Site icon ETHIO12.COM

በምዕራብ ውለጋ ነጹሃን ተገደሉ፤ ግድያው ብሄርን መሰረት ያደረገ ነው፤ “ጃልመሮ በቪኦኤ ያስተባብላል”

አስቀድሞ ነዋሪዎቹን አንድ ቦታ ሰብሰቦ እንደጨፈጨፋቸው ነው የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ያስታወቀው። ቦታው በምዕራብ ወለጋ ዞን ባቦ ጋምቤል ወረዳ፣ ቦኔ ቀበሌ ሲሎን በርካታ ዜጎች በብሄር ተለይተው ነው የተገደሉት። የተለያዩ የዩቲዩብ አውታሮች የሟቾችን ቁጥር ወደ መቶ ከፍ አድረገውታል። አንዳንዶች በፌስ ቡክ በተመሳሳይ ቁጥሩን ከሰባ በላይ እንደሆነ አመልክተዋል። የኦሮሚያ ፖሊስ ግን 28 ሰዎች መሞታቸውን በይፋ አመልክቷል። በድንገት በሚከፈት ጥቃት በርካታ ንጹሃን አርሶ አደሮችን የገድላል በሚል የሚወነጀለው ጃልመሮ ይህንኑ ጥቃት አስመልክቶ በቪኦኤ ማስተባበያ ይሰጣል ብለው እንደሚጠብቁ የገለጹ አሉ።

ግድያውን ተከትሎ የኦሮሚያ ክልል ባወጣው መግለጫ በዞኑ ውስጥ በሚገኘው ባቦ ገንቤል ወረዳ በቦኔ ቀበሌ ውስጥ በሚገኙ ሰዎች ላይ “አሰቃቂና ዘግናኝ” ያለውን ጥቃት የፈጸመው ኦነግ-ሸኔ መሆኑንን አመልክቷል። ወዲያው የክልል የጸጥታ ሃይል የአጸፋ እርምጃ መውሰዱን በቀጣይነትም በቡድኑ ላይ የሚወሰዱ እርምጃዎችን ለሕዝብ ይፋ አደርጋለሁ ብሏል። ክልሉ ይህንን ባለ ሰዓታት ውስጥ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል አራርሳ መርዳሳ ሶስት የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ወዲያውኑ መገደላቸውን አመልክተዋል።

ክልሉ እንዳለው ኦነግ ሸኔ የህወሓት ተላላኪ በመሆን በአካባቢው የመንግሥት መዋቅርን በማፍረስ በገጠርና በከተማ በመንግሥት አመራሮችና በሰላማዊ ዜጎች ላይ ከዚህ በፊት “ዘግናኝ የሽብር ጥቃቶችን ሲፈፅም ቆይቷል” ብሏል አያይዞም የቀበሌ ጨምሮ በተለያዩ ደረጃ ያሉ አመራሮችንና፣ እንዲሁም ንጹሃን ዜጎች መገደላቸውን የክልሉ መንግሥት መግለጫ አውስቷል። ቡድኑ በግልና በመንግሥት ንብረቶች ጥቃት ሰንዝሯል።

በተደጋጋሚ መንግስት በወስደበት እርምጃ በመዳከምና ተስፋ በመቁረጥ ውስጥ ያለው ኦነግ ሸኔ “በሞትና በህይወት መካከል ሆኖ የጥፋት ሴራውንና እርምጃውን ቀጥሏል” ሲል ክልሉ በመግለጫው የቡድኑን የማይቀየር ባህሪ አመላክቷል።

የኦሮሚያ ፖሊስ እንዳለው የተገደሉ ንፁሀን ዜጎች 28 ናቸው። 16 ወንዶች እና 12 ሴቶች ህይወት ተቀጥፏል። የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል አራርሳ መርዳሳ እንዳሉት ከሟቾች በተጨማሪም 12 ሰዎች ላይ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

የክልሉ ፖሊስ በአካባቢው ደርሶ አካባቢውን ለማረጋጋት ባደረገ ስራም ሶስት የኦነግ ታጣቂዎች ላይ እርምጃ መወሰዱን ኮሚሽነር ጀነራል አራርሳ መርዳሳ ተናግረዋል።ከምሽቱ ሶሰት ሰአት ላይ ከ50 በላይ የሚሆኑ ነዋሪዎችን ሰብስቦ የኦነግ ሸኔ ታጣቂ ጭፍጨፋ ፈፅሟል ሲሉ ኮሚሽነሩ ገልጸዋል። ባለፈው አንድ አመት በኦነግ ሸኔ ላይ በተወሰደም እርምጃ 1 ሺህ 947 አባላቱ የተገደሉ ሲሆን 489 አባለቱ ደግሞ መማረካቸውን ኮሚሽነር ጀነራሉ ተናግረዋል።

” ስሜ ኦነግ ሸኔ አይደለም” ሲል ባለፈው በሆሮ ጉድሩ የተፈጸመውን እጅግ ዘግናኝ ጭፍጨፋ በቪኦኤ እንዲያስተባብል እድል የተመቻቸለትና ከስሙ በቀር በውል ማንነቱ የማይታወቀው ጃልመሮ በቅርቡ እንዳለው በአዲሱ ስሙ ” ወንጀሉን እኛ አልፈጸምንም። የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት በብሄርና በሃይማኖት ለይቶ አይገድልም፤ ግድያውን የፈጸሙት የአማራና የኦሮሚያ ብልጽግና ናቸው” በማለት እንደሚያስተባብል ጭፍጨፋው ስር አስተያየት የሰጡ ገልጸዋል።

የአማራ ክልል ብልጽግና ወለጋ ድረስ ሄዶ የራሱን ወገኖች ለምን መግደል እንዳስፍለገው ማብራሪያ እንዲሰጥ ያልተጠየቀው ጃል መሮ ዛሬም ተመሳሳይ መግለጫ እንደሚሰጥ በአስተያየት ሳጥን ስር የጻፉ ” አትገረሙ ቢቢሲና ቪኦኤ የጃልመሮ ናቸው” እያሉም ብስጭታቸውን በስላቅ ለማሳየት ሲሞክሩ ታይተዋል።


Exit mobile version