ETHIO12.COM

“በዲሽቃና በታንክ ፈራረሰ የተባለው የፋሲል ግንብ ምንም አልሆነም”

መሳይ መኮንን የአገር መከላከያ ሰራዊት በድሽቃና በታንክ አፈራርሶታል ያለው የፋሲል ግንብም ሆነ ቤተ ከርስቲያናትና ቅርሶች አንዳችም ጉዳት እንዳልደረሰባቸው ነዋሪዎችና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አመለከቱ። የክልሉ መገንኛም በምስል አስደግፎ ምስክሮች የተጠቀሰው ጉዳት እንዳልደረሰ ሶናገሩ አሰምቷል።

መሳይ መኮንን አዲስ አበባ ሆኖ የልማት ዜናዎችን ሲዘግብና የመከላከያን ገድል ሲያስራውቅ ቆይቶ በድንገት የተቃውሞ ጎራውን ከተቀላቀለ በሁዋላ በቅርቡ የፋሲል ግንብ መውደሙን በዚህ መልኩ ለመግለጽ የፈለገበትን ልዩ ምክንያት ይህን ባለበት ጽሁፉ ግርጌ አላስታወቀም። በምስል ተደግፎ ሃሰት መናገሩ ይፋ መሆኑንንም ተከትሎ በሚዲያ ህግ መሰረት አላስተባበለም። ይቅርታም አልጠየቀም። የሚከታተሉት ወገኖችም ይህን እንዲያደርግ ሲጠይቁት አልተሰማም።

“በጎንደር ከተማ ተከስቶ በነበረው አለመረጋጋት በቅርሶች ላይ የደረሰ ጉዳት የለም” ሲል በጎንደር ከተማ የዓለም አቀፍ ቅርሶች አስተዳደር በይፋ ገልጿል። ቱሪስ ለጎንደር ታላቅ ገቢዋና የበርካቶችን ህይወት የሚደግፍ መሆኑ እየታወቀ በዚህ ደረጃ የተሳሳተ መረጃ ለማሰራጨት የተኬደበት ርቀት ” እውን እንዲህ ያለው አካሄድ አማራን ይጠቅማል?” የሚል ጥያቄ አስነስቷል። አማራ መገናኛ የሚከተለውን ዘግቧል።

በጎንደር ከተማ የዓለም አቀፍ ቅርሶች አስተዳደር አስተዳዳሪ ጌታሁን ስዩም፤ በጎንደር ከተማ ዘጠኝ ቅርሶች በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) ተመዝግበው የሚገኙ መሆኑን ገልፀዋል። እነዚህም ቅርሶች ጎንደር ከተማን የቱሪዝም ማዕከል በማድረግ የላቀ አስተዋጽዖ እያበረከቱ መሆኑን ተናግረዋል።

በመሆኑም ከቱሪዝም እንቅስቃሴ አንፃር በከተማዋና አካባቢው የሚነሱ ማናቸውም አለመረጋጋቶች በዘርፉ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ መሆኑን አብራርተዋል።

በጎንደር ከተማና አካባቢው ሰሞኑን በተፈጠረው አለመረጋጋት በቱሪዝም እንቅስቃሴው ላይ እንከን የፈጠረ ቢሆንም በቅርሶች ላይ የደረሰ ጉዳት የለም ሲሉ ገልጸዋል።

የሰላም ጉዳይ ለቱሪዝም እንቅስቃሴ እድገትና ልማት የላቀ አስተዋጽዖ እንዳለው የገለጹት አስተዳዳሪው፤ የሰላም እጦትና አለመረጋጋት ዘርፉን የሚጎዳ ስለመሆኑ አንስተዋል።

በጎንደር ከተማና አካባቢው ሰሞኑን የተፈጠረው አለመረጋጋት በቅርሶች ላይ ጉዳት ባያስከትልም የቱሪዝም እንቅስቃሴውን በእጅጉ አስተጓጉሏል ብለዋል።

በጎንደር ከተማ የሚገኙ ሁሉም ቅርሶች የሚጠበቁት በሕዝቡ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይም የሀገርና የዓለም ኃብት የሆኑ ቅርሶችን ሁሉም የመጠበቅ ኃላፊነት እንዳለበት አስገንዝበዋል።


Exit mobile version