ETHIO12.COM

አንዳንድ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ስለ ትግራይ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ ያወጡት መረጃ የተዛባ ነው – ዶክተር ሙሉ

የተወሰኑ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ስለ ትግራይ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ ያወጡት መረጃ መሬት ላይ የሌለና የተዛባ መረጃ መሆኑን የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ስራ አስፈጻሚ ዶክተር ሙሉ ነጋ ገለጹ።

ዶክተር ሙሉ በሰጡት መግለጫ አንዳንድ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች የህወሓት ጁንታ ቡድን ያደራጃቸውን ሰዎች ሃሳብ ብቻ በመውሰድ ስለ ክልሉ የተዛባ መረጃ ማውጣታቸው ስህተት መሆኑን ገልጸዋል።

የክልሉን ተጨባጭ እውነታ መዘገብ ያስፈልጋል ያሉት ዶክተር ሙሉ ጊዜያዊ አስተዳደሩና የፌዴራል ጸጥታ አካላት ክልሉን እያረጋጉና ለሕዝቡ የሚያስፈልገው አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።

የጥፋት ቡድኑ በተለያየ ቦታ ተበትኖ ችግር እየፈጠረ፣ ሕዝቡን እየጎዳና የኅብረተሰቡንም ሠላም ለማወክ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል ይህን በሚያደርጉ ላይም ህጋዊ እርምጃ እየተወሰደ ይገኛል ብለዋል።

መገናኛ ብዙሃኑ ግን የጥፋት ቡድኑ አባላት የሚያደርሱትን ጉዳት የመንግስት የጸጥታ አካላት እንደፈጸሙ አድርገው መዘገባቸውን ነው የገለጹት።

በክልሉ እየተፈጸሙ ለሚገኙ ችግሮች ዋነኛው ተጠያቂ የህወሓት ቡድን መሆኑንም ተናግረዋል።


የጥፋት ቡድኑ ሆን ብሎ ሕዝቡ ውስጥ በመሸሸግ ጉዳት በማድረስ የአገር መከላከያ ሠራዊት እንደፈጸመው ለማስመሰል እየተንቀሳቀሰ መሆኑንም ጠቁመዋል። ከፌዴራል መንግስት በተጨማሪ በክልሎችና በአጋር ድርጅቶች በሚደረጉ የተለያዩ ድጋፎች ክልሉን መልሶ ለመገንባት እየተሰራ እንደሆነም ገልፀዋል። እንደ ዶክተር ሙሉ ገለጻ ክልሉን መልሶ ለማደራጀት እየተሰራ ያለው ስራ በጥሩ ሁኔታ እየሄደ ነው። ( ኢዜአ)

Exit mobile version