Site icon ETHIO12.COM

እነ ስብሃት ነጋ በትግራይ ክልል ለመዳኘት ያቀረቡት ጥያቄ ውድቅ ሆነ – ቅድመ ምርመራ ክስ እንዲሰማ ተወሰነ

እነ ስብሃት ነጋ በትግራይ ክልል ፍርድ ቤት ጉዳያችን ይታይልን ሲሉ ያቀረቡት ጥያቄ ውድቅ ሆነ፡፡ ባለፈው ቀጠሮ ተጠርጣሪዎቹ ጉዳያችን በፌደራል ፍርድ ቤት ሳይሆን በትግራይ ክልል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ነው መታየት ያለበት ሲሉ አቤቱታ አቅርበው ነበር፡፡

አቤቱታውን የተመለከተው ፍርድ ቤትም ጉዳያቸው መታት ያለበት አካባቢ ወሰን ሳይደረግበት ወንጀሉ ሲፈፀምም ከክልሉ ውጪ ማለትም ባህር ዳርና ጎንደር በሮኬት የተመታ እና በሃገር መከላከያ ሰራዊት ላይ ጥቃት የደረሰ በመሆኑ እንዲሁም የፌደራል መንግስትን ስልጣን በሃይል ለመቆጣጠር የተፈፀመ ወንጀል በመሆኑ የአካባቢ የዳኝነት ስልጣን ያለው የፌደራል ፍርድቤቶች ነው ሲል ጥያቄቸውን ውድቅ አድርጎታል፡፡

በዛሬው ችሎት አቶ ስብሃት ነጋ፣ አምባሳደር አዲስአለም ባሌማ፣ አምባሳደር አባይ ወልዱ፣ አቶ አብርሃም ተከስተን ጨምሮ ሌሎች ተጠርጣሪዎች ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ነገር ግን ዶክተር ግዳይ በርሄና አባዲ ዘሙን ጨምሮ ሌሎች ዘጠኝ ተጠርጣሪዎች በህመም ምክንያት ችሎት አለመቅረባቸው ተገልጿል፡፡

የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ተጠርጣሪዎች ያነሱትን አቤቱታ ተከትሎ ብይን ሰጥቷል፡፡በዚህ መሰረትም ዐቃቤ ህግ የቅድመ ምርምራ ምስክር እንዲሰማ የመወሰን ስልጣን የለውም ብለው ባነሱት መቃወሚያ ላይ ፍርድ ቤቱ ቀዳሚ ምርመራ የመወሰን ስልጣን የጠቅላይ አቃ ህግ ነው ሲል መቃወሚያውን ህጋዊ መሰረት ያለው ሆኖ አላገኘሁትም በማለት ውድቅ አድርጎታል፡፡

እንዲሁም በወንጀል ስነ ስርዓት ህጉ አንቀፅ 80 ንዑስ ቁጥር 1 መሰረት በከባድ ወንጀልና የግፍ ግድያ ቀዳሚ ምርመራ የሚደረግ መሆኑን የመወሰን ስልጣን ለዐቃቤ ህግ እንዲሰጠው ችሎቱ አብራርቷል፡፡ተጠርጣሪዎቹ የምስክር ስም ዝርዝር ይገለፅልን ብለው ባቀረቡት አቤቱታ ላይም በምስክሮች ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 699 መሰረት ምስክሮች ለደህንነታቸው ሲባል ማንነታቸው ሳይታይ ምስክርነታቸውን እንዲሰጡ የተደረገ በመሆኑ ፍርድ ቤቱ አልተቀበለውም በማለት ውድቅ አድርጎታል፡፡በዚህ መሰረትም ለዝግ ችሎት የዐቃቤ ህግ የቅድመ ምርመራ ምስክሮችን ለመስማት ለመጋቢት 29 ቀን 2013 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡በቀጣይ ቀጠሮም ማረሚያ ቤቱ ዛሬ ችሎት ያልተገኙ ተጠርጣሪዎችን እንዲያቀርብ ትዛዝ መስጠቱን ኤፍ ቢሲ ዘግቧል።


Exit mobile version