዓት ለመቆጣጠር አዳጋች ሆኖ በመገኘቱ፣ የፌደራል መንግስት አስፈላጊውን የህግ ማዕቀፍ በኢፌድሪ ህገ መንግስት መሰረት እንዲደነግግ እና ተገቢውን እርምጃ እንዲወስድ ጥያቄ አቅርቧል።

በመደበኛ የህግ ስርዓትን መሰረት አድርጎ ይህን ፈር የለቀቀ እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር አዳጋች ሁኔታ በመፈጠሩ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጅ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ህገመንግስቱ እና ህገመንግስታዊ ስርዓት ላይ የተቃጣ አደጋን በመደበኛ የህግ ስርዓት ለመቆጣጠር ባልተቻለ ጊዜ የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማወጅ ህገመንግስታዊ ስርዓትን ከአደጋ የመከላከል ስልጣን እንዳለው በኢፌዴሪ ህገመንግስት አንቀፅ 93 (1) ተደንግጓል፡፡

በመሆኑም የሚኒስትሮች ምክር ቤት በህገ መንግስቱ የተጣለበትን ሃላፊነት ለመወጣት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጅ ስላለበት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 6/2015 እንዲታወጅ በሙሉ ድምጽ ወስኖል።

2.በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማቋቋሚያ ረቂቅ ደንብ ላይ ነው፡፡

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአካዳሚክ ነጻነት እንዲረጋገጥ፣ ከፖለቲካዊም ሆነ አስተዳደራዊ ጣልቃ ገብነት ነጻ ሆነው የመማር ማስተማር እና የምርምር ሥራዎችን የሚያካሂዱ እንዲሆኑ ለማስቻል የራስ ገዝ ዩኒቨርሲቲ አዋጅ መውጣቱ ይታወቃል፡፡

በዚሁ መሰረትም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ራስ ገዝ ሆኖ አካዳሚያዊ እና አስተዳደራዊ ነፃነቱ ተጠብቆ መንቀሳቅስ እንዲችል፣ በትምህርት ዘርፍ ለተጀመረው የሪፎርም እንቅስቃሴ ፈር ቀዳጅ ሆኖ፣ የራስ ገዝ ዩኒቨርስቲ ስርዓትን ተግባራዊ እንዲያደርግ እና ለሌሎች ዩኒቨርሲቲዎችም ተምሳሌት እንዲሆን አስቻይ ሁኔታን የሚፈጥር ረቂቅ ደንብ ተዘጋጅቶ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቧል፡፡

ምክር ቤቱም በደንቡ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣት ቀን ጀምሮ በሥራ ላይ እንዲውል ወስኗል፡፡

Exit mobile version