Site icon ETHIO12.COM

ሴኔቱ ዶናልድ ትራምፕ ላይ ክስ የመመስረቱ ሂደት ሕገ መንግሥታዊ ነው አለ

የአሜሪካ ሴኔት የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ላይ ክስ መመስረቱ ሕገ መንግሥታዊ ነው በማለት የክስ ሂደቱን አስቀጠለ።

የትራምፕ ጠበቆች በበኩላቸው ዶናልድ ትራምፕ ዋይት ሃውስን ከለቀቁ በኋላ መሰል ክስ ሊቀርብባቸው አይችልም ሲሉ ተከራክረዋል። ይሁን እንጂ 56-44 በሆነ የድምጽ ብልጫ የቀድሞ ፕሬዝደንት ላይ ክስ የመመስረቱ ሂደት ድጋፍ አግኝቷል። ዶናልድ ትራምፕ ባሳለፍነው ወር ደጋፊዎቻቸው በካፒቶል ሂላ ላይ ጉዳት እንዲያደርሱ አመጽ ቀስቅሰዋል በሚል እየተወነጀሉ ነው።

ትራምፕ ምንም አይነት ማረጋገጫ ሳያቀርቡ ምርጫው ተጭበርብሯል ሲሉ መቆየታቸው ይታወሳል። ትራምፕን እየከሰሱ የሚገኙት ዲሞክራቶች ሂድቱን በኤግዚቢትነት ያቀረቧቸውን ተንቀሳቃሽ ምስሎች በማሳየት ጀምረዋል።

በተንቀሳቃሽ ምሰሉ ትራምፕ ደጋፊዎቻቸው ወደ ካፒቶል ሂል እንዲሄዱ ‘ሲያነሳሱ’ እና በሺዎች የሚቆጠሩ የትራምፕ ደጋፊዎች ካፒቶል ሂልን ሰብረው ሲገቡ፤ በንብረት እና በጸጥታ አስከባሪዎች ላይ ጉዳት ሲያደርሱ ያሳያል።

ዴሞክራቶች ባቀረቡት ተንቀሳቃሽ ምስል ላይ ትራምፕ ደጋፊዎቻቸው ‘እስከመጨረሻው እንዲታገሉ’ መልዕክት ሲያስተላልፉ፤ ይህን ተከትሎም በካፒቶል ሂል ላይ ጉዳት ሲደርስ አስመልክተዋል።

ዲሞክራቱ ጄሚ ራስኪን፤ ይህ ተግባር ትራምፕን በወንጀል ማስጠየቅ አለበት ብለው ተከራክረዋል። “ይህ የአሜሪካ የወደፊት እጣ መሆን የለበት። በመንግሥታችን ላይ አመጽ የሚቀሰቅስ ፕሬዝደንት ሊኖረን አይገባም” ብለዋል።

የቀድሞ ፕሬዝደንት ትራምፕ ጠበቆች በበኩላቸው፤ ዶናልድ ትራምፕን በዚህ ሂደት ውስጥ ማሳለፍ ሕገ መንግሥታዊ አይደለም በማለት ተከራክረዋል። ዲሞክራቶችም ይህን እያደረጉ ያሉት ፖለቲካዊ ፍላጎታቸውን ለማሳካት ነው ብለዋል። 56-44 የሚለው የድምጽ ውጤት ስድስት የትራምፕ ፓርቲ አባላት የሆኑ ሪፐብሊካኖች ከዲሞክራቶች ጎን በመሆን ድምጽ መስጠታቸውን ያመላክታል።

በትራምፕ ላይ ክስ ለመመስረት 100 መቀመጫ ባሉት ሴኔት ውስጥ 2/3ኛ ድጋፍ ያስፈልጋል። ትራምፕ ላይ ክስ እንዲመሰረት ከተወሰነ ዶናልድ ትራምፕ ወደፊት የፖለቲካ ተሳትፎ አድርገው ስልጣን እንዳይዙ ሊደረጉ ይችላሉ።

የምስሉ መግለጫ,በካፒቶል ሂል የነበረው አመጽ

በቀጣይ ምን ይፈጠራል?

በትራምፕ ላይ ክስ እንዲመሰረት የሚጠይቁት ዴሞክራቶችም ሆኑ የትራምፕ ጠበቆች ለአንድ ተጨማሪ ቀን መከራከሪያ ነጥቦቻቸውን ማቅረባቸውን ይቀጥላሉ። በሴናተሮች በኩል ለሚነሱ ጥያቄዎች ዴሞክራቶች እና የትራምፕ ጠበቆች ምላሽ ይሰጣሉ። ዴሞክራቶቹ የዓይን ምስክሮችንም ቃል ሊያሰሙ ይችላሉ። እስከ መጪው ሰኞ ድረስ ትራምፕ ክስ እንዲመሰረትባቸው አልያም ነጻ እንዲወጡ ሴኔቱ ውሳኔ ማስተላለፉ አይቀርም ተብሏል።

bbc amaharic

Exit mobile version