Site icon ETHIO12.COM

ሕገወጥ እርድ እስከ 25ሺህ ብር አልያም በእስር እንደሚያስቀጣ ተገለጸ


ሕገወጥ እርድ ላይ ተሰማርቶ የተገኘ ሰው እስከ 25ሺህ ብር አልያም በእስር እንደሚቀጣ የአዲስ አበባ አርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን አስታወቀ፡፡በ2012 ዓ.ም በተደረገ ጥናት ከተማዋ በአንድ ዓመት ውስጥ ብቻ በሕገወጥ እርድ ምክንያት 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ማጣቷም ይፋ ሆኗል፡፡

በትናንትናው ዕለት ኮሚሽኑ ከአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ጋር በመሆን በመጪው የፋሲካ በዓል ኅብረተሰቡ ከእርድ ጋር ተያይዞ ሊያደርግ ስለሚገባው ጥንቃቄ ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥቷል፡፡

መግለጫውን የሰጡት የአዲስ አበባ አርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ወይዘሮ ፍቅርተ ነጋሽ እንደገለፁት፤ በሕገወጥ እርድ ላይ የተገኘ ሰው ከ15 እስከ 25ሺህ ብር አልያም ከሁለት እስከ ሦስት ወር በሚደርስ እስር ይቀጣል፡፡

እንደ ምክትል ኮሚሽነሯ ገለፃ ወንጀሉን ሲፈፅም የተገኘ ድርጅት የተጣለበት ቅጣት እስከሚተላለፍ ድረስም ሥራ የሚያቆም ሲሆን ድርጅቱም ይታሸጋል፡፡

ሕገወጥ እርድ መንግሥት ማግኘት ያለበትን ገቢ እንዳያገኝና ኅብረተሰቡም ንፅህናና ጤንነቱ ያልተጠበቀ ስጋ እንዲመገብ እንደሚያደርገው የገለፁት ምክትል ኮሚሽነሯ ከተማዋ በአንድ ዓመት ውስጥ ብቻ በሕገወጥ እርድ ምክንያት 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር እንዳጣች በ2012 ዓ.ም በተደረገ ጥናት ይፋ ሆኗል ሲሉም ገልፀዋል፡፡

እንደ ምክትል ኮሚሽነሯ፤ ሕገወጥ እርድ የሚደረጉባቸው ስፍራዎች በጥናት ተለይተዋል፡፡ከሕግና ከሰው እይታ ለመሰወርም በቆሻሻ ስፍራዎች፣ ሸለቆና አሳቻ ቦታዎች፣ የእንስሳት ማሳደርያ በረቶች እና ሆቴሎች ጀርባ ሕገወጥ እርድ የሚከወንባቸው ስፍራዎች መሆናቸውንም ምክትል ኮሚሽነሯ ተናግረዋል፡ via (ኢ ፕ ድ)

Exit mobile version