Site icon ETHIO12.COM

ትራምፕ የካፒቶሉን ነውጥ አነሳስተዋል መባሉን ጠበቆቻቸው ካዱ

የካፒቶሉን ሂል ነውጥ አነሳስተዋል በሚል ክስ የቀረበባቸው የቀድሞው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕን አስመልክቶ ምላሽ የሰጡት ጠበቆቻቸው ደጋፊዎቻቸው በራሳቸው ፈቃድ ነው ሁከቱን ያስነሱት በማለት ትራምፕ ተሳትፎ የላቸውም ሲሉ ክደዋል።

በትናንትናው ዕለት በነበረው ቅድመ- የፍርድ ሂደት የትራምፕ ጠበቆች ነውጡ ከቀናት በፊት ታቅዶና በደንብ ተደራጅተውበት እንደነበር የፌደራል ምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ) መረጃዎችን በመጥቀስ አስረድተዋል።

ይህም ማለት ትራምፕ ነውጡን አላነሳሱም በማለት ይከራከራሉ።

ከዚህም በተጨማሪ የፍርድ ሂደቱ ኢ-ህገ መንግሥታዊ ነው በማለት የጠቀሱ ሲሆን ለዚህም እንደ ምክንያትነት የሚያነሱት ከስልጣን ተነስተው እንደ ማንኛውም ዜጋ እየኖሩ ያሉ ናቸው ጉዳያቸው በምክር ቤቱ እንዴት ይታያል ሲሉ ይጠይቃሉ።

ታህሳስ 28፣ 2013 ዓ.ም የትራምፕ ደጋፊዎች የህግ መምሪያ ምክር ቤት እንደራሴዎች ውይይት እያደረጉ በነበረበት ወቅት ሰብረው በመግባት ነውጥ አስነስተዋል ተብሏል።

ዶናልድ ትራምፕ ሁከቱና ነውጡ ከተነሳ ከሳምንት በኋላ በስልጣን ላይ እያሉ ሁለት ጊዜ እንዲከሰሱ የተወሰነባቸው ወይም ኮንግረሱ በወንጀሎች የጠየቃቸው የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት ሆኑ

የትራምፕ በምክር ቤቱ የሚኖራቸው የፍርድ ሂደት በዛሬው ዕለት ይጀመራል።

ጠበቆቻቸው የፍርድ ሂደቱን “ፖለቲካዊ ቲያትር” በማለት የጠሩት ሲሆን ይህ “አሳፋሪ የፖለቲካ ድርጊት” ተቃዋሚዎችን ዝም ለማሰኘትና ፓርቲው ላይ ያነጣጠረ የዲሞክራቶች ሴራ ነው ይላሉ።

“የክሱ ሂደት በጭራሽ ከፍትህ ጋር የተያያዘ አይደለም” በማለት በመግለጫቸው አስፍረዋል።

ዲሞክራቶች በበኩላቸው ለጆ ባይደን ስልጣን እንደማያስረክቡና ለህዝቡ መታገል አለባችሁ በማለት ያስተላለፉት ቃል ለነውጠኛ ደጋፊዎቻቸው መነሳሳትን ፈጥሮላቸዋል በማለት ይከራከራሉ።

ጠበቆቻቸው በበኩላቸው የመናገር ነፃነታቸውን ከማስጠበቅ ባለፈ ምንም አላደረጉም ቢልም ክሳቸውን በበላይነት እያየ ያለው የምክር ቤቱ አካል በበኩሉ “የአሜሪካን ህዝብ ክደዋል። ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር እንዳይኖር እክል ፈጥረዋል። ይህ ደግሞ በመሪዎች ታሪክ ተፈፅሞ የማያውቅ ህገ መንግሥቱን የሸረሸረ ወንጀል ነው” ብሏል።

የቀድሞው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከወር በፊት ነበር በዋይት ሃውስ አቅራቢያ ለነበሩ ሰልፈኞች “በሰላማዊና በአርበኝነት” ድምፃቸው እንዲሰማ እንዲያደርጉ ጥሪ ያስተላለፉት።

ነውጠኛ ሰልፈኞቹ ወደ አሜሪካው ካፒቶል ህንፃ እየተቃረቡ ነበር ተብሏል። የቀድሞው ፕሬዚዳንት አክለውም “በእልህ እንዲታገሉም” ለደጋፊዎቻቸው ተናግረዋል።

በዚህም የተነሳ ነውጡን አነሳስተዋል በሚል ክስ የተመሰረተባቸው ሲሆን ትራምፕ የምስክርነት ቃሌን አልሰጥም ብለዋል።

በወቅቱ በተነሳው ሁከት አራት ተቃዋሚዎች ሲገደሉ በቦታው የነበረ የካፒቶል ፖሊስም ተገድሏል። ፖለቲከኞቹም ተደብቀው ነበር።

bbc Amharic

Exit mobile version