Site icon ETHIO12.COM

አብይ አህመድ ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤት እንደምትሆን አረጋገጡ፤ “የሴራ ተንታኞች ሲሳካ በልጆቻችሁ ማፈሪያ እንዳትሆኑ”

የቀይባህርን አስፈላጊነት ዓለም ሁሉ ከሩቅ እያነሳና ቀርቦ ቦታ እያዘጋጀ ባለበት በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ይህን ጉዳይ ማንሳቷ እንዴት ሃጤያት ይሆናል፣ በርካታ አገር ወዳድ ዜጎች ሲያነሱት የነበረው ጥያቄ ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ይህንኑ ጉዳይ አንስተው የቀይ ባህር ባለቤት የመሆን ጉዳይ ጥርጥር እንደሌለው አስታውቀዋል።

“የልጆቻችንን የወደፊት ህይወት መታደግ ግዴታችን ነው” ያሉት አብይ አህመድ ” ኢትዮጵያ የወደብ ባለቤት ትሆናለች። አትጠራጠሩ” ብለዋል። አክለውም አሁን በሴራ ትንተና በቪዲዮ በተቃውሞ ጎራ ለቆሙና አጅንዳ ለማስቀየር የቀረበ አሳብ እንደሆነ ለሚሰብኩ ” ሴራውን በጽሁፍም አድርጉት። ሲሳካ በልጆቻችሁ ፊት ታፍራላችሁ” ብለዋል።

“አጀንዳ ለማስቀየር፣ አገር ለመውረር…” በሚል የኢትዮጵያን የባህር በር ባለቤት ለመሆን የጀመረችውን ሩጫ ለማጣጣል ለሚሞክሩ ” ባህር ሃይል ስንገነባ የትነበሩ? ባህር ሃይል ስንገነባ የባህር በር እንፈልጋለን ማለት አይደል?” በሚል ጥያቄ ሰንዝረው ” የዛኔ ዩቲዩብ የላቸውም ነበር” ሲሉ አክለው ህዝብ እንዲመዝን የሚያስችል አቅጣጫ አመላክተዋል።

ኢትዮጵያ ማንንም የመውረርም ሆነ ሉአላዊነት የመድፈር ፍላጎት እንደሌላት ለዓለምም ለአፍሪካም በይፋ ያስታወቁት ጠቅላይ ሚኒስትሩ “የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በዓለም የቢዝነስ ውል አግባብ መቀበል ግን ግዴታ ነው” ብለዋል።

ከሰላሳ ዓመት በፊት ሁለት ወደብ የነበራት አገር ወደ ግዢ ዝቅ ማለቷን፣ ከኤርትራ ጋር በወቅቱ በተፈጠረ ችግር ወደ ጅቡቲ ብቻ በመዞር ይበልጥ ዝቅ እንዳለች ያስታወሱት አብይ አህመድ፣ ዛሬ ላይ ታላላቆቹ አገሮች ጅቡቲ መሰባሰባቸውን አንስተው እንደሱ ቢታኮሱ ኢትዮጵያ በማታውቀው ምክንያት ችግር ውስጥ እንደምትወድቅ አንስተዋል።

ለጅቡቲ መንግስትና ህዝብ ታላቅ ምስጋና አቅርበው ከጅቡቲ በኩል ምን ስጋት እንደሌለ አመልክተው፣ በሌሎች ችግር ወደብ ቢስተጓጎል መድሃኒት፣ ነዳጅ፣ ማዳበሪያ ወዘተ ማስገባት አይቻልም። ይህን አስቦ አስቀድሞ መዘጋጀት ለጥያቄ የሚወርብ ጉዳይ እንዳልሆነም አመልክተዋል።

በዓለም ታላላቅ የሚባሉትን የቢዝነስ ተቋሞቻችንን በማጋራት የባህር መጠየቅ እጅግ ፍትሃዊ መሆኑን አብይ አህመድ አስምረውበታል። “አሜሪካ፣ ቻይና ድፍን አፍሪካ፣ መካከለኛው ምስራቅ አገራት ያነጋግሩንና ጥያቄያችሁ ፍትሃዊ አይደለም ካሉን እንተወዋለን” ብለዋል። ይህን ንፅፅር ያቀረቡት አብይ አህመድ ” እኛ በጥያቂያችን አናፍርም፤ የልጆቻችንን ህይወትና ወደፊት መታደግ ነው ዓላማችን” ሲሉ አቋሙ ታስቦበትና የወደፊቱን በማስላት የተያዘ መሆኑን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነቷ ቁርጥ ጉዳይ እንደሆነ ሲያስረዱ ሁሉም አግባብ ካልሆነ ” ቁጭ ብለን አንሞትም” አይነት መግለጫ ነው የሰጡት። በንጉሱ ዘመን ሃይል ያለው የኮንፌዴሬሽን ውል ሰነዱን ቀዶ፣ በፌዴሬሽን እንደተካው ያስታወሱት አብይ አህመድ “አቅም ያለው” ያን ታሪክ የማይደግምበት ምክንያት ሊኖር እንደማይችል አመላክተዋል። አያዘውም በቢዝነስ ህግ ሌሎች ቀይ ባህር ላይ እየተስተናገዱ ጉዳዩን ኢትዮጵያ ስታነሳው ከወረራና ” ደሃ ስለሆነች አይገባትም” ማለት ቁብ እንደሌለው ተናግረዋል።

“ኢትዮጵያ አሉ” አብይ አህመድ፣ “ዛሬ ኢትዮጵያ ከየትኛውም ጎረቤቶቿ ተነስቶ ያጠቃኛል በሚል የምትፈራው ሰራዊት የለም” በማለት ለፓርላማው ተናገሩ። ቀጠሉና ” አስተማማኝ ሃይል ተገንብቷል” አሉ። አብይ አህመድ ይህን ሲሉ በተዘዋዋሪ ለማን እንደሆነ ግልጽ ቢሆንም ስም አልጠሩም።

አንድ መቶ ሃያ ሚሊዮን ህዝብ ያላት፣ በሃያ ዓመት ውስጥ ሃያ እጥፍ ያደገ ገቢና ወጪ የምታስተናግድ አገር ከሳሃራ በታች ካሉ አገራት ትልቁን ኢኮኖሚ የምታንቀሳቅስ አገር፣ እንደሆነች የሚገልጹ የህግ ባለሙያዎች “ኢትዮጵያ የባህር በሯን ያጣችው በሴራ ነው። ማስመለስ የምትችልበት ህጋዊ አገባብ አለ” በሚል አብይ አህመድን ተከትለው ድምጻቸውን እያሰሙ ነው።

አብይ አህመድም የደገሙት ይህንኑ ነው። “ችግር ከመጣ፣ መድሃኒት ከጠፋ፣ ነዳጅ መግቢያ ካጣ … ከዚያ በሁዋላ ህግም ደንብም አይገዛንም” ሲሉ በዓለም የቢዝነስ ህግ መነጋገርና መፍትሄ ማበጀት ግዴታ እንደሆነ ገልጸዋል። አክለውም ይህ የባህር በር ጥያቄ ያለ ምንም ጥርጥር የሚሳካ እንደሆነ ” ያታሪክ ትራፊ” በሚል ለሚወቀሱት ቅምጥ የሚዲያ ተዋጊዎች ጭምር ገልጸዋል።

ቀደም ባለው ንግግራቸው አብይ አህመድ ” አልነጋገርም፣ አያገባኝም ማለት አይቻልም” የሚል ጥብቅ ማሳሰቢያ መስጠታቸው ይታወሳል። ዛሬ ለፓርላማ ሲገልጹ ” መነጋገር ከፈለጉ በየትኛውም የመረጡት ቦታ ለመነጋገር ዝግጁ ነን” ብለዋል። ጉዳዩ በአያገባኝም የሚቀጥል ከሆነ ለመነጋገር ፈቃደኛ መሆን ግዴታ እንዲሆን መረዳት የሚቻልበት አግባብ ሊፈጠር እንደሚገባ ባለሙያዎች እየገለጹ ነው።

አሰብን ለሻእቢያ አሳልፎ ለመስጠት የተነደፈው ሴራ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናው ” አሰብን ጊዜው ሲደርስ ከኢትዮጵያ ከመውሰድ ከሻዕቢያ መውሰድ ይቀላል” የሚል ህልም መነሻ እንደሆነ ምስክሮች መግለጻቸውን ጠቅሰን መዘገባችን ይታወሳል።

አሁን አሁን መንግስት በኤርትራ ሪፈረንደም አካሄድና የባህር በር ኪሳራ ዙሪያ የተደረጉ ስምምነቶችን ከምስክሮች፣ ከነበሩ ተሳታፊዎች፣ በወቅቱ ከነበሩና በአቋማቸው ሳቢያ መለስ ካስወገዷቸው የትህነግ አባላት እንዲሁም የጽሁፍ መረጃዎች፣ የተባበሩት መንግስታት ለአቶ መለስ የጻፈውን ደብዳቤ በማካተት ሰነዶችን ለታሪካና ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግ በየአየቅጣጫው ጥያቄ እየቀርበለት ነው።


Exit mobile version