Site icon ETHIO12.COM

ሱዳን የዕርቅ ጥያቄ አቀረበች ” ከኢትዮጵያ ጋር መረዳዳታን መልካም ግንኙነት እንሻለን”

ኢትዮጵያ በወረራ የተወሰደባትን መሬት በሃይል ማስመለሷን ተከትሎ ሱዳን ከኢትዮጵያ ጋር ድርድር እንደምትፈልግ አስታወቀች። የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርን ጠቅሶ ብሉምበርግ እንደዘገበው፣ ሚኒስትሩ ” ከኢትዮጵያ ጋር መልካም ግንኙነትና ትብብር እንፈልጋለን” ብለዋል።

ማርያም ሳዲቅ መሃዲ ዛሬ ደቡብ ሱዳን በተገኙበት ወቅት ለሪፖርተሮች እንዳስታወቁት አገራቸው የድንበር አለመግባባቱን በቀጠናው ባሉ አሸናጋዮች አማካይነት እልባት ለመስጠት ሙሉ ፈቃደኛ መሆኗን አመልክተዋል። ከቀናት በፊት ግን ” የያዝኩትን መሬት ለቅቄ አልወጣም፣ የማይታሰብ ነው” ትል ነበር።

እጅግ ታጋሽነት የተሞላው አካሄድ እንደሚከተሉ የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ከትዕግስት ውስጥ የሚወጣው ሃይል ግን ሳያደቅ እንደማይመለስ ጠቅሰው ኢትዮጵያ በህግ ማስከበር ተወጥራ ባለችበት ወቅት ሱዳን ለፈጸመችው የድበር ወረራና ጥፋት ብድሯን እንደምታገኝ ተናግረው ነበር።

ይህንኑ መሰረት ባደረገ የብሄራዊ አገር ደህንነት ዋና ዳይሬክተር አቶ ተመስገን ዛሬ ጀግናው መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ ልዩ ሃይል፣ ሚሊሻውና ፋኖ በህብረት ወራሪው የሱዳን ሃይል ክፉኛ መደቆሱን፣ በመኪና መጥቶ ከሙትና ምርኮ የተረፈው በግሩ ፍርጥጦ መሸሸሹን በፊስ ቡክ አምዳቸው ” ድሉ ተደገመ” በሚል ይፋ አድርገው ነበር። እሳቸው ይህን ባሉ ሰዓታት ውስጥ ሱዳን የእርቅ ጥያቄ ማቅረቧ ዱላው ከባድ ስለመሆኑ ማሳያ ነው ተብሏል።



ሱዳን ትሪቡን በትናንትናው እለት ኢትዮጵያ ሃይል ተጠቅማ የተወሰዱባትን ቦታዎች ማስመለሷን የአገሪቱን ከፍተኛ ባለስልጣናት ጠቅሶ አስታውቆ ነበር። ሱዳን ኤትዮጵያና ኤርትራ አንድ ላይ ሆነው እንደወጓትና የኤርትራ ሰራዊት የኢትዮጵያን መለያ ልብስ ለብሶ ድንበር አካባቢ እንደሚታይ በመጠቆም ጉዳዩን አቅጣጫ ለማስቀየር ሞክሮ ነበር።

ይህንኑ የሱዳን አቤቱታ ተከትሎ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ለሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትርና የጦር ሃይሉ መሪና የአገሪቱ የፊት ሰው የጽሁፍ መልዕት በማስያዝ ባለስልጣኖቻቸውን ልከው ነበር። መልዕክተኞቹ ኤርትራ በጉዳዩ እንደሌለችበት አስታውቀው ሱዳን ጉዳዩን በእርቅ እንድተፈታ አሳስበውና መክረው ተመልሰዋል።

ከዚህ ሁሉ በሁዋላ የድሉን ዜና ለማብሰር ግንባር ቀደም የሆኑት የቀድሞ የአማራ ክልል መሪ አቶ ተመስገን፣ ” የሱዳን መከላከያ ሰራዊት በማን አለብኝነት የአማራን መሬት ወረረ፣ ቀጥሎም የአማራን ንብረት አወደመ። ጀግናው የአማራ ልዩ ኃይል ሚሊሻ እና ፋኖ ከሃገር መከታው መከላከያ ጋር በመሆን ከህወሓት ያልተማረውን የሱዳን መከላከያ በሚገባው ቋንቋ አናግሮ በርካታ መኪኖችን ነጥቋል፣ ብዙዎችንም ማርኳል፣ ከፊሎቹም ህይዎታቸው ሲያልፍ የተወሰኑት እግሬ አውጭኝ ብለው በመኪና መጥተው በእግራቸው ፈርጥጠዋል” ነበር ያሉት።

አቶ ተመስገን አያይዘም ” የአማራ ልዩ ኃይል እና ፋኖ በየትኛውም ግዳጅ የላቀ ውጤት ያስመዘግባል፣ አሁንም ይህ ድል ብርቁ ያልሆነው ልዩ ሃይል ሚሊሻ እና ፋኖ ለቀጣይ ግዳጅ ዝግጅቱን ጨርሶ የመጨረሻዎ ፊሽካ እስክትነፋለት በመጠባበቅ ለይ ይገኛል! በመጨረሻ የሰይጣን አመለካከት ያላችሁ ከዚህ አረመኔያዊ ተግባር ካልተቆጠባችሁ የመልስ ምቱ ከባድ ነው። በአለም ታሪክ የተጨቆነ ህዝብ ተሸንፎ አያውቅም! እየሞተ የሚፈራ ጀግና ህዝብ ሲኖረህ የትኛውም ትግል ሊያስፈራህ አይችልም” ማሳሰቢያ ሰጥተዋል።


Exit mobile version