Site icon ETHIO12.COM

በአዳማ ከተማ የምርጫ ሂደቱን ለማወክ በመሞከርና በምርጫ ጣቢያ የጦር መሳሪያ ይዞ በመገኘት የተከሰሱ ተቀጡ

በአዳማ ከተማ የምርጫ ሂደቱን ለማወክ በመሞከርና በምርጫ ጣቢያ የጦር መሳሪያ ይዞ በመገኘት የተከሰሱ ሁለት ግለሰቦች በእስራትና በገንዘብ ተቀጡ።

የአዳማ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ከፍተኛ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ኢንስፔክተር ወርቅነሽ ጋልሜቻ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ግለሰቦቹ የተቀጡት ሰላማዊውን የምርጫ ሂደት ለማወክ በመሞከርና ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ይዞ በመገኘት ወንጀል ተከሰው ፍርድ ቤት ቀርበዋል።

ስንታየሁ ዑርግዬ የተባለ ግለሰብ በአዳማ ከተማ አባገዳ ክፍለ ከተማ ኦዳ ቀበሌ ምርጫ ጣቢያ የጦር መሳሪያ ይዞ በመገኘቱ በአዋጅ ቁጥር 1177/2011 ዓ.ም የተቀመጠን ክልከላ በመጣስ ወንጀል ተከሶ መቀጣቱን ተናግረዋል።

በተመሳሳይ በዚሁ ክፍለ ከተማ በምርጫ ጣቢያ ስድስት ከጠዋቱ 2:40 ላይ ከማል አብዶ የሚባል ግለሰብ ድምፅ ሰጪ መስሎ ድምፅ መስጫ ጣቢያው ድረስ በመግባት ሂደቱን ለማወክ ጥረት በማድረጉ መቀጣቱን አመልክተዋል።

በምርጫ ወቅት ሊኖሩ የሚችሉ ወንጀሎችን ለመመልከት የተቋቋመው የአዳማ ወረዳ የወቅታዊ ጉዳይ ችሎት ግለሰቦቹ በእስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቀዋል።

ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ይዞ የተገኘው ስንታየሁ ዑርግዬ በአንድ ዓመት እስራትና በ5 ሺህ ብር መቀጣቱን ተናግረዋል።

ምርጫውን ለማስተጓጎል የሞከረው ከማል አብዶ የተባለ ግለሰብ ደግሞ በስምንት ወር እስራት መቀጣቱን ኢንስፔክተር ወርቅነሽ አስታውቀዋል። ENA

Exit mobile version