Site icon ETHIO12.COM

በዚህ ጊዜ ውስጥ ሁሉ የሚደንቀኝ የጠ/ሚ አብይ አህመድ የተለመደ መረጋጋት ነው

በአገራችን ጉዳይ አንድ ችግር ሲገጥመን ብዙዎቻችን እንሸበራለን፤ መቀመቅ የገባን ያህል ይሰመናል፤ ያበቃልን ያህልም እንቆጥራለን።

የችግሩ ፈጣሪዎች ደግሞ ማን ያክለናል ሲሉን ሰምተናል። ነገር ሁሉ በጭብጣችን ውስጥ ነው ብለው አስፈራርተውናል። ምን ልናደርግ እንደምንችል ብዙም ሳትቆዩ ታያላችሁ ብለውም በድፍረት ነግረውናል።

በዚህ ጊዜ ውስጥ ሁሉ የሚደንቀኝ የጠ/ሚ አብይ አህመድ የተለመደ መረጋጋት ነው። የእሳቸው መረጋጋት ብቻ ሳይሆን ሕዝቡንም ማረጋጋት መቻላቸው ነው።

ብዙዎቻችን ተጨንቀን ሳለን ምንም የተፈጠረ አይመስላቸውም። ይባስ ብለው ወቅቱ ከሚጠይቀው ውጭ በሆኑ ሥራዎች ተጠምደው ሳይ ግርም ይለኛል። አንዳንዴም እኒህ ሰው ትኩረት ከሚሻው ሥራ ውጭ ሆነው እንዳያስበሉን እላለሁ።

በእኔ ግምት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሚያስደነግግ ችግር ተፈጥሮ እሳቸው የልማት ሥራዎችን ሲጎበኙ ሳይ ደነግጣለሁ። ሱዳን መሬታችንን በወረራ ይዛ የሆነው ይኸው ነው።

እንደወትሮው እኛ በሀሳብ ተዉጠን እሳቸው እንደ አገር መሪ ምንም የተፈጠረ ያልመሰላቸው ሆነው ታይተዋል።

እኛ ኢትዮጵያ ለመበታተን በቋፍ ላይ ነች ብለን አስበን ስንጨነቅ፣ አትጠራጠሩ ኢትዮጵያ አትፈርስም። የሚፈርሱት ሊያፈርሷት የሚፈልጉ ናቸው ይሉናል።

ብዙ ማውራት አይስተዋልባቸውም፣ ፉከራም ቀረርቶም አያሰሙም። አለም ይወቅልኝ ይስማኝ ብለው ብዙም ሲማጸኑ አይደመጡም። ሕዝቡንም አያሸብሩትም

መነገር የሚገባው ነገር እንኳን ቢኖር ከእሳቸው በታች ባሉ ሀላፊዎች ወይም ቃል አቀባዮች ሲገለጽ ነው የምንሰማው። ይህ ሁኔታ በብዙ መሪዎች ዘንድ የሚስተዋል አይደለም።

ይህ ባለመሆኑ፣ ነገሮች የሚፈለገውን ትኩረት አያገኙም። በዚህም አገር ይጎዳል ብለን የምናስብ ብዙዎች እንደምንሆን እገምታለሁ።

እሳቸው ስለሆነ ነገር መናገር ካለባቸው ብዙን ጊዜ የሆነ አጋጣሚን ተጠቅመው ካልሆነ ለጉዳዩ የተለየ ጊዜ አዘጋጅተው አይደለም።

እነዚህ ሁኔታዎች ስለሚገርሙኝ ምክኒያታቸውን ለማወቅ እራሴን ብዙ ጊዜ ጠይቄ ለእራሴ ግምታዊ ምላሽ ከመስጠት በስተቀር ትክክለኛውን መልስ ማግኘት የምችልበትን እድል አላገኘሁም።

ሰውዬው የአንድን ነገር መከሰት በጣም ቀድመው የሚያዉቁ እና የሚያውቁበት መንገድም ያላቸው ይመስለኛል።

ማወቅ ብቻ ሳይሆን ለነገርዬው ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት የሚያስችላቸዉን አስፈላጊውን ዝግጅት የሚያደርጉ ይመስለኛል። ይህን ለማድረግ እንቅልፍ የላቸውም። ሲበዛም ትጉህ ይመስሉኛል።

በእሳቸው ዘንድ ሰርገኛ መጣ ብሎ ነገር ያለ አይመስልም። ዝግጅታቸውም ዘመናዊ አስተሳሰብን፣አሠራርን፣ አደረጃጀትን፣ ቴክኖሎጂን በከፍተኛ ደረጃ ግምት ያስገባ ሳይሆን አይቀርም።(ድሮን

ይህን በማንኛውም ሥራቸው ግምት እንደሚያስገቡ መገመት አያዳግትም። ከዚህ ጋር የክትትል ሥራቸው እና የማሠራት አቅማቸው ቀላል አይመስለኝም።

ከውጤት በፊት ስለ ሥራቸው ብዙ ስለማይናገሩ እና ሙያ በልብ የሚለውን መርህ ስለሚከተሉ፣ ተገዳዳሪዎቻቸው ብዙ ቦታ ሊሰጧቸው አይፈልጉም። ምናልባትም ሳይንቋቸው አይቀርም። ይህ ደግሞ ለእሳቸው ጠቅሟቸዋል።

ከሚያደርጉት ዝግጅት ጎን ለጎን የበዛ ትእግሥታቸው፣ የሕዝብን ድጋፍ እንዲያስገኝላቸው እና ፍትሀዊነትን ሳያላብሳቸው አልቀረም ብዬ እገምታለሁ።

የተሟላ ዝግጅታቸው ደግሞ በራስ የመተማመን እና የአሸናፊነትን ስሜት እንደሚያጎናጽፋቸው መገመት አያዳግትም።

ባልተለመደ መልኩ ከሕዝብ ጋር የሚያደርጉት ግኑኝነት፣ ንግግር አዋቂነታቸው እንዲሁም ያሉትን በተግባር የማሳየት አቅማቸው እና ትህትናቸው ከሕዝብ የማይናቅ ድጋፍ ሳያስገኝላቸው አልቀረም።

ለዚህ ሊሆን ይችላል እኛ ስንጨነቅ እሳቸው አስቀድመው ያወቁት ፣ የተዘጋጁበት እና ውጤቱንም ከሞላ ጎደል ያወቁት ነገር ብዙም የማያስጨንቃቸው።

ለእኛ አዲስ የሆነብን ነገር ለእሳቸው የቆየና የተለማመዱት እንዲሁም ውጤቱንም ያወቁት ሊሆን ይችላል።

አንድ መሪ ሊኖረው ከሚገባው ባህሪያት እና አቅሞች መካከል አንዱ ይህ ይመስለኛል። እሱ ቀድሞ ሕዝብን መምራት እና ማሻገር።

በሰሜን የተከናወነው የሕግ ማስከበር ሥራ፣ የሕዳሴ ግድብ እና በሱዳን የግዛታችን መወረር አያያዝ ጉዳይዮች በአብነት የሚነሱ ናቸው።
በእነዚህ ሁኔታዎች ውስጥም ሆነን በአገሪቱ ውስጥ የማይናቁ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውም ከግምት የሚገባ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአዲስ አበባ ከተማ እየተካሄዱ ስላሉ አስደማሚ የልማት ሥራዎች በመገናኛ ብዙሀን አማካኝነት እንደ አንድ ባለሙያ የሰጡት ማብራሪያ በዉስጤ የቆየውን ነገር እንድጽፍ ምክንያት ሆነኝ።

Via Berhanu Assefa FB

Exit mobile version