Site icon ETHIO12.COM

ትህነግ ሲከስም፣ እነ ጃዋር ምግብ መብላት መጀመራቸው ይፋ ሲሆን ልደቱ አያሌው “ፖለቲካ በቃኝ”ብለው ተሰናበቱ

በስተመጨረሻ ” መንግስት የለም” የሚለውን ትግል ተቀላቅለው የነበሩትና፣ ትህነግ ባስቀመጠው የትግል ስልት የማስተባበር ስራ ሲሰሩ እንደነበር በመግለጽ ክስና ወቀሳ ሲሰነዘርባቸው የነበሩት አቶ ልደቱ አያሌው በድንገት ከፖለቲካ በበቃኝ መገለላቸው ተሰማ። ውሳኔያቸው ክትህነግ ህልውና መክሰማና ከነ ጃዋር ምግብ መብላት መጀመር ጋር መያያዙ ውሳኔያቸውን የተስፋ መቁረጥ አስመስሎባቸዋል።

ጥሩ ተነጋሪ የሚባሉት ልደቱ አያሌው በቅርቡ ተከሰው በነበሩበት ወቅት የተገኘባቸውን ሽጉጥ ከድህንነት መስሪያ ቤት የተሰጣቸው መሆኑንን መግለጻቸው፣ በድህንነት መስሪያ ቤት ውስጥ በሂሳብ መዝገብ ወጪ እየተደረገ ደሞወዝ ይከፈላቸው እንደነበር ይፋ መሆኑ ” ቀድሞም ትህነግ ነበሩ” የሚለውን ወቀሳ አጠናክሮባቸው ነበር።


ጃዋር “የአንድነት ኃይሎች ከዱኝ”


ቀደም ሲል ህግ ተጥሶም ቢሆን ምርጫ መደረግ እንደሌለበት ሲሞግቱ የነበሩት አቶ ልደቱ፤ ትህነግ መቀለ ሆኖ “ከመስከረም 30 በሁዋላ ቅቡል መንግስት የለም” የሚል አዋጅ ካሰማ በሁዋላ ” የሽግግር መንግስት ይቋቋም ” በሚል የመሃል ፖለቲካውን ለመምራት ከነ ጃዋር መሐመድ ጋር ግንባር ገጥመው እንደነበር ይታወሳል። በወራት እድሜ ውስጥ ለተቀያየረው አቋማቸው በወጉ ተጠይቀው ምክንያታቸውን ሲያስረዱ ያልተሰሙት አቶ ልደቱ፣ ዛሬ ባሰራጩት ሰፊ ጽሁፍ ራሳቸውን ከፖለቲካ ማሰናበታቸውን አስታውቀዋል።

“በመጨረሻም ከአቅም በላይ በሆነ የጤና ምክንያት ቢሆንም ሀገራችን ከመቼውም ጊዜ በላይ ዋጋ የሚከፍልላት ዜጋ በሚያስፈልጋት በአሁኑ ወቅት ለጊዜውም ቢሆን ከትግል ተሳትፎዬ ለመታቀብ በመገደዴ፥ የትግል አጋሮቼንና የዐላማ ደጋፊዎቼን ሁሉ ከልብ ይቅርታ እጠይቃለሁ” ያሉት አቶ ልደቱ፣ ስንብቱን የመረጡት በጤና እክል የተነሳ ነውልል

“..ከእኔ ብዙ እንደምትጠብቁና ለእኔ ለራሴ እንደሆነብኝ ሁሉ ለእናንተም ይህ ክስተት ድንገተኛ መርዶ እንደሚሆንባችሁ ስለምገነዘብ ነው። ወደፊት የጤና ሁኔታዬ ተሻሽሎ እስከመጨረሻው በፖለቲካ ሒደቱ ለመቀጠል ለራሴ የገባሁትን ቃል ለመፈጸም ፈጣሪ ዕድል እንደሚሰጠኝ ተስፋ እያደረግኹ ሀገራችን ኢትዮጵያ መልካሙ ሁሉ እንዲገጥማት ያለኝን ልባዊ ምኞት በዚህ አጋጣሚ እገልጻለሁ ” ሲሉ ደብዳቤያቸውን የቋጩት አቶ ልደቱ፣ እሳቸው በሚሉት ደረጃ ለኢትዮጵያ ወሳኝና ለዘመኑ ቀውስ መድሃኒት የሆኑ ዜጋ ስለመሆናቸው የሚያሳይ ታሪካቸው ለማሳያነት አልጠቀሱም።

በጽሁፋቸው ኢትዮጵያ በኤርትራና በሱዳን መወረሯን አንስተው ” ይህ የመበታተን ምልክት ነው” ብለዋል። የኢትዮጵያ ጦር ላይ ክህደት ተፈጽሞ በተኛበት መጨፍጨፉን አጉልተው ሲነቅፉ ያልተሰሙት አቶ ልደቱ ዛሬም ኤርትራን ወራሪ አድረገው መሳላቸው ግራሞትን ፈጥሯል።


ልደቱ አያሌው ከእነ ጃዋር ጋር በጥምረት እንደሚሰሩ አረጋገጡ


“ከሞት የተረፈው የኢትዮጵያ ጦር እርቃኑንን በርሃብና በውሃ ጥም ተሰቃይቶ ኤርትራ ሲገባ ነብስ እንዲዘራና ሃፍረተ ሰወነቱን እንዲሸፍን ያደረጉት የኤርትራ ሰራዊትና መንግስት ናቸው” በሚል የአገር መከላከያ ሰራዊት አባላት የደረሰባቸውን ግፍ በተናገሩት መጠንና ህዝብ ቁጣውን በገለጸበት ልክም ባይሆን አቶ ልደቱ ለትህነግ ወግነው መቆማቸው ደጋፊ አለባ አድርጓቸዋል እየተባለ ነው።

ተወለድኩበት የሚሉት አካባቢ ሳይቀር በዚሁ ከትህነግ ጋር ያላቸውን ትሥሥር ጥላቻ ድጋፍ እየነሳቸው መሆኑንን በመረዳታቸው ከጤና ችግራቸው ጋር አዳምረው ከፖለቲካው ዓለም ለመሰናበት መወሰናቸውን ከጽሁፋቸው ግርጌ አስተያየት የሰጡ አስታውቀዋል። ” ሲሻለኝ እንደምመለስ ተስፋ አደርጋለሁ” ያሉትን አስመክልቶ ” አቶ ልደቱ አሁን የደበዘዘውና የሰከነው የውስጡ ፖለቲካ ሲጋጋል እንደሚሻላቸው አመላክች ነው” የሚል ሽሙጥ ቢጤ አስተያየት ተሰጥቶበታል።

አቶ ልደቱ “የትግራይ ህዝብና ትህነግ አንድ ናቸው” በሚል ድምዳሜያቸው ይታወቃሉ። በዛሬ የመለያያ ጽሁፋቸው መንግስትን ለአንዴና ለመጨረሻ በሚመስል መልኩ ደብድበዋል። ህገ መንግስቱ እንዲቀየር ጥሪ አቅርበዋል። የህገመንግስት ረቂቅና አፈጻጸም መጽሃፍ እያዘጋጁ ስለሆነ ተቃዋሚዎች እንደ ሰነድ ተጠቅመውበት የመታገያ አጀንዳቸው እንዲያደርጉት ታቦት ሳይተሩ ተማጽነዋል። በተዘዋዋሪ መጽሃፉን ግዙ ብለዋል።

የትህነግ መክሰም በኢትዮጵያ በርካታ ችግሮችን አብሮ እንደሚያከስም በፖለቲካው ዙሪያ ያሉ አስተያየት ሰጥተዋል። በርካታ ደጋፊዎቻቸውም ተስፋ እንደሚቆርጡ አመልክተዋል።

ሌላው የተነሳው ጉዳይ አቶ ልደቱ ከፖለቲካ መሰናበታቸውና የእነ ጃዋር መሐመድ ምግብ መጀመር ግጥምጥሞሽ ነው። አቶ ልደቱ ” ከመስከረም ሰላሳ በሁዋላ መንግስት የለም” የሚለውን ዘመቻ ሲቀላቀሉ ከነ ጃዋር ጋር ገጥመው የነበረ መሆኑንን፣ በኦሮሞ ሚዲያዎች ላይ ከጃዋር ጎን በመሆን በህብረት ዘመቻውን ማራመዳቸውን ያታወሱ፣ ሁሉም ነገር ማክተሙና እነ ጃዋርም መግብ ለመብላት መወሰናቸው አቶ ልደቱን አዲስ የሚተበቅ ተስፋ አሳጥቷቸዋል። በዚህም የተነሳ ስንበቱን ለጊዜውም ቢሆን መርጠዋል የሚሉ አስተያየቶች ተሰምተዋል። አቶ ጃዋር ” የአንድነት ሃይሎች ከዱኝ” በማለት መናገሩን እንዚህ ላይ የሚያነሱ አሉ።

Exit mobile version