Site icon ETHIO12.COM

ትህነግ ለድርድር ባቀረበው ቅድመ ሁኔታ ኦሮሞ ተባባሪዎቹን ከዳ “ደግ አደረጉ፤ ዋጋቸውንም ሰጣቸው”

ከተፈጠረ ጀምሮ ራሱን የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ብሎ የሚጠራው ትህነግ ከስልጣን ከተባረረ ሶስት ዓመት በሁዋላ “ አሸባሪ” ተብሎ መፈረጁ ይታወሳል። ሃያ ሰባት ዓመት ኢትዮጵያን ሲመራም የተገንጣይ ስም ይዞ የነበረው ትህነግ ስሙን ለምን እንደማይቀይር የበርካቶች ጥያቄ ሆኖ ኖሯል። ይህ ሃይል ወደ መቀሌ ከተመለሰ በሁዋላ ሰባት ነጥብ ቅደም ሁኔታ አስቀምጦ የተኩስ ማቆሙን እንደሚቀበል ዛሬ ይፋ አድርጓል። መግለጫው አሜሪካና ወዳጆቿ፣ ዕርዳታ ሰጪዎችና ተመድ ከሚሉት፣ የትህነግ ደጋፊ ሚዲያዎች ከሚናገሩት ሃሳብ ብዙም የተለየ ነገር የለውም ተብሏል። የኦሮሞ አክቲቪስቶችና እስር ቤት ሆነ በጾም ጸሎት ሲያስቧቸው የነበሩትን ፖለቲከኞች አላነሱም።

ትህነግ መንግስት ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ የተኩስ አቁም እርምጃ መውሰዱን በመርህ ደረጃ መቀበሉን አመልክቶ ባሰራጨው መግለጫ ተኩስ አቁሙን በሙሉ ልቡ ለመቀበል ቅድመ ሁኔታ ያላቸውን ይፋ ከማደርጉ ቀደም ሲል ኒውዮርክ ታይምስና ሌሎች ሚዲያዎች ትህነግ በድርድሩ ጡንቻው የፈረጠመ እንደሆነ ትንተና ሲሰጡ ነበር። በትንተናቸውም ክፉኛ ሲያሞግሱት የኢትዮጵያን ሃይል አንኳሰዋል።

ከዚሁ የቅሰቀሳ ትንተና በሁዋላ አቶ ጌታቸው ይፋ ያደረጉት ቅድመ ሁኔታ ያስቀመጠ መግለጫ የትግራይ ክልላዊ መንግስት እንዳወጣው ያናገራል።

መንግስት የትግራይ ሕዝብ ያለበትን ክፉ ሁኔታ በማገናዘብ፣ የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ባቀረበው ጥያቄ መሰረት፣ ሰብአዊነትን በማስቀደም የተናጠል የተኩስ አቁም በማድረግ የመከላከያ ሰራዊት ትግራይን እንደለቀቀ አውጇል። ይህንኑ ተከትሎ ከበረሃ ወደ መቀለ የገባው ሃይል”ያለ ቅድመ ሁኔታ ዓለም አቀፍ በረራዎች በትግራይ ከሚገኙ አየር ማረፊያዎች በቀጥታ ጉዞ እንዲያደርጉ መፈቀድ” አለበት ብሏል።

መንግስት ከትናት በስቲያ ከዓለም አቀፍ ተቋማትና ዲፕሎማቶች ጋር ባደረገው ውይይት፣ እርዳታ ሰጪዎች፣ ለጋሾች ወደ ትግራይ በአውሮፕላን መጓዝና ማጓጓዝ እንደሚችሉ፣ መንግስት ወድ ትግራይ ከመነሳታቸው በፊት ግን አስፈላጊውን የደህነትና የጸጥታ ፍተሻ እንደሚያደርግ፣ በትግራይ ክልል ለሚሆነው ማናቸውም ጉዳዮች ግን ሃላፊነት እንደማይወስድ በይፋ ማስታወቁን አቶ ሬድዋን ይህ ጥያቄ ከትህነግ ከመቀረቡ በፊት አስቀድመው ለጠየቋቸው ነጮች አስረድተዋል። በጥያቄው መሰረት የማያስማማው ፍተሻን የመቀበልና ያለመቀበል ጉዳይ እንጂ በመርህ ደረጃ ዲፕሎማቶቹ አሳቡን መቀበላቸው ተመልክቷል።

የኤርትራና የአማራ ክልል የጦር ሰራዊት አባላት ከጦርነቱ በፊት ወደነበሩበት ስፍራ እንዲመለሱ፣ በጦርነቱ ተሳትፈዋል የተባሉና የሰብአዊ መብት ጥሰትን ፈጽመዋል በሚል የሚከሰሱትን አስመልክቶ በገለልተኛ ወገን ማጥራት እንዲካሄድ ትህነግ ጠይቋል። ማይካድራን ስለማካተቱት ግን ግልጽ አይደለም። ትህነግ በማይካድራ ለፈጸመው ወንጀል ምንም ሳይባልና ምንም ሳይል ዳግም እንዴት ማይካድራ ስለመመለስ ይመኛል የሚል አስተያየት ወዲያው ተሰራጭቷል።

መንግስት የተባበሩት መንግስታትና የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ጉዳዩን በጋራ እንዲያጣሩ መፍቀዱንና ማንኛውንም ድጋፍ እንደሚያደርግ፣ እንዲሆም አቃቤ ህግ ምርመራ አካሂዶ ሪፖርት ማቅረቡንና ጥፋተኛ ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ ተይዘው ምርመራ እየተደረግባቸው እንደሆነ ማስታወቁ ይታወሳል። ትህነግ ምርመራ እንዲካሄድ ሲጠይቅ ከዚህ የተለየ በምን መልኩ እንደሚሆን አላሳወቀም።

ትህነግ ሌላ ቅድመ ሁኔታ ሲል ያቀረበው የቴሌኮሙኒኬሽን ፣ የመብራትና ሌሎች የተቋረጡ አገልግሎቶች ዳግም ወደ መደበኛ መስመራቸው እንዲመለሱ፣ያለምንም ገደብ የሰብአዊ እርዳታ የሚቀርብበት መንገድ እንዲመቻችና ከቤት ንበረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖች ወደ ቀድሞ ቀያቸው እንዲመለሱ ነው። አክሎም የዓመቱ በጀት እንዲለቀለት ጠይቋል።

የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ሁሉም ዓይነት  ድርድሮች መሰረታቸው የአገሪቱን ሕገ መንግሥት መሰረት አድርጎ እንደሆነ አመልክቷል።” የማይደረግ” በሚል ስሜት የማእከላዊ መንግሥት ወታደራዊና የጸጥታ ኃይል ወደ ትግራይ ክልል እንዳይገባም ጠይቋል።

የኢትዮጵያ መንግስት ህገ-መንግስታዊው የማስተዳደር ስልጣኑ መስከረም 2013 ላይ ስላበቃ፣ በፓርላማ እና በፌዴራል ፍርድ ቤቶች የተላለፉ ማንኛውም ህጎች አይሰሩም፤ በእስር የሚገኙ የትግራይ ፖለቲከኞች፣ ትግራዋይ የኢትዮጵያ የመከላከያ ጦር አባላት ከእስር አሁኑኑ እንዲፈቱ ሲልም ጠይቋል።

በጥቅምት 24 ቀን 2013 አቶ ሴኮ ቱሬ እንዳረጋገጡትና ከጥቃቱ የተረፉ እንደመሰከከሩት ትህነግ በአገር መከላከያ ሰራዊት ላይ በድንገት ጥቃት ሰንዝሮ በአሰቃቂ ሁኔታ ጭፍጨፋ መፈጸሙን ተከትሎ በተጀመረ ጦርነት ይፋ ያልሆነ ህይወት አልፏል።

ትህነግ ወደ ስልታን ሲመጣ ያካለላቸውና አዲስ ካርታ ሰርቶ የራሱ እንዳደረጋቸው የሚገልጸው የወልቃይት፣ የጠገዴ፣ ጠለምትና ራያ ጉዳይ የተዘጋ ፋይል መሆኑንን የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ይፋ አድርገዋል። ፓርቲያቸውም “ ጸቡ ከመላው አማራ ጋር ነው” ሲል ትህነግ በሃይል እልማስመለስ የሚሞክር ከሆነ አስፈላጊውን ምላሽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን መናገራቸውን ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።

የገንዘብ ተቋማትና የባንክ አገልግሎቶችን በተመለከተ ልክ ትህነግ ያነሳው ጥያቄ ቃል በቃል በዲፕሎማቶች ቀርቦ ነበር። አሁን ላይ መንግስት ባለመኖሩ ገንዘብ ተሸክሞ ወደ ትግራይ መግብባት ወይም ሰዎች መመደብ ወይም ሄደው እንዲሰሩ ማስገደድ እንደማይቻል፣ በራሱ ተነሳሽነት ለመስራት ፈቃደኛ የሚሆን ባንክ ካለ ግን ድጋፍ እንደሚያደረግ፣ ባንኮች አትራፊ ድርጅቶች በመሆናቸው ሃላፊነት ለመውሰድ እንደሚያስቸግር አቶ ሬዲዋን ከትናት በስቲያ መልስ ስጥተው ነበር።

ሰዎቻቸው እንዲፈቱ ከመጠየቃቸው ውጪ በአብዛኛው ማለት በሚቻል ደረጃ አዲስ አሳብ የሌለው የትህነግ መግለጫ አሜሪካና ሌሎች አገሮ፣ እንዲሁም የርዳታ ድርጅቶች የሚያነሱት ጥያቄ ተጨምቆ የቀረበ ይመስላል። መንግስት ምን ምላሽ እንደሰጠ ይህ እስከታተመ ድረስ አልታወቀም።

አስቀድሞ ትህነግ የታሰሩ የኦሮሞ ፖለቲከኞች እንዲፈቱ ቅድመ ሁኔታ ያስቀምጣል በሚል ሲያስተጋቡና በተጋሩ የፓልቶክ ሚድያ ሳይቀር በስፋት ” ኦሮሞን ይዘን አማራውን …” በሚል ሃሳብ ይሰጡ ስለነበር በድርድሩ ጉዳይ ቅድሚያ የፖለቲካ ካርድ ያደርጓቸዋል ተብሎ ነበር። የዘወትር የኢትዮ 12 ተባባሪ አቶ ገመቹ እንዳለው ” ይበላቸው። እንኳንም በአደባባይ ዓለም እያየ ካዱዋቸው” ሲል አስተያተቱ ሰንዝሯል። አያይዞም በኦሮሞ ጉዳይ ትህነግን ከጸሃይ በታች እንደማያምንና በኦሮሞ ህዝብ ላይ የሰሩትን ግፍ፣ ኤርትራ ድረስ ተሰዶ የደረሰበትን ግፍ ጠቅሶ በቀላሉ ሊረሳው እንደማይችል አመልክቷል። ይህ የመጨረሻው ትምህርት እንደሆነም አመልክቷል። በስፋት ቃለ ምልልሱን ይዘን እንመጣለን። አቶ ገመቹ ኤርትራ ስድስት ዓመት ቆይቶ በአንድ አጋጣሚ ራሱን ነጻ ያደረገ ታጋይ ነው።



Exit mobile version