Site icon ETHIO12.COM

“በትግራይ ያለው ገጽታ ከድሮውም የባሰበት አፈና ነው” ገብሩ አሥራት

“ኢሕአዴግ በጣም አምባገነን ፓርቲ እንዲያውም ጥንት ከነበሩ መንግስታት በተለየ ነው”

“ዲፋክቶ መንግስት ያዋጣል ብሎ የሚያስብ ፓርቲና ፖለቲከኛ እጅግ በጣም ለትግራይ ሕዝብ ጥፋት እየደገሰ ያለ ነው” አቶ ገብሩ አስራት የአረና ትግራይና የመድረክ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ከአዲስ ዘመን ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ መናገራቸውን ጋዜጣው ዘግቧል። የንግግራቸው አንኳር ሃሳቦች ከዚህ በታች በሚከተለው መልኩ ቀርቧል፤

• ሕወሓት ይፋዊ በሆነው ልሳኑ ወይን ጋዜጣ ላይ ዲፋክቶ መንግስት እንመሰርታለን ነው ያሉት።

• የሕወሓት አመራር ስለተቸገረና የኢትዮጵያ ፖለቲካ ስለተበላሸ እንገነጠላለን የሚለው ነገር የማያዋጣ ለሕዝብ የማይበጅ፤ ጥፋትን የሚያስከትል ነው ብዬ አምናለሁ።

• ዲፋክቶ መንግስት ማለት ሕገወጥ መንግስት ማለት ነው። ለሕወሓት አመራር ፤ ለአንዳንድ አክቲቪስቶች እንዲመች ሲባል የትግራይን ሕዝብ ወደ አልተፈለገ መንገድ እየመሩት እንዳሉ ሊሰመርበት ይገባል።

• ይሄ ትግራይን ነጻ እናወጣለን፣ ዲፋክቶ መንግስት (ኢ-መደበኛ ) የሆነ መንግስት ነው።

• ዲፋክቶ መንግስት በአለም መንግስታት እውቅና ፤ፓስፖርትና ቪዛ የለህም። መንቀሳቀስ አትችልም። ልትነግድ አትችልም፤ ሕገወጥ ነህ፤ ኢንቨስትመንት የሚባል ነገር የለም፤ የውጭ ኢንቨስትመንት አይኖርም። የውጭ ምንዛሪ ማንቀሳቀስ አትችልም፤ መጨረሻም ላይ ከጎረቤቶችህ ጋር ወደ ግጭት ወደ ጦርነት ውስጥ ነው የምትገባው።

• ባይሆን ኢትዮጵያ ውስጥ ችግር አለ፤ እንስማማበታለን። ችግሩን በጋራ መፍታት ነው ያለብን። ጥሩ ነገር ሲሆንም አብረን እንቋደሳለን። ችግር ሲኖርም አብረን እንካፈላለን።

• ጠላት መጥቶ ሲወረን አብረን ታግለናል። ጣሊያኖችን፤ ግብጾችን፤ቱርኮችን፤ ሁሉንም። ይሄንን ያደረገ ሕዝብ ነው።

• በፖለቲካ ረገድ ኢህአዴግ ቀድሞ ያስቀመጠው አሁንም በህወሓት በኩል እየቀጠለበት ያለው ነገር ሌሎችም ይሄ ሊኖራቸው ይችላል። ተፎካካሪ ፓርቲን ጠላት ብሎ ነው የሚፈርጀው።

• ኢህአዴግ አብዮታዊ ዲሞክራሲን ካልተቀበለ ህወሓት አሁንም ሞቼ እገኛለሁ እያለ ነው።

• አብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠላት፤ ወዳጅ፤ መሀል ሰፋሪ ብሎ ነው የሚፈርጀው። ስለዚህ ጠላትን ጠላት ካልከው እንደ ጠላት ነው የምታየው።

• በአብዮታዊ ዲሞክራሲ አትደራደርም፤ አትገናኝም፤ ታጠፋዋለህ። ይሄን ተከትሎ እየሄደ ያለ ፖለቲካ በሀገራችን ቅን የሆነ እና የሚያግባባ የሰለጠነ ፖለቲካ እናካሂዳለን የሚል እምነት የለኝም።

• ኢህአዴግ አብዮታዊ ተሞክሮ የወደቀን ነገር እንደገና ካልተቀበላችሁ የሚለው ነገር ስህተት ነው። ግን አቋሙ ስለሆነ ሊከበር ይገባል።

• ሕወሓት ፓርቲዎችን እየፈጠረ ተቃዋሚዎችን የሚያጠቃበት ሁኔታ አሁንም እንዳለ አውቃለሁ።

• ፓርቲዎች ይፈጠራሉ፤ ይወለዳሉ፤ይከስማሉ፤ ይሞታሉ ፤ ይፈርሳሉ። ሁልግዜም የሚኖረው ሕዝብ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሺ አመታት አብሮ መስተጋብር ያለው ሕዝብ ነው።

• የትግራይና የአማራም ሕዝብ አብሮ የኖረ ነው። አሁን ብዙ ፖለቲከኞችና አክቲቪስቶች ጭምር በኢትዮጵያ እያደረጉት ያሉትና መታየት ያለበት የሚመስለኝ የእነሱን የፖለቲካ ትርፍ ለሟሟላት የትግራን እና የአማራ ህዝብን በማጋጨት እንደ መሳሪያ እየተጠቀሙበት ነው።

• በጣም ጽንፍ በወጣ ፖለቲካ እየቀሰቀሱት ነው ያሉት። አማራም አካባቢ ትግራይም አካባቢ በሌሎችም ቦታዎች ይሄ ችግር አለ።

• ዋነኛው ሕዝብ የማሰባሰቢያ መንገድ ጽንፍ የሆነ ሕዝበኛነት(ፖፑሊስት) የሆነ እንቅስቃሴ ነው። ሕወሓትም ሆነ ሕወሀትን እንቃወማለን የሚሉ ጭምር ይህን እየተጠቀሙበት ነው።

• ኢሕአዴግ በጣም አምባገነን ፓርቲ እንዲያውም ጥንት ከነበሩ መንግስታት በተለየ እስከ ቤተሰብ ድረስ ወርዶ ሕዝቡን ለመቆጣጠር ሙከራ ያደረገ፤ መንግስትና ፓርቲን አንድ አድርጎ ለመሄድ የሞከረና አፈናው እጅግ በጣም ከፍተኛ ነበር ፓርቲ ነው።

• ስልጣኑን ተጠቅሞ ብዙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችና አፈናዎች ፤ የሀብት ምዝበራ ያካሄደ ድርጅት ነው።

• ሙስና ቀላል ቃል ነው። የበጀት ዝርፊያ ፤ የመሬት ዝርፊያ፤ ቅሚያ ሁሉ ያካሄደ ድርጅት ነበር። የኢትዮጵያ ሕዝብ አልተቀበለውም። እንዲወገድ ይፈልግ ነበር።

• በተለይ ከአራት አመት በፊት እንቅስቃሴው በጣም ጎልቶ ወጥቶ ሕዝብን እንደ ድሮው መግዛት ያልቻለበት ሁኔታ ተፈጠረ።

• ኢሕአዴግ ድሮም በህዝብ አልተመረጠም። የሕዝቡ ጫና ከፍተኛ ስለነበረ ኢሕአዴግ በውስጡ መሰነጣጠቅ ጀመረ።

• ይሄ 120 ፓርቲ የሚባል ነገር ጨዋታ ነው። አንዳንዱ የቤተሰብ ያህል የአባል ቁጥር የለውም።

• ኢ-መደበኛ አደረጃጀቶች የተስፋፉት መደበኛ ነጻ አደረጃጀት ስላልተፈቀደ ነው። ሰው ሲታፈን መውጫ ይፈልጋል።

• በአንዳንድ አካባቢዎች ከመንግስት ባለስልጣን ይልቅ አደረጃጀቶቹ የሚፈሩበትና የሚወስኑበት ከፈለጉ ሰው ሊገድሉ፤ ሊሰቅሉ፤ ሊያስሩ፤ ሊያፈናቅሉም ይችላሉ።

• እንኳን ተቃዋሚው መንግስትም የማይገባባቸው አካባቢዎች አሉ። ተቃዋሚዎች ሄደው የሚመቱበት። አዲስ አበባም ጭምር ስብሰባ ማድረግ የማይቻልበት ሁኔታ አለ።

• በትግራይ ያለው ገጽታ ከድሮውም የባሰበት አፈና ነው። በክልሉ የፖለቲካ ምህዳሩ ጭራሽ የተዘጋበት፤ እውነተኛ ተቃዋሚ ሁኖ መኖር የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሮአል።

• በዚህ ሁኔታ ምርጫ ማለት ጨዋታ ነው። እንደድሮው መቶ በመቶ ሕወሓት የሚያሸንፍበትን ሁኔታ ለመፍጠር እየተሰራ ነው።

• “እኔ አሸንፌአለሁ እና እነሱ እኔን ይከተሉ” የሚለው አካሄድ ነው ኢሕአዴግንም ሀገርንም ያጠፋው።

• ኢህአዴግ በሕዝቡ ተገዶ እንጂ ለውጥ ያመጣው ፍላጎቱ እኮ ለ40 አመት ለመግዛት ነበር ፕሮግራሙ።

• ሕወሓት ኢሕአዴግም ውስጥ እያለ ብዙ ፓርቲዎችን ፈልፍሎ የተቃዋሚ ተቃዋሚ ይፈጥር ነበር። ይሄ የሕወሓት ኢሕአዴግ ስልት ነው። ፓርቲው በዚህ የተካነበት ነው።

• ከእንግዲህ ይሄ ነገር አይሰራም። መሬት ላይ በቦታው የነበረው ፓርቲ አረና ነው። ለ12 አመታት ትግራይ ውስጥ የታገለ ሕይወት እየከፈለ ነው።

• ሕወሓት ድሮ ያደርገው እንደነበረ የተቃዋሚ ተቃዋሚ በመፍጠር ተቃዋሚዎችን የመምታት የመጋፈጥ ስራ አሁንም እየቀጠለበት መሆኑን አያለሁ።

• ዋናው በፖለቲከኞቻችን የከፋው ነገር ግን መደራደር የሚባል በሀገራችን አልተለመደም። ከመደራደር ይልቅ መጠፋፋት ነው የተለመደው። ስትደራደር ሰጥቶ መቀበል የሚባል ነገር አለ።

• የኢሕአዴግ እድሜ ወደ 30 አመት እየተጠጋው ነው። አንድ ትውልድ ማለት ነው። ያኔ የተወለደ ነው አሁን ያለው። እስቲ ራሱ መንገድ ይፈልግ። ይጠቅመኛል ያለውን መንገድ ራሱ ይነጋገር፤ ይቀይስ። ፈልጎ ያግኝ። እኛ ብንፈልግም መጫን አንችልም።

• እኛ ያልሰለጠነ ፖለቲካ ይዘን ስለምንሄድ ነው እንጂ የሠለጠንን ቢሆን ኖሮ ተቃዋሚ ሁኖ መቀጠል ይችላል። ለእኔ እንዲያውም አሁን የተፈጠረው ሁኔታ አንድ እድል ነው።

• ሕወሓት ዋናውን ማዕከል እስካልተረከብኩ ድረስ ኢትዮጵያን አምሳለሁ እያለ ነው። ማዕከላዊ መንግስትም ሕወሓት ካልገባ “አርማጌዶን ይፈጠራል” እያለ ነው።

• በህንድ ሀገር ትላልቆቹ ፓርቲዎች በሀገር ደረጃ ይሸነፋሉ። ግን ስቴቶችን ያሸንፋሉ። ያስተዳድራሉ። ይሄ አይነቱ ልምድ በሀገራችን መምጣት አለበት።

• የፌደራል ስርአት ነው እስካልን ድረስ አንድ ፓርቲ በሀገር ደረጃ ተሸንፎ በክልል ደረጃ ቢያሸንፍ ክልሉን ማስተዳደር ይችላል።

• በሕገመንግስቱ መሰረት እንዲያስተዳድር መፍቀድ። ይሄን ሀሳብ ሁለቱም አይቀበሉትም። ሕወሓት ማእከሉን ተቆጣጥሮ ኖሮ ስለነበር ይሄን እስካልተቆጣጠርኩ በሚል እንቅስቃሴው በክልሉ ብቻ ተወስኖ የሚቀር አይመስለኝም።

• ትግራይ ላይ ነጻና ፍትሀዊ ምርጫ ከተካሄደ ቢያንስ ብዙ መቀመጫዎችን እናሸንፋለን ብለን እናምናለን። ቀደም ሲል ሁለት ምርጫዎችን አካሂደናል። ምርጫዎቹ ፍጹም ተዘርፈዋል። አፈና የበዛበት ነበር። ታዛቢ እንኳን ማስቀመጥ አንችልም። ማሰርና ማዋከቡም ብዙ ነበር።

• ከትግራይ ዴሞክራሲያዊ ትብብር /ትዴት/ ጋር ተነጋግረናል። በመርህ ደረጃ አብረን ለመስራት የመግባቢያ ሰነድ ፈርመናል።

ምንጭ አዲስ ዘመን ታህሳስ 16 ቀን 2011 ዓ.ም

Exit mobile version