ETHIO12.COM

ፖሊስ የጎዳና ተዳዳሪ መስለው የሽብር ተልዕኮ የወሰዱ ያላቸውን አሰረ፤ የተያዙት በዝርፊያ ላይ የተሰማሩትን ጨምር 990 ናቸው

የአካባቢ አደረጃጀትና መረጃ ተጠርታሪዎቹን በቁጥጥር ስር ለማዋል ጉልህ ሚና አለው ተብሏል። ሕዝብ በፈቃደኛነት ወታደር እየሆነ ነው፤ የመረጃ ግንኙነቱ በየመንደሩ መዝለቁ ተሰምቷል

በአዲስ አበባ ከተማ የጎዳና ተዳዳሪ በመምስል የሽብር ተግባር ለማስፈፀም የሚንቀሳቀሱ ሰዎችን ጨምሮ ለፀጥታ ስጋት የሆኑ ከ900 በላይ ግለሰቦች መያዛቸውን ፖሊስ አስታወቀ። የተሰወኑት ግለሰቦች የጎዳና ተዳዳሪ በመምስል የሽብር ተግባር ለማስፈፀም ተልዕኮ ተቀብለው ሲንቀሳቀሱ እንደነበርም ተመክቷል።

በአዲስ አበባ ከተማ የጎዳና ተዳዳሪ በመምስል የሽብር ተግባር ለማስፈፀም የሚንቀሳቀሱ ሰዎችን ጨምሮ ልዩ ልዩ ወንጀሎችን በመፈፀም ለፀጥታ ስጋት የሆኑ ከ900 በላይ ግለሰቦችን ይዞ ምርመራ እያጣራ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጠቅሶ ኢዜአ ነው የዘገበው።

ኮሚሽኑ ከህዝብ የደረሰውን መረጃ መነሻ በማድረግ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት በጥናት ላይ በመመስረት በሰባት ክፍለ ከተሞች በተመረጡ 20 ቦታዎች ላይ ግንቦት 22 ቀን 2013 ዓ.ም ባከናወነው ኦፕሬሽን ቋሚ አድራሻ የሌላቸውና በዋና ዋና አደባባዮች እና በምሽት በሰዋራ ቦታዎች የተለያዩ ወንጀሎችን ሲፈፅሙ የነበሩ 999 ግለሰቦችን ይዞ ምርመራ መጀመሩን አስታውቋል፡፡

በቁጥጥር ስር ከዋሉት ግለሰቦች መካከል አብዛኞቹ ማስቲሽና ቤንዚን በመጠቀም እራሳቸውን በማደንዘዝ የትራፊክ እንቅስቃሴዎችን ሲያውኩ እንደነበር በተለይ ደግሞ የትራፊክ መብራት ካስቆመው ተሽከርካሪ ላይ ስፖኪዮ ገንጥለው እንደሚወስዱ፣ ከአሽከርካሪ ወይም ከተሳፋሪ ላይ ሞባይል ስልክ፣ የአንገት ሃብል፣ ቦርሳ እና ልዩ ልዩ ንብረቶችን ቀምተው እንደሚሰወሩ ማረጋገጡን ገልጿል።

በተለይም ሴት አሽከርካሪዎች አደጋ ሳያደረሱባቸው አደጋ እንዳደረሱባቸው በማስመሰልና በማዋከብ ገንዘብ እንደሚቀበሉ፣ የትራፊክ አደጋ ሲያጋጥም ልዩ ልዩ ስልቶችን በመጠቀም ንብረቶችን እንደሚሰርቁ በጥቅሉ ትኩረታቸውን በዋና ዋና አደባባይ የትራፊክ መብራት በያዘው ተሽከርካሪ ላይ አድርገው ወንጀል ሲፈፅሙ እንደነበር ኮሚሽኑ ከህዝብ ከደረሰው ጥቆማና ባደረገው ጥናት ማረጋገጡን አመልክቷል።

ግለሰቦቹ በምሽት የቅሚያ ወንጀል ሲፈፅሙ እንደነበር መረጋጋጡ በተለይ ደግሞ የውጪ ሀገር ዜጎችንና የዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡን በማዋከብና በማስጨነቅ በከተማዋ መልካም ገፅታ ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ሲፈጥሩ እንደነበር የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታውቋል፡፡

የተሰወኑት ግለሰቦች የጎዳና ተዳዳሪ በመምስል የሽብር ተግባር ለማስፈፀም ተልዕኮ ተቀብለው ሲንቀሳቀሱ መገኘታቸውንም ኮሚሽኑ ገልጿል።

በከተማዋ የሚስታወሉ መሰል ስጋቶችን ለመቀነስ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር የሚደረገው ህግን የማስከበር ተግባርና በተጠርጣሪዎቹ ላይ እየተደረገ ያለው ምርመራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል፣ በወንጀል ተጠርጥረው ከተያዙት ግለሰቦች መካከል እንደ ድርጊታቸው መጠንና ስፋት በህግ የሚጠየቁት እንተጠበቀ ሆኖ እድሜያቸው አነስተኛና በወንጀል ድርጊት ተሳትፏቸው እጅግ ቀላል የሆኑት ደግሞ ከሚመለከተው የአስተዳደር አካል ጋር በመቀናጀት የተሃድሶ ስልጠና እንደሚሰጣቸው ፖሊስ ገልጿል፡፡

ኮሚሽኑ የከተማዋን ሰላምና ደህንነት የማስጠበቅ ተግባሩን አጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን ነዋሪው ለሰላም ስጋት የሆኑ ግለሰቦችን በመጠቆምና ማስረጃ በመሆን ተባባሪነቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጥሪ አቅርቧል፡፡


Exit mobile version