Site icon ETHIO12.COM

የሬዲዮ መገናዎችን ለትግራይ ልዩ ሃይል ያስታጠቁ፣ የሬዲዮ ግንኙነት ያቋረጡና ሰራዊቱን ያስመቱ ተጠርጣሪ መኮንኖች ፍ/ቤት ቀረቡ

እነሜጀር ጄኔራል ገ/መድህን ፍቃዴ የመከላከያ ሰራዊት ንብረት የሆነ በጀርባ ከ30 እስከ 40 ነጠላ ሬዲዮኖችን የሚያገናኙ 50 በጀርባ የሚያዙ የሬዲዮ መገናኛ ዎችን ለትግራይ ልዩ ሃይል መስጠታቸውን ጠቅላይ አቃቢ ህግ ገለጸ። ጠቅላይ አቃቢ ህግ ይህን የገለጸው ዛሬ እነ ሜጀር ጄኔራል ገ/መድህን ፍቃዴን ጨምሮ ሰባት ከፍተኛ የመከላከያ መኮንኖች ፍርድ ቤት በቀረቡበት ወቅት ነው።

በተለይም ሜጀር ጄኔራል ገ/መድህን ፍቃዴ የመከላከያ ሰራዊት ሬዲዮ መገናኛዎችን አውጥቶ ለትግራይ ክልል ልዩ ሃይል በመስጠትና እዛው በአካባቢው በአካል በመሄድ የሬዲዮ ሞገድ በማስተካከል ሰፊ ድጋፍ አድርጎ ሰራዊቱ ላይ ጥቃት እንዲደርስ አድርጓል ሲል ገልጿል። ዛሬ ፍርድ ቤት የቀረቡት ሜጀር ጄነራል ገ/መድህን ፍቃዴ ፣ሜጄር ጄነራል ይርዳው ገ/መድህን ፣ ብርጋዴል ጄኔራል ገ/ህይወት ሲስኖስ ፣ብርጋዴል ጄኔራል ኢንሶ ኢጃጆ ፣ ብርጋዴል ጄነራል ፍስሃ ገ/ስላሴ ፣ኮሎኔል ደሳለኝ አበበ እና ኮሎኔል እያሱ ነጋሽ ናቸው።

የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ወንጀል ምርመራ ቡድን ከዚህ በፊት በተሰጠው 14 የምርመራ ቀናት የተጠርጣሪዎችን የወንጀል ተሳትፎን ጨምሮ ያከናወነውን ምርመራ ውጤት ለችሎቱ አብራርቷል። ከመርመሪ ጋር አብሮ የቀረበው የፌደራል ጠቅላይ አቃቢ ህግም በተጠርጣሪዎች የተነሳ መቃወሚያ ላይ ምላሽ ሰቷል። መርማሪ ፖሊስ በሰራው ምርመራ ስራ 1ኛ ተጠርጣሪ ሜጀር ጄነራል ገ/መድህን ፍቃዴ የመከላከያ ሬዲዮ ግንኙነት ዋና መምርያ ሃላፊ ሆነው ሲሰሩ ጦርነት በህወሓት አመራሮች ከመጀመሩ በፊት እንዴት የሰሜን እዝ ተለይቶ መምታት እንደሚቻል እና የትግራይ ልዩ ሃይል እንዴት ተጠናክሮ ጥቃት መፈጸም እንደሚችል እቅድ ማዘጋጀቱን ገልጿል።

በተጨማሪም የመከላከያ ሰራዊት ሬዲዮ መገናኛዎችን አውጥቶ ለትግራይ ክልል ልዩ ሃይል በመስጠትና እዛው በአካባቢው በአካል በመሄድ የሬዲዮ ሞገድ በማስተካከል ሰፊ ድጋፍ አድርጎ ሰራዊቱ ላይ ጥቃት እንዲደርስ አድርጓል ሲል የተጠርጣሪውን የወንጀል ተሳትፎ ገልጿል። አራተኛ ተጠርጣሪ ብርጋዴል ጄነራል ኢንሱ ኢጃጆ በተመለከተም ፖሊስ ከ1ኛ ተጠርጣሪ ጋር በቀጥታ በስልክና በአካል በመገናኘት የሬዲዮ ግንኙነት ኮዶች እንዲቀየሩ ና ግንኙነቱ እንዲቋረጥ በማድረግ የራሱን የወንጀል ተባባሪዎች በመመደብ ድርጊቱ እንዲፈጸም ሲያመቻች እንደነበረ በምርመራ መለየቱ ተገልጿል።

5ኛ ተጠርጣሪ ብርጋዴል ጄነራል ፍስሃ ገ/ስላሴ በተመለከተም መርማሪው በደቡብ እዝ መረጃ ሃላፊ ሆነው ሲሰሩ ከ1ኛ ተጠርጣሪ ህገ ወጥ ትዛዝ በመቀበል የሬዲዮ ግንኙነቱን በማቋረጥ በመከላከያ ሰራዊት ላይ የደረሰው ጉዳትን የደቡብ እዝ አውቆ እርዳታ እንዳያደረግ እንዲሁም ከማእከላዊ አመራሮች ግንኙነቱ እንዲቋረጥ የሬዲዮ ባለሙያዎችን በመመደብ ሲያመቻች እንደነበረ በምርመራው መለየቱን ጠቅሷል።

የምእራብ እዝ ኦፕሬሽን ም/አዛዥ የነበሩት ሜጄር ጄነራል ይርዳው ገ/መድህን፣የደቡብ እዝ የሰው ሃብት ልማት ሃላፊ የነበሩት ብርጋዴል ጄነራል ገ/ህይወት ሲስኖስ እና ፣ የመከላከያ ጠቅላይ ኢታማዡር ሹም ልዩ ረዳት የነበሩት ኮሎኔል ደሳለኝ አበበ እንዲሁም በደቡብ እዝ 33ኛ ክፍለ ጦር ዋና አዛዠ የነበሩት ኮሎኔል እያሱ ነጋሽ ከ1ኛ ተጠርጣሪ ጋር በመሆን በህቡዕ በመደራጀት በአካል እና በስልክ በመገናኘት ጥቃቱ በምን አግባብ እና እነማን ሊፈጽሟቸው እንደሚችሉ በመለየት ሰዎችን ሲመድቡና ሲያመቻቹ የነበሩ መሆናቸውን ባቀረበው የወንጀል ተሳትፏቸው ማብራሪያ አመላክቷል።

ወንጀሉ ሲፈጸም በቦታው የነበሩ ተጨማሪ ምስክሮች ቃል ለመቀበል ቀሪ የምርመራ ስራዎችን ለማምጣት ፍርድ ቤቱ ከግምት ወስጥ አስገብቶ ተጨማሪ 14 ቀናት እንዲሰጠውም ጠይቋል። ተጠርጣሪዎቹ ከጠበቆቻቸው ጋር የቀረቡ ሲሆን ጠበቆቻቸውም በምርመራው አብዛኛውን ስራ ተሰርቷል÷ ስለዚህ ተጨማሪ ጊዜ መጠየቁ አግባብ አይደለም ሲሉ መቃወሚያ አሰምተዋል።

ወንጀሉ ተፈጽሟል አልተፈጸመም የሚለው በዋና ክርክር የሚታይ ስለሆነ ለተጠየቀው ምክንያት ብቻ ደንበኞቻቸን ታስረው መቆየት የለባቸውም 90 ቀናት ታስረዋል ተመጣጣኝ ዋስትና ተሰጥቷቸው በዋስ ይውጡ ሲሉም የዋስትና ጥያቄ አቅርበዋል። በመከራከሪያ ነጥባቸው ላይ ምላሽ የሰጠው አቃቢ ህግም ከተፈጸመው ወንጀል እና ከደረሰው ጥቃት አንጻር 90 ቀን መታሰር ምንም ማለት አደለም ሲል ምላሽ ሰቷል።

አብዛኛወን ስራ ተሰርቷል የተባለውም ቢሆን ወንጀሉ ሰፊ በመሆኑና ሰፊ ምርመራ ነው እየተከናወነ ስላለ ግዳጅ ላይ ያሉ በወቅቱ ወንጀሉ ሲፈጸም የነበሩ ምስክሮችን ቃል መቀበል አለብን ብሏል አቃቢ ህግ በምላሹ። በአሁን ወቅት በመካላከያ ሰራዊት ፣በፖሊስ እና በአቃቢ ህግ የተዋቀረ ቡድን ቦታው ሄዶ ሰፊ ምርመራዎችን እያከናወነ ሰፊ ማስረጃዎችን እየሰበሰበ መሆኑን ጠቅሷል። ተጠርጣሪዎቹ ከ30 እስከ 40 ነጠላ ሬዲዮዎችን የሚያገናኙ 50 በጀርባ የሚያዙ ሬዲዮ መገናኛዎችን መከላከያ ሰራዊት ላይ ጥቃት እንዲፈጸም ለትግራይ ልዩ ሃይል ሰተው መገኘቱንም ገልጿል። ከደቡብ ወደ ወሎ በዝውውር የሚሄዱ መከላከያ ሰራዊቶችን ትጥቅ እንዳይዙ በማድረግ የራሳቸው ያደራጇቸውን ትጥቅ አስታጥቀው አሳፍነዋቸው እንደነበር አቃቢ ህግ በምላሹ አስታውቋል።

እንደ ኤፍቢሲ ዘገባ፤ የሁለቱን ክርክር ያዳመጠው ችሎቱ ተጨማሪ ምርመራ ያስፈልጋል ሲል 14 የምርመራ ቀናትን የፈቀደ ሲሆን ውጤቱን ለመጠባበቅ ለየካቲት 11 ቀን 2013 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰቷል።

Exit mobile version