Site icon ETHIO12.COM

በትግራይ መደበኛ ትምህርት ለማስጀመር እየተሰራ ቢሆንም ተቋማቱ መጎዳታቸውና መዘረፋቸው ቸግር ፈጥሯል

በትግራይ ” ህግ ማስከበር” በሚል መንግስት በወሰደው እርምጃ የትህነግ አቋም እንዳይመለስ ሆኖ መንኮታኮቱን በርካቶች ይመስከራሉ። ሆኖም ግን ከጦርነቱ ጎን ለጎን የሚሰሙት መረጃዎች ሕዝብን ግራ እያጋቡ መሆናቸውም የዛኑ ያህል እየተሰማ ነው። ዛሬ መንግስት ይፋ ያደረገው የትምህርት ዳግም ማስጀመር አጀንዳ ያነሳቸው ጉዳዮች በቀጥታ ባይሆኑም መነጋገሪያ እየሆኑ ነው።

የመንግስት ሚዲያዎች ዛሬ ትምህርት ሚኒስሬርን ጠቅሰው ይፋ እንዳደረጉት በትግራይ ክልል የተቋረጠውን ትምህርት ለማስጀመር ምክክር ተጀምሯል። በዚሁ አጀንዳ ስር ይፋ የሆነው በትግራይ ትምህርት ቤቶች መዘረፋቸው፣ ጉዳት የደረሰባቸው መሆኑ በቅድመ የመስክ ምልከታ መረጋገጡ ተዘግቧል።

ትግራይ ወደ መደበኛ ህይወት እንድትመለስ ከሚያስችሏትና ወደ መደበኛ ሕይወት ለመመለሷ ማሳያ ከሚሆኑት ጉዳዮች መካከል አንዱና ዋናው የትምህርት ቤቶች መከፈት በመሆኑ ዜና በበጎ ተወስዷል። ሰሞኑንን በይፋ እንደተሰማው ስልክና መብራት መልሶ የማስጀመሩ ስራ ተግባራዊ ሲሆን ጎን ለጎን ይፋ የሆነው የመሰረተ ልማት መውደም ነው።

ለትምህርት ቤቶች፣ ለቴሌና ኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት እንዲሁም ለመንገድና አየር ማርፊያዎች መውደም ምክንያት የሆነው ትህነግ እንደሆነ በምስል የተደገፈ መረጃ መቅረቡ አስገርሟል። ” ለትግራይ ህዝብ አልፋና ኦሜጋው እኔ ነኝ” የሚለው ትህነግ፣ የክልሉን መሰረተ ልማት እያወደመ ከተሞችን መሰናበቱ በአፍቃሪዎቹ ዘንዳ እንደ በጎ ታክቲክ ወይም ” አላደረገውም” በሚል ቢወሰድለትም፤ ትህነግን ሲቃወሙ በነበሩና ገለልተኛ አቋም በያዙ ወገኖች ግን ለጥፋቱ ቅድሚያ እንዲይዝ ሆኗል።

ዛሬ ትምህርት ሚኒስትርን ጠቅሶ ኢዜአ አንደዘገበው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አመራሮችና ባለሙዎች በትግራይ ክልል በቀጣይ ትምህርት ለማስጀመር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር አመራሮችና ባለሙያዎች ጋር መክረዋል።

” በክልሉ የሚገኙ የትምህርት መሠረተ-ልማትና ግብዓቶች በህወሃት የጥፋት ቡድን ጉዳት እንደደረሰባቸውና እንደተዘረፉ ለናሙናነት በተካሄዱ የመስክ ምልከታዎች እንደተረጋገጠም ተገልጿል” ሲል ያስታወቀው ዜናው በዝርዝር ቦታና አካባቢ ጠቅሶ አልስታወቀም።

“መማር-ማስተማር ሥራው በቅርብ ጊዜ ወደ ነበረበት እንዲመለስ የክልሉ መንግሥትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የሚያደርጉትን ጥረት ለማገዝ ቀጣይነት ያለው ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ሲሉ የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ ገልጸዋል” የሚለው የመንግስት ዜና በትግራይ የተቁረጠውን ትምህርት ለማስጀመር በርካታ ችግሮች ስለመኖራቸው አመላካች ጉዳዮችን አመላክቷል።

ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት የክልሉ የአንድ ዓመት በጀት ውስጥ አብዛኛው እንደባከነ፣ ባንኮች እንደተዘረፉ ይፋ ሆኗል። ከዚህም በተጨማሪ በክልሉ ረሃብ እንደነገሰ በስፋት እየተነገረ ነው። የዚህ ሁሉ ድምሩ የወደቀው መንግስት ላይ በመሆኑ ትግራይን ወደ ነበረችበት መመለሱ ቀላል እንደማይሆን በርካቶች እየጠቆሙ ነው።

Exit mobile version