Site icon ETHIO12.COM

በመቐለ ከተማ የካቲት 1 ቀን ትምህርት ይጀመራል፤ የሰላም ሚኒስትር እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ሁሉ ለማድረስ እየሰራ ነው

ከንቲባ አቶ አታክልቲ

በትግራይ ክልል በተካሄደው ሕግን የማስከበር እርምጃ እና በኮሮና ቫይረስ ምክንያት በመቐለ ከተማ ተቋርጦ የነበረው ትምህርት የካቲት 1 ቀን 2013 ዓ.ም እንደሚጀመር የከተማዋ ከንቲባ አስታወቁ።

ከንቲባ አቶ አታክልቲ ኃይለስላሴ በተለይ ለኢፕድ እንዳስታወቁት፣ በከተማዋ ትምህርት መጀመሪያ በኮሮና ምክንያት በኋላም በሕግ ማስከበር ዘመቻው ምክንያት ተቋርጦ መቆየቱን አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት የከተማዋ ሰላምና ፀጥታ የተረጋጋ በመሆኑና የኮሮና ቫይረስ ለመከላከያ የጥንቃቄ እርምጃዎችን በመውሰድ በሁሉም ደረጃ ባሉ የትምህርት ክፍሎች ከየካቲት 1 ቀን 2013 ዓ.ም አንስቶ ትምህርት መስጠት ይጀመራል ብለዋል።

በአሁኑ ወቅት በመቐለ ከተማ የሚገኙ የመንግሥት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት መደበኛ ሥራቸውን እያከናወኑ መሆኑን አስታውቀዋል።ወላጆች ልጆቻቸውን ከተጠቀሰው ዕለት ጀምሮ ወደ ትምህርት ቤት እንዲልኩም አቶ አታክልቲ ጥሪ አቅርበዋል።

 የትግራይ ክልልን ጨምሮ የሰብአዊ ድጋፍ በሚያስፈልጋቸው አካባቢዎች እየተሰራ ያለው ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የሰላም ሚኒስቴር ገለፀ። በመተከል ዞን ከሚገኙት 183 ቀበሌዎች ውስጥ ከሰላሳ ሁለቱ በስተቀር አብዛኛዎቹን ከታጣቂዎች የማጥራት ሥራ መሠራቱን አስታወቀ።

የሰላም ሚኒስትሯ ወይዘሮ ሙፈሪሃት ካሚል የአስቸኳይ ጊዜ ምላሽ ሰጭ የሚኒስትሮች ኮሚቴ እየተከታተለው የሚገኘውን ሰብአዊ ድጋፍና መልሶ ግንባታ ሥራን አስመልክቶ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አንዳስታወቁት፣ በትግራይ ክልል የሕግ ማስከበሩን ተከትሎ 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዜጎች የዕለት ደራሽ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው ታውቆ ድጋፉን ለማድረስ ጥረት እየተደረገ ነው።

ወይዘሮ ሙፈሪሃት

መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም ድጋፍ በማድረጉ ሂደት እየተሳተፉ ነው ያሉት ሚኒስትሯ፥ እስካሁን 1 ነጥብ 6 ሚሊየን ለሚሆኑት ዜጎች ከ305 ሺህ በላይ ኩንታል የእህል ድጋፍ መደረጉን አስታውቀዋል። 22 ሺህ ሜትሪክ ቶን እህል በጥምረት እና 69 ሺህ ሜትሪክ ቶን እህል ለሴፍቲኔት ተረጅዎች ለማድረስም በሂደት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል። እህል ነክ ያልሆኑ ድጋፎችም በስፋት እየደረሱ መሆኑን ገልፀዋል።

መንግሥታዊ አገልግሎቶችን የማስጀመር ሥራው ተጠናክሮ መቀጠሉን ያመለከቱት ወይዘሮ ሙፈሪሃት፣ 71 ሚሊየን ብር ወጪ ተደርጎ የመድሃኒት አቅርቦት ለማድረስ ጥረት መደረጉንና የውሃ መስመሮች እስከሚጠገኑ በቦቴ ውሃ ለማድረስ እየተሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል። ትምህርት ለማስጀመር በሂደት ላይ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሯ፥ የፀጥታ ሃይሉ እንዲጠናከርና ወደ ሥራ እንዲመለስ መደረጉ ውጤት እየታየበት መሆኑንም አመልክተዋል።

በተመሳሳይ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን በተፈፀመው ጥቃት ሳቢያ ለተፈናቀሉና ችግር ውስጥ ለሚገኙ ከ104 ሺህ በላይ ዜጎች የሰብአዊ ድጋፍ ለማድረስ እየተሰራ መሆኑንም የገለጹት ወይዘሮ ሙፈሪሃት፣ በዞኑ ከሚገኙት 183 ቀበሌዎች ውስጥ ከሰላሳ ሁለቱ በስተቀር አብዛኛዎቹን ከታጣቂዎች የማጥራት ሥራ መሠራቱን ገልፀዋል፤ በቀሪዎቹ ላይ የማጥራት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። ከማህበረሰቡ የተውጣጣ ሚሊሻ ለማደራጀት እየተሠራ መሆኑን ገልፀው፣ በቅርቡ 9 ሺህ የሚሆኑት ወደ ስልጠና ይገባሉ ብለዋል።

አዲስ ዘመን ጥር 27/2013

Exit mobile version