Site icon ETHIO12.COM

ቤኒሻንጉል- 34 ሺህ የሸፈቱ ጉምዞች ወደ መኖሪያቸው ተመለሱ፤ 151 ቀበሌውች አዲስ አመራር ሰየሙ፤ 50 ሽፍታው የያዛቸው ቀበሌዎች ተመለሱ …

ግብረ ሃይሉ በመተከል ዞን ዘላቂ ሠላምና መረጋጋት ማምጣት የሚያስችል ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን ሲናገር ከዚህ በፊት ተደብቆ የነበሩ የአሃዝ መረጃዎችን በማጣቀስ ነው። አሃዞቹ እንደሚያሳዩት 151 ቀበሌውች አዲስ አመራር ሰይመዋል። 32 ቀበሌዎች ይቀራሉ። 50 ሽፍታው ይዟቸው የነበሩ ቀበሌዎች በግብረሃይሉ አማካይነት መንግስት ተቆጣጥሯቸዋል። የኢትዮጵያ ፕሪሰ ድርጅት ይፋ ያደረገው ከታች ያለው ዜና እንደሚያሳየው ክልሉ መንግስት እጅ ነበር ማለት አይቻልም። ለዚህ ይመስላላ 10 ሺህ ሚሊሻዎች እንዲሰለጥኑ እየተደረገ ነው። ሙሉ ዜናውን ከስር ያንብቡ

(ኢ ፕ ድ ) የመተከል የተቀናጀ ግብረ ሀይል የፀጥታና ህግ ማስከበር ስራውን ከተረከበ በኋላ በዞኑ ዘላቂ ሠላምና መረጋጋት ማምጣት የሚያስችል ውጤት እያስመዘገበ መሆኑ ተገለጸ፡፡ግብረ ሃይሉ ቀሪ ሽፍታውን የማፅዳት ስራ ለማከናወንና ተፈናቃዮችን ወደ ቀያቸው ለመመለስ የ15 ቀናት ዕቅድ አስቀምጧል፡፡

በመተከል በለስ ከተማ ሲካሄድ የቆየው ከወረዳ እስከ ዞን ያሉ የግብረ ሃይሉ አመራሮችና አባላት ግምገማ ተጠናቋል፡፡ሽፍታው ከሚንቀሳቀስባቸው 32 ቀበሌዎች ውጭ በሚገኙ 151 ቀበሌዎች የመንግሥት መዋቅር በአዲስ መልክ እንዲደራጅ መደረጉ ተገልጿል፡፡በሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ በልጅጌ ግብረ ሃይሉ መተከልን ከተረከበ በኋላ ከህዝቡ ጋር ባካሄደው ውይይት ሽፍታው የማንንም ብሄር እንደማይወክል መግባባት ተፈጥሯል ብለዋል፡፡

ግብረ ኃይሉ ከማኅበረሰቡ ጋር ያደረገው ውይይትና ተጨማሪ ስራዎች ውጤት በማስመዝገባቸው ጫካ ገብተው የነበሩ 34 ሺህ የጉምዝ ማኅበረሰቦችን ወደ ቀያቸው መመለስ እንደተቻለ አስታውቀዋል፡፡ታስበው የነበሩ ግጭቶችም ከህብረተሰቡ ጋር በተደረገው ወይይት መክሸፋቸውን ነው አቶ ተስፋዬ የተናገሩት፡፡በዚህም ሽፍታውን ከህበረተሰቡ በመነጠል በጋራ በተወሰደው እርምጃ በሽፍታው ስር የነበሩ 50 ቀበሌዎችን ወደ ሠላም ቀጣና መመለስ ተችሏል ብለዋል፡፡

የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን የመተከል ጉዳይ የህዝብ ለህዝብ ግጭት ሳይሆን ፖለቲከኞች ለርካሽ የፖለቲካ ትርፍ የፈጠሩት ሽኩቻ ነው ብለዋል፡፡በግጭቱ ተሳታፊ የሆኑ በተለይ በዞንና በክልል ደረጃ ያሉ የስራ ሃላፊዎች ከዚህ እኩይ ድርጊታቸው መቆጠብ እንዳለባቸውም አሳስበዋል፡፡የግብረ ሃይሉ መሪ ሌተናል ጄኔራል አስራት ዴኔሮ ከቀበሌ እሰከ ዞን ያለውን አደረጃጀት ለውጥ ማምጣት በሚችል መንገድ ማደራጀት ጀምረናል ብለዋል።

“ተፈናቃዮች ወደ ቀድሞ ቀያቸው ሲመለሱ አስተማማኝ ሠላም እንዲሰፍን የአካባቢውን ህዝብ የሚመስል የሚሊሻ አደረጃጀት ተፈጥሯል፤ ወደ 10 ሺህ የሚጠጉ የሚሊሻ አባላትም ከዛሬ ጀምሮ የመጀመሪያ ዙር ስልጠና ይወስዳሉ” ብለዋል፡፡ሽፍታው የሚንቀሳቀስባቸውና የጸጥታ ስጋት ያለባቸው 32 ቀበሌዎች በሚቀጥሉት 15 ቀናት ሙሉ በሙሉ ከሽፍታው እንቅስቃሴ ነጻ እንዲሆኑ አመራሩ ታች ድረስ ወርዶ መስራት እንዳለበትም አሳስበዋል፡፡

የሠላም ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ስዩም መስፍን ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው ከመመለሳቸው በፊት የአካባቢው ሠላም አስተማማኝ መሆኑን ማረጋገጥ እንደሚገባም አመልክተዋል፡፡ተፈናቃዮች በሚቋቋሙበት ጊዜ የሚፈጠረውን ውዝግብ ለመፍታት አስቀድሞ ትክክለኛ ቁጥራቸውን መለየት እንደሚገባ ገልጸው፤ለዚህ ደግሞ የሠላም ሚኒስቴር ከሚመለከታቸው ጋር ይሰራል ብለዋል። በሚኒስትር ማዕረግ የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ በልጅጌም ተፈናቃዮችን ለመመለስ ማወያየት፣ የዕርቀ ሠላም ስራና ሌሎችም ቅድመ ሁኔታዎች እንደሚሟሉና ያ ሳይሆን የመመለሱ ስራ እንደማይሰራ ማረጋገጣቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

Exit mobile version