Site icon ETHIO12.COM

“ዐጼ ምኒልክ ከ119 ዓመት በፊት የጦር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ያቋቋሙበት ቀን የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀንኾኖ እንዲከበር ተደርጓል”

“ዐጼ ምኒልክ የጦር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ያቋቋሙበት ቀን የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን ኾኖ እንዲከበር ተደርጓል” ሲሉ በዓሉ 119 ዓመታትን ወደሁዋላ ሄዶ በዓሉን ማክበር የተፈለገበትን ምክንያት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ አስታወቁ።

የኢትዮጵያ ጦር ኃይሎች ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በ116ኛ የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን አከባበር ላይ ንግግር ነው ይህን ያሉት። ፊልድ ማርሻሉ ኢትዮጵያ ረጅም ዕድሜ ያላት ቀደምት እና በትውልድ ቅብብሎሽ የዘለቀች ታላቅ ሀገር መኾኗን ገልጸዋል።

በእነዚህ ረጅም የታሪክ ዘመናትም በየትውልዱ በነበሩ ልጆቿ ተጋድሎ ነጻነቷ እና ክብሯ ተጠብቆ የተላለፈችልን ሀገር ናት ብለዋል።

መንግሥት በተለወጠ ቁጥር የሀገር እሴቶች እየፈረሱ በመሄዳቸው ቀደምት ጀግኖች እና ባለድሎች እየተዘነጉ፣ ተተኪው ትውልድም የጀግንነት እና የአርበኝነት ሞዴል እንዳያገኝ የሚያደርጉ ፖለቲካዊ እሳቤዎች ሲያጋጥሙን ቆይተዋል ነው ያሉት።

በተለያዩ ጊዜያት ወደ ሥልጣን በመጡ መሪዎች እሳቤ ላይ ብቻ ተመስርተው ሲጻፉ የነበሩ ታሪኮች የጭቅጭቅ እና የግጭት መንስዔ ስለመኾናቸውም ተናግረዋል።

ትውልድ በጋራ የተግባባበት የጋራ ታሪክ ባለመኖሩ በአንድነት ቆሞ ሀገሩን ከመገንባት ይልቅ ገዥዎች በሚሰጡት አጀንዳ ጎራ ለይቶ ለመናቆር ተገዷል ብለዋል።

ለአብነትም በፊት ይከበር የነበረው የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን የቀደምት ጀግኖችን ታሪክ ቆርጦ ያስቀረ እና የረሳ ነበር ነው ያሉት። ከለውጡ በኋላ በተደረሰው ውሳኔ መሠረት ቀኑ ታሪክን አካታች በኾነ መልኩ እንዲከበር ኾኗል ነው ያሉት ፊልድ ማርሻሉ።

የመከላከያ ሠራዊት ቀን የሚከበርበትን ወቅት ለመምረጥ ጥናት ስለመደረጉም ገልጸዋል። በዚህም መሠረት በዘመናዊ የመንግሥት አሥተዳደር ውስጥ የሀገር መከላከያ ሠራዊት በቋሚነት ተደራጅቶ እንደተቋም የተመሠረተበትን ቀን የሠራዊት ቀን በዓል ለማድረግ ተመራጭ ኾኖ ተወስዷል ነው ያሉት።

በዚህም መሠረት “ዐጼ ምኒልክ የጦር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ያቋቋሙበት እና ሚኒስትር የሰየሙበት ቀን የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን ኾኖ እየተከበረ ነው” ብለዋል ፊልድ ማርሻሉ።

ይህ ታሪካዊ ቀን ጥቅምት 15/1900 ዓ.ም ነበር። ለዚህም ነው የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን በየዓመቱ ጥቅምት 15 እንዲኾን የተወሰነው ብለዋል።

የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን በዚህ ታሪካዊ ቀን መከበሩ ቀደምት ጀግኖችን ሞዴል ያደረገ፣ ከቀደምቶች ታሪክ የሚማር እና የሀገር አለኝታ የኾነ ሠራዊት ለመገንባት ስለማስቻሉ ፊልድ ማርሻሉ አመላክተዋል።

ዜናው የአሚኮ ነው


Exit mobile version