Site icon ETHIO12.COM

በፔሮል የሚከፈላቸው የውጭ አገር ሚዲያና የሠብዓዊ መብት ታጋይ ነን የሚሉ ሃይሎች ኢትዮጵያ ላይ ዘመቻ መክፈታቸውን ይፋ ሆነ

 በትግራይ ክልል ቀውስ ሰበብ በኢትዮጵያ ላይ ተፅዕኖ እንዲደርስ የሚሹ ተከፋይ የምዕራባዊያን ሚዲያና በሠብዓዊ መብት ስም የሚንቀሳቀሱ ሃይሎች መኖራቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ገለጹ። የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በዜጋ፣ በኢኮኖሚና በፖለቲካ ዲፕሎማሲ ሣምንታዊ አበይት ክንውኖች ላይ መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫቸው በትግራይ ክልል ከተካሄደው የሕግ ማስከበር ዘመቻ በኋላ ምዕራባዊያን በየጊዜው በኢትዮጵያ ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር የሚያደርጉትን ጥረት አስመልክቶ ለተነሱላቸው ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል።

የአገራቱ ጥያቄ በመጀመሪያ በጦርነቱ ወቅት ሠብዓዊ ድጋፍ አልተፈቀደም፣ ቀጥሎም የሠብዓዊ መብት ጥሰት አለ፣ በመጨረሻም ሠብዓዊ ድጋፉ ይጠናከር የሚሉ ጉዳዮችን ሲያነሱ መቆየታቸውን ገልጸዋል።

ጥያቄያቸው በጊዜው እንደተፈቀደላቸው ገልጸው፤ ነገር ግን ከዓመታት በፊት እንደተደረገው በሠብዓዊ ድጋፍ ሰበብ በመግባት በእርዳታ ማሰባሰብ ስም መክበር የሚሻ ሃይል እንዳለ ጠቁመዋል። ከዚህ ባሻገር ቀጣናውን ወደ ትርምስ ለማስገባት የሚሹ የጦር መሳሪያ ነጋዴዎች ፍላጎት እንዳለም ገልጸዋል።

የሕግ ማስከበር ዘመቻው በጥፍነት በመጠናቀቁ ተስፋ የቆረጠ ሃይል መኖሩን የጠቀሱት አምባሳደር ዲና፤ በተለያየ ጊዜ ኢትዮጵያ ላይ ተጽዕኖ እንዲያርፍባት የሚሹ መኖራቸውን ጠቅሰል።

በዚህም ቀድሞውኑ የፔሮል ተከፋይ የነበሩ ታዋቂ ሰዎችን፣ የሚዲያ ባለሙያዎችና በሠብዓዊ መብት ተሟጋች ስም የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦችን ያካተተ ፕሮፓጋንዳ የሚነዛ ሃይል መኖሩንም ጠቁመዋል።

የኢትዮያ ሠላም ለአሜሪካም ሆነ ለአውሮፓ ጠቃሚ እንደሆነ ገልጸው፤ ‘በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ ይጣላል’ በሚል የሚነዙትም የፔሮል ተከፋይ ግለሰቦች መሆናቸውን ተናግረዋል።

ያም ሆኖ ነባራዊ ሁኔታውን ዲፕሎማቶችና ሚዲያዎች በመታየቱ፤ የአውሮፓና አሜሪካ ተጽዕኖ ይቀጥላል የሚል እምነት እንደሌላቸው ቃል አቀባዩ አብራረተዋል።

በኢትዮጵያ በኩል የተዛባ ምልከታ የነበራቸውን ወገኖች ነባራዊ ሁኔታውን የማስረዳት ዲፕሎማሲያዊ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል።

በዚህም በሣምንቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከተለያዩ አገራት አቻዎቻቸውና አምባሳደሮች ጋር መወያየታቸውን፤ በአዲስ አበባ የሚገኙ የአገራት አምባሳደሮች በትግራይ ክልል በአካል ተገኝተው ሁኔታውን መመልከታቸውንና እርዳታ ለማድረግ አዎንታዊ ምላሽ መስጠታቸውን ጠቅሰዋል።

በተለያዩ አገራት የሚገኙ የኢትዮጵያ አምባሳደሮችም ለሚመለከታቸው አገራት መንግስታት የማስረዳት የዲፕሎማሲ ስራዎች ማከናወናቸውን ተናግረዋል።

በትግራይ ክልል ከ4 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ ለሆኑ ዜጎች የመጀመሪያ ዙር ምግብና ምግብ ነክ ሠብዓዊ ድጋፍ መቅረቡንና በቀጣይ ምዕራፍ ድጋፍ የሚሹ ዜጎችን የመለየት የዳሰሳ ጥናት እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል።

በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲም ከተለያዩ አገራት ዜጎች እየተመለሱ መሆኑን፤ ከሳዑዲ ዓረቢያ ጂዳ ብቻ 888 ዜጎች ባለፈው ሣምንት መመለሳቸውን አስታውሰዋል።

በየመን ሰንዓ እስር ቤት በደረሰው የእሳት አደጋም ሕይወታቸው ካለፈ 43 ሰዎች መካከል ኢትዮጵያዊያን እንዳሉበት ገልጸው፤ በየመን ኤደን የሚገኙ ከ150 በላይ ዜጎች ዛሬ እንደሚመለሱም ጠቁመዋል።

በአሜሪካና በአውሮፓ አገራት ኢትዮጵያዊያን ለአገራቸው ብሔራዊ ጥቅም ወግነው ያካሄዱት የድጋፍ ሠልፍ የሣምንቱ አበረታች ክስተት እንደነበረ በመግለጽ ምስጋና አቅርበዋል።

የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የሶሰትዮሽ ድርድርን በተመለከተም ሱዳንና ግብፅ አራት አደራዳሪ ወገኖች ይግቡ በሚል ያቀረቡትን ሃሳብ በተመለከተ ለኢትዮጵያ በይፋ እንዳልቀረበላት ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ፣ የሱዳንና የግብፅ የሶስትዮሽ ድርድር የሚቋጨው በሶስቱ አገራት እንጂ በአደራዳሪዎች እንዳልሆነ የገለፁት ቃል አቀባዩ፤ “የአደራዳሪ ሚና ማስተባበር እንጂ ማጉረስ አይደለም” ብለዋል።

“ለአፍሪካ ኅብረት ትልቅ ክብር አለን፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካን ችግር በአፍሪካ የመፍታት ፅኑ አቋም አላት” ነው ያሉት።

“ኢትዮጵያ ለድርድር ሁሌም ዝግጁ ናት” ያሉት አምባሳደር ዲና፤ የውሃ ሙሌቱም በታቀደለት መንገድ እንደምትፈጽም፣ ድርድሩም “ከሙሌቱ በፊትም ቢሆን ቢቋጭ ኢትዮጵያ ችግር የለባትም” ብለዋል።

ሱዳንና ግብጽ በሶስትዮሽ ድርድሩ ከአፍሪካ ኅብረት በተጨማሪ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ የአውሮፓ ኅብረትና አሜሪካ እንዲገቡ ፍላጎት እንዳላቸው ማስታወቃቸው ይታወሳል።

ENA

Exit mobile version