Site icon ETHIO12.COM

” ኦሮሙማ ይውደም፣ ኢትዮጵያ ትቅደም ” ለፍትህ ጥያቄ ምኑ ነው?

“ኦሮሙማ ማለት ኦሮሞነት ማለት ነው” መነሻም መድረሻም የሆነው ሃሳብ እሱ በመሆኑ አስቀደምኩት። አማራ ይትህነግ ክፉ አገዛዝ ሲጠነሰስ ጀመሮ የፈረጀው ሰርቶ የሚበላ ምስኪን፣ ጨውና ምግባር ያለው ሕዝብ ለመሆኑ ቅንጣት ሳልጠራጠር እመስከራለሁ። ከሁሉም ዓይነይ የህብረተሰብ ክፍል እንክርዳድ እንደማይጠፋው ሁሉ በየትኛውም ስርዓት የአማራን ህዝብ በጥቅል የማይወክሉ ጥፋት የሰሩ የስልጣንና የነዋይ አምላኪዎች ነበር፤ አሉ፤ ወድፊትም ይኖራሉ። እያየናቸውም ነው። ይህ እውነት ቀድሞ እነደተባለው ኦሮሞው፣ ሶማሌው፣አፋሩ፣ ትግሬው … ሁሉም ጋር አለ። ይኖራል። ነበር። ተረኘቱም ሆነ ለተረኝነት የሚደረገው ግብግብ እንደዚህ ነበር። ይኖራል። ይቀጥላል። በንጽሃን አስከሬንና ደም የሚቆመረውም ለዚሁ ነው።

ይህንን ካልኩ ወደዋናው ጉዳዬ ስመለስ በቀጥታ ሰሜን ሸዋ የሆነውን ጉዳይ በጨረፍታ ማስታወስ እወዳለሁ። ሰሞኑን በሰሜን ሸዋ በተለይም በአጣዬና አካባቢው፣ እንዲሁም የአካባቢው ባለስልጣናት፣ የክልሉ መግስት፣ የፌደራል ተቋማት እንዳስረዱን ” ኦነግ ሸኔ” የተባለው የአውሬዎች ስብስብ በቃላት ሊገለጹ የማይችል ጉዳት አድርሷል። ከሚሰጠው መላምት በቀር ጉዳቱን አድራሹ አካል ለምሳሌ የሁለት ዓመት ሕጻን ለምን እንደሚገድል፣ መን ፈልጎ እንደሚገድል፣ ምን እስኪሟላለት ህጻናትን እንደሚያርድ፣ እስከመቼ የሕጻናትን ደም እንደሚጠጣ ፣ የአረጋዊያንን ስጋ እንደሚበላ፣ የነብሰ ጡሮችን ህይወት እንደሚቀጥፍ … እንደ ድርጅት ሃላፊነት ወስዶ ከሚነገረን ይልቅ በቪኦኤ ” የአምላክ ደቀ መዝሙር ነኝ” እያለ በደም የተለውሰበትን ከፈኑንን ሲቀይር እየሰማን ነው።

በተደጋጋሚ በቪኦኤ ” ስሜ ኦነግ ሸኔ አይደለም” ብሎ አዲስ ስም ሲያበጅ፣ ” ከዚህ ቀደም አስከሬን ላይ እየደነስክ ኦነግ ሸኔ እያልክ በኩራት መግለጫ ትሰጥ ነበር ” እንኳን ብሎ የማይጠይቅ ” ኢትዮጵያዊ ሪፖርተር ” ሲጠፋ፣ /” ጋዜጠኛ” የሚለውን ስም መጠቀም ስለማልፈልግ ነው/ ሃላፊዋ ትዝታ በላቸው የት ነች? ወይስ አውቃ ነው? ወይስ ” የዘሬ ያንዘርዝረኝ” ውስጥ አለችበት? ወይስ ” የአሳዳሪዎቻቸው መመሪያ ወርዶ” አይታወቅም። ግን ይህ ሆኗል።

ዋናው ሃሳቤ ይህ ባለመሆኑ ይህንን እንደ ሃሳብ አንስቼ ልለፈውና በጂሌና ጡሙጋ ወረዳ ፋሪስ ወረዳ በመሳሰሉት ስፍራዎችም የኦሮሞዎች ቤት ሲቃጠል፣ አቃጣዮቹ እነማን እንደሆኑ በግልጽ በሚያሳይ መልኩ ቪዲዮ አለ። ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ፣ አቅሙና ሁኔታው የተመቻቸላቸው ሁሉንም ጥርት አድረገው ከሁሉም ወገን የሆነውን ለመዘገብ የተጉ ኢትዮጵያዊ ባለሙያዎች እጥረት አለ። ወይም ፍላጎት የለም። በዩቲዩብና በማህበራዊ ሚዲያ የሚተላለፈው መረጃና ቪዲዮ በአብዛኛው ፣ ሌላ ነውጥ እንዲፈጠር፣ ሌላ የእልቂት ሰደድ እንዲነሳ የሚጋብዝ፤ ሳንቲም ለመልቀም በሚያስችል ለከት ያጣ የዩቲዩብ ጉሊት በእሳቱ ላይ ቤንዚን የሚያርከፈክፍ፣ ትንተናው ደግሞ በአብዛኛው ሌላ የጥፋት ስትራቴጂ የሚያመላክትና በተፈጠረው ቁጣ ላይ አሲድ የሚያራባ አይነት ነው።

ይህንን ክፉ እልቂትና ውድመት ተከትሎ እንባ ሳይደርቅ፣ ደም ሳይረጋ፣ የቃጠሎው ጭስ ሳይበርድ፣ የድንጋጤ ስሜት ሳይረግብ፣ ሁሉም ግራ በተጋባባት ቅጽበት የደም ስር ቁማርተኞችና የትህነግ ዓላማ ተሸካሚዎች ” የሽግግር መንግስት ይቋቋም፣ ሁሉንም ያካተተ ንግግር ይጀመር” የሚል አስተያተቻው ላይ ተተምደዋል። የአማራ ክልል ተቀናቃኝ ድርጅት ” የክልሉን መሪ ድርጅት መክኗል” ሲል ከተት አውጆ ” እኔ ዘመቻው ከፊት እመራለሁ” ሲል ራሱን መንግስት አድርጓል። ቢቢሲ የአጣዬን ነዋሪ ጠቅሶ ” ኦነግ ሸኔና ህወሃት ጨፈጨፉን” ሲል የዘገበውና ጌታቸው ረዳ አስቀድሞ ሃይል ወደ አማራ ክልል ገብቷል ሲል የዛተው ትልቅ ስዕል ተዘንግቷል።

የድራማው ተዋናዮች በአንደበታቸው አማራ ክልል መዝለቃቸውን ይፋ አድርገው ሳለ፣ በተለያዩ ከተሞች አማራ ላይ የተነጣጠረ የጥፋ ዘመቻ የሚቃወምና ፍትህን የሚጠይቅ ሰልፎች ተካሂደዋል። ሰልፎቹ ሰላማዊ መሆናቸው ደስ ያሰኛል። በጨዋነት ምሬትን ማሰማት በራሱ የሚመሰገን እድገት ነው። ከሆነውና ሲሆን ከነበረው አንጻር ተቃውሞውና ምሬቱ አግባብ ነው። ይደገፋል። ቅር የሚላቸው አካላት ካሉም መብት ነውና ቅር እንዳላቸው ይቀራሉ። ነገር ግን የአጣዬ ነዋሪ የህወሃት አፍ በሆነው ቢቢሲ ላይ የተናገሩት ታላቅ ቁም ነገር ሰልፉን እመራለሁ ላለው አብን ቁብ ሊሰጠው አለመቻሉ በግል ያሳስበኛል።

እሱ ብቻም ሳይሆን ይህን ተቃውሞ በማስፋት ወደ መንገድ መዝጋትና ህገ መንግስት እንዲቀየር በሚጠይቅ ደረጃ ከፍ እንዲል የሚያሳስቡ ሃሳቦች ደግሞ ሰላማዊ የተባሉትን ሰልፎች እያጀቡ እየወጡ መሆናቸው መምታታትን ፈጥሯል። ዓላማቸው መንግስት መገልበጥ ይሁን ሌላ በግልጽ ባይጠቅሱም ሰለፎቹ በይዘትም፣ በቅርጽም ለየት ብለው እንዲያድጉ ጥሪ እየቀረበ ነው። ኦሮሚያ ክልልም በተመሳሳይ እንዲያምጽ ግብዣ እየቀረበለትም ነው። ኦሮሞ መንገድ እንዲዘጋና ጃዋርን እንዲያስፈታ የሚቀርበው ጥሪ ለአማራ እንቆረቆራለን የሚሉት ናቸው እያቀረቡ ያሉት።

ሕገመንግስት

ዛሬ ህገመንግስት አንድ ክልል ወይም ብሄር ስለፈለገ፣ ስለተሰለፈ ወይም ስለተቆጣና በደል ስለደረሰበት ይቀየራል? ወይም ሌሎች ከምርጫ በሁዋላ ይታያል የሚል አሳብ ቢኖራቸውስ? ወይም እስከነ አካቴው ባይፈልጉስ? እንዴት ይሆናል? ይህ ጥያቄ በዛሬዋ የኢትዮጵያ ስሪት መነሳትና በእርጋታ መታየት የለበትም?

ሕገመንግስት የሚቀየርበት የተቀመጠ ሕጋዊ አግባብ አለ። ይህ በመርዝ ተለውሶ “የጸደቀ የዕዳ ጽህፈት” በሕጋዊ መንገድ ካልሆነ በስተቀር በሌላ መልኩ ለመቀየር መሞከር ሌሎችን ለተቃውሞ አይጋብዝም? እንዲሁ በማህበራዊ ገጽ ስለተባለ ይሆናል? አሁን ባለው ህጋዊ አግባብ ማሰብ አይገባም? በዚህ መልኩስ ይሁንታ ማግኘት ይቻላል? ጥያቄውን ወይም አሳቡን መቃወሜ ሳይሆን እነዚህ ጉዳዮች እንዴት ይታያሉ? የሚለው ስለሚያሳበኝ እንጂ ይህ ? መርዝ የዕዳ ጽህፈት” አሁኑኑ ቢቃጠል ደስተኛ ነበርኩ።

ኦሮሚያን ለዓመጽ መጋበዝ

አሁን በሚካሄዱት የተቃውሞ ሰልፎች የሚወገዙት ” የኦሮሞ ጽንፈኞች” ናቸው ቢባልም ” ኦሮሙማ ይውደም” እየተባለ ኦሮሞን የዚህ ተቃውሞ አካል እንዲሆን ማሰብ እንዴት እንደሚታረቅ ግልጽ አይደለም። ” ኦሮሙማ ” ወይም ” ኦሮሞነት” እንዲወድም ጥሪ እየቀረበ፣ ኦሮሚያ ላይ አመጽ እንዲነሳ ማሰብ የሚታረቅ ጉዳይ ነው? ይህን እያየና እየሰማ ኦሮሞ እንኳን አመጽ ” ኮሽ” እንዲል ይፈልጋል? ለአቅመ አዳም ያልደረሰው የተቃርኖ ፖለቲካና እሳቤ ውጤት ነውና አይገርምም።

ምስሉን የተጠቀምኩት ለሃሳቤ ማሳያ እንዲሆን፣ ፈጥሬ የተናገርኩት እንዳልሆነ ለማሳየት ነው። ከደረሰው በደል አንጻር እዚህ ግባ ሊባል የማይችል ጉዳይ መስሎ የሚታያቸው ቢኖሩም በኔ እይታ አለመሆኑንን ለማሳየት ነው

ይህ ብቻ አይደለም ” ጃዋር መሀመድን መፍታት ህግን መጻረር ነው” የሚሉ ወገኖች ዛሬ ኦሮሚያ በዓመጽ እንድትናጥ ሲጠይቁ ምን እንዲጠየቁ ወይም ምን እንዲሆን እየፈቀዱ እንደሆነ ስለመረዳታቸው ጭራሽ መገንዘብ አይቻልም። በግል ጃዋርም ሆነ ሌሎች እንዲፈቱ መጠየቁ ቅር የሚያሰኘኝ ሰው አይደለሁም። እንደውም አሁን ከመስመሬ እንዳልወጣ እንጂ በዚህ ጉዳይ በሌላ ብዕር እመለሳለሁ። በጥቅሉ ኦሮሚያ እንዲነሳ መጋበዝ፣ እነሱም ካደረጉት

1- ኦሮሚያን ተነስ ማለት ጃዋርን አስፈታ ማለት ነው።

2- ኦሮሚያን ተነስ ማለት ኦነግ ሸኔንና ሌሎች ከኦህዴድ የባሱ ጽንፈኞች እንዲነግሱ መመኘት ነው። መለመንና ” እባካችሁን” ብሎ መማጸንም ጭምር ነው። ለዘብተኛ አቋም ያላቸውን ካድሬዎችን አመለካከት የሚቀይር ይመስለኛል።

3- ከትህነግ ጋር አንድ የሆነው የኦሮሞ ጽንፈኛ ቡድን እንዲነግስ መመኘት የአማራ ክልል ላይ ወዶና ፈቅዶ ተቀጣጣይ ፈንጂ ማያያዝ ማለት ሆኖ ይሰማኛል። አስቡት ኦነግ ሸኔ ኦሮሚያ ላይ ነግሶ፣ ትህነግ በአደባባይ ወደ ክብር ቦታው ተመልሶ፣ የትህነግና የሱዳን ወዳጅነት በግብጽ ድጋፍ ታክሎበት የሚፈጠረው ምን ይሆን?

4- ኦሮሚያን ተነስ ማለት አስተዳደር ቀይርና ኦነግ ሸኔን አንግሰህ ትህነግና ወደ ኦሮሚያ ጋብዘው ማለት ብቻ አይደለም፣ በሰሞኑ የህግ ማስከበር ዘመቻ አማራ ላይ ጥርስ ለነከሰው የትህነግ የቂም መጋዝ ይህን ምስኪን ሕዝብ አሳልፎ መስጠት ነው። በቤኒሻንጉል ጋብ ያለውን ግጭት ማፋፋም ነው። በቅማንት እሳት እንዲነድ ቤንዚን ማርከፍከፍ ነው። በሱዳን በኩል በሩን መበረጋገድ ነው። ሌላም ሌላም። ብዙ ብዙ …

5- ከሁሉም በላይ አሁን ያለውም የኦሮሚያን መንፈስ አለመረዳት ነው።

ምን ይሁን

አማራ ክልልን እየመራ ያለው ሃይል አሁን ወደ ምርጫ እያዘገመ ነው። ህዝብ ብሶቱን ችሎ በፍትሃዊ ምርጫ ለማስወግድ በጥበብ መንቀሳቀስና ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ማድረግ። ምርጫው ደርሶ ውጤቱ እስከሚለይ ፍትህን በሚገባ መጠየቅ፣ ሌላ ጥቃት እንዳይደገም አንድ መሆን፣ ሌሎችን ምስኪኖችን በጅምላ አለመስደብ፣ ” የሰው ልክ፣ የሰውነት መጨረሻ፣ ተራራ…” የሚሉ ተራ ቀረቶ ማቆም። ከሁሉም በላይ በሌሎች አካባቢዎች ለፍቶና ጥሮ ግሮ የሚኖረው ማስኪን የአማራ ህዝብ ከዚህም በሰፋ መልኩ ሰላሙ እንዳይናጋ ጥንቃቄ መውሰድ፣ በደሉና ሃዘኑ እጅግ የሚያም ቢሆንም ሕመሙን በጥበብ ለማስታገስ መስራት የሚሻል ይሆናል። በአጭሩ በራስ ዙሪያ ማሰብ !! የራስንም ጉድፍ ማየት፤

ማስታወሻ – ከሆነው ነገር አንጻር ይህ ምስልና መፈክር ሊወዳደር አይችልም ሊባል ይችላል። ነገር ግን ” ኦሮሙማ ይወደም” ሲባል፤ “ኦሮሞነት ይውደም”እየተባለ ነው። ይህ ደግሞ ጥሩ ስሜት አይፈጥርም። ከለውጡ በሁዋላ በርካታ መዘዝ የመጣው በምላስ ወለምታ ነው። ይህ መፈክር የትኛውንም ኦሮሞ አያስደስትም። ከላይ እንዳልኩት የሆነው ነገር እጅግ የከፋ ነው። ያለ ምንም ማጋነን ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ የኦሮሞ ሕዝብን አያስደስትም። ጥቂት ጽንፈኞችና ኦሮሞ አንድ አይደሉም።

ጽሁፉ ነጻ አስተያየት ነው። የሚወክለውም የጸሃፊውን አሳብ ብቻ ነው


Exit mobile version