Site icon ETHIO12.COM

በኢትዮጵያ የኮቪድ-19 ስርጭት አስደንጋጭ በሆነ ሁኔታ እየጨመረ ነው – የኮቪድ-19 ክትባት ቅዳሜ ይጀምራል

በኮሮናቫይረስ የመያዝ ምጣኔ በኢትዮጵያ የ12 ነጥብ 8 በመቶ ጭማሪ  ማሳየቱን የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ገለጸ። ይህ በኮሮናቫይረስ የመያዝ ምጣኔ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ  2 በመቶ፣ በአፍሪካ 10 በመቶ መጨመሩን ገለጸ።  በኢትዮጵያ የኮቪድ-19 ክትባት ከፊታችን ቅዳሜ መጋቢት 4 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ መሰጠት እንደሚጀምር የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

ኢንስቲትዩቱ በኢትዮጵያ የኮቪድ-19 ስርጭት አስደንጋጭ በሆነ ሁኔታ እየጨመረ ነው  ሲልም  አስጠንቅቋል። ባሳለፍነው ሳምንትም ከየካቲት 22 እስከ 28 ቀን 2013  ዓ.ም በዓለም አቀፍ ደረጃ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር የ2 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።

በአፍሪካም በዚሁ ሳምንት በቫይረሱ የመያዝ ምጣኔ በ10 በመቶ የጨመረ ሲሆን በተለይ በኢትዮጵያ ደግሞ ከዚህም አልፎ በ12 ነጥብ 8 በመቶ አድጓል፡፡ በትናንትናው ዕለት የኮቪድ-19 የላቦራቶሪ ምርመራ ካደረጉ 7 ሺህ 819 ሰዎች መካከል 1 ሺህ 543ቱ የኮቪድ-19 ቫይረስ ተገኝቶባቸዋል፡፡

ይህ ማለት ከተመረመሩት 100 ግለሰቦች 20 ያህሉ ወይም 20 በመቶ ኮሮናቫይረስ ተገኝቶባቸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ከፍተኛ ቁጥር የተመዘገበው በነሐሴ ወር 2012 ዓ.ም  ማህበረሰብ አቀፍ ንቅናቄና የምርመራ ዘመቻ በተካሄደበት ወቅት ነው፡፡

በከፍተኛ ፍጥነት እየጨመረ ያለው የፅኑ ሕሙማን ቁጥርም ትናንት 438 ደርሷል፡፡ ይህ ቁጥር ኮቪድ-19 ወደ አገሪቱ ከገባ ጀምሮ ከፍተኛው ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ በትናንትናው እለት ብቻ 15 ግለሰቦች በኮቪድ-19 ምክንያት ሕይወታቸውን ያጡ ሲሆን የሟቾች አጠቃላይ ቁጥር 2 ሺህ 446 ደርሷል፡፡ የቫይረሱ ስርጭት በሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች በፍጥነት እና በአስደንጋጭ ሁኔታ እየተዛመተ መሆኑን  ገልጸዋል።

ኢንስቲትዩቱ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ማስክ በመልበስ እንዲሁም አካላዊ ርቀታቸውን እና የእጃቸውን ንጽህና በመጠበቅ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ የሚያደርሰውን ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት በጋራ እንዲከላከሉ ጥሪ አቅርቧል፡፡

 በኢትዮጵያ የኮቪድ-19 ክትባት ከፊታችን ቅዳሜ መጋቢት 4 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ መሰጠት እንደሚጀምር የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

ክትባቱ በሁሉም ክልሎች እና የከተማ መስተዳድሮች ላይ የፌደራልና የክልል ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት እንደሚሰጥም ነው ሚኒስቴሩ ያስታወቀው፡፡

ጤና ሚኒስቴር ክትባቱን ለመጀመር የሚያስችሉ ቅድመ ዝግጅቶችን በስፋት እያከናወነ መሆኑን ገልጿል፡፡

እስካሁን ስልጠና መስጠት፣ ክትባቱን ማሰራጨትና ክትባቱን መውሰድ የሚገባቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች የመለየቱ ተግባርና ሌሎችም ዝግጅቶች በስፋት ማከናወኑንም አስታውቋል፡፡
ኢትዮጵያ 2 ነጥብ 2 ሚሊየን የመጀመሪያው ዙር የኮቪድ 19 ክትባት በኮቫክስ ዓለም አቀፍ ጥምረት መረከቧ ይታወሳል፡፡

በመጀመሪያ ለቫይረሱ ተጋላጭ የሆኑ የጤና ባለሙያዎችና ሰራተኞች፣ እድሜያቸው ከፍ ያሉ እና ተጓዳኝ ህመም ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ክትባቱን እንዲያገኙ ይደረጋል ተብሏል፡፡

FBC

Exit mobile version