Site icon ETHIO12.COM

ትህነግ ከትግራይ አስተዳደር ጋር መሳሪያ አስረክቦና ጦሩን በትኖ እንዲደራደር ታስቧል፤ መንግስ የተረፈውን ሃይል ሊያጸዳ ነው

ራሱን የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር / ትህነግ ብሎ የሚጠራው ቡድን አሁን ካለበት ዋሻ በመውጣት ወደ ሰላማዊ ውይይት ለመውጣት በውጭ አገር ባሉት አመራሮቹ በኩል ድርድር አንዲደረግ እየገፋ መሆኑ ተሰማ። አንድ ታዋቂ የአሜሪካ ሴናተርና የትህነግ ወዳጅ ዲፕሎማት በዝርዝር ጉዳዮች ላይ እየሰሩ መሆኑ ታውቋል።

የኢትዮ 12 የአሜሪካ ተባባሪ እንዳለው ለጊዜው ስማቸውን ከማይጠቅሳቸው ሲናተር ጋር ግንኙነት ያላቸው ዜናውን ጠቁመዋል። እንደ ዜናው ከሆነ የትህነግ የውጭው ክንፍ ፍላጎቱ ድርድሩን ከመንግስት ጋር ማድረግ ነበር። ለጊዜው ስማቸው የማይጠቀሰው ሲናተር መንግስትን አነጋግረው ” ከቶውንም አይቻልም” የሚል ምላሽ ካገኙ በሁዋላ ነው ትህነግ ከትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር ሊደራደር የሚችልበትን አግባብ ሁለተኛ አማራጭ አድርገው የያዙት።

በዚህ መሰረት መንግስት ለሁለተኛው አማራጭ ፈቃድ ሰጥቶ ትግራይን እያስተዳደረ ያለው ጊዜያዊ አስተዳደር ከትህነግ ጋር እንዲደራደር መደላድል እንዲፈጠር ነው እየተሰራ ያለው። ለመንግስት እጅግ ቅርብ የሆኑ ወገኖችን በዚሁ ጉዳይ አማክረው የማግባባት ስራ እንዲሰሩ የተጠየቁት ክፍሎች ” ትህነግ የታጠቀውን መሳሪያ አስረክቦ፣ ሰራዊቱን በትኖ ለመነጋገር ከወሰነ መንግስት ፈቃድ እንዲሰጥ ለማግባባት እንሞክራለን” ማለታቸውን ረዳታችን ጠቁሟል።

ከትህነግ የውጭ ክንፍ አመራሮች ጋር የቅርብ ግንኙነት ያላትን ጠቅሶ የአሜርካን ተባባሪያችን እንዳስታወቀው ትህነግ መሳሪያውን ፈቶና ወታደሮቹን በትኖ ለመነጋገር ፈቃደኛ እንደሚሆን የሚያረጋግጥ ምላሽ ተሰጥቷል። በጎን በተደረገ ውይይት ከመንግስት በኩል ፈቃደኛነቱ ካለ አሜሪካ ማንኛውንም ጫና እንደምታደርግ ስለሚታመንና ትህነግ አሁን ባለው አቋቋሙ ጫና ቢደረግበትም ከመቀበል ውጭ አማራጭ እንደምይኖረው ተመልክቷል።

የህዳሴው ግድብ እውን እየሆነ መምጣትን ተከትሎ ትግራይን በመንተራስ ኢትዮጵያ ላይ የሚደረገው ጫናና ፈርደ ገምድል ዳኝነት ለማርገብ ሩጫ በሚደረግበት በአሁኑ ወቅት፣ የትህነግ የውጭው ክንፍ ድርድር ለማድረግ መንቀሳቀሱ በግብጽ በኩል ምን ስሜት ሊፈጥር እንደሚችል እስካሁን የተሰማ ነገር የለም። ፖለቲካውን ባለመረዳት ድጋፍ የሚሰጡ የትህነግ ወዳጆች በጉዳዩ ዙሪያ ምን አስተያየት እንደሚኖራቸው ከወዲሁ የታወቀ ነገር የለም።

በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው ባለስልጣን የትጨበጠ መረጃ እንደሌላቸው በመጠቆም የክልሉን አስተዳደር መጠየቁ እንደሚሻል ተቁመዋል። የክልሉን አስተዳደርና በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ለማነጋገር ሞክረን አልተሳካም።

ይህ በንዲህ እንዳለ መንግስት ቀጣይ የማጽዳት ዘመቻ አካል ነው የተባለ የተመረጠ ኦፐሬሽን ለማድረግ ዝግጅት ላይ መሆኑ ተሰምቷል። የተሸራረፈው ሃይል እየተገፋ ወደ አንድ አካባቢ እንዲሰባሰብ ሲደረግ መቆየቱ ቀጣይ ዘመቻ ስለመኖሩ አመላካች እንደሆነ ግምት የሚሰጡ አሉ።

Exit mobile version