Site icon ETHIO12.COM

የግብረ-ሶዶም ጥቃትና የአስገድዶ መድፈር ወንጀል የፈፀመው በ16 ዓመት ፅኑ እስራት ተቀጣ

በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የሚስቱ ለጆች (የእንጀራ ልጆቹ) በሆኑ የ10 እና የ13 ዓመት ወንድና ሴት ህፃናት ላይ የግብረ-ሶዶም ጥቃትና የአስገድዶ መድፈር ወንጀል የፈፀመው ተከሳሽ በ16 ዓመት ፅኑ እስራት አንዲቀጣ ተወስኖበታል።

የዐቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው ሀብታሙ ገብረ ጊዮርጊስ ገብረስላሴ የተባለው ተከሳሽ የወንጀል ህግ አንቀፅ 631(1) (ለ) እና 4 (ሀ) እንዲሁም አንቀፅ 620(2) (ሀ) እና (ለ) ላይ የተመለከቱትን ድንጋጌዎች በመተላለፉ በሁለት ወንጀሎች ላይ ክስ ተመስርቶበታል ።

ተከሳሹ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው አቢሲኒያ ትምህርት ቤት አካባቢ ከሚገኘው መኖርያ ቤታቸው ውስጥ ጥር 01/2013 ዓ.ም ከምሽቱ 2፡30 ሰዓት ላይ የ10 ዓመቱን የሚስቱን ልጅ (የእንጀራ ልጁ) ላይ የግብረ ሰዶም የፈጸመበት እንዲሁም በሁለተኛ ክስ ላይ ደግሞ የ13 ዓመቷን የሚስቱ ልጅ (የአንጀራ ልጁ) ላይ ህጋዊ ሚስቱ የማትኖርበትን ግዜ እየጠበቀ በተለያየ ሰዓትና ቀን ለማንም ብትናገሪ እገልሻለሁ በማለትና በማስፈራራት አፏን በጨርቅ እያፈነ የአስገድዶ መድፍር ወንጀል ይፈፅምባት አንደነበር የዐቃቤ ህግ የክስ መዝገብ ያስረዳል።

የዐቃቤ ህግን ክስ የተመለከተው የፌዴራሉ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት 7ኛ ምድብ ወንጀል ችሎት ለተከሳሽ ክሱ ተነቦለት የእምነት ክህደት ቃሉን ሲጠየቅ ድርጊቱን ሙሉ በሙሉ ያላመነ በመሆኑ ዐቃቤ ሕግ የሰው እና የሰነድ ማስጃዎቹን አቅርቦ አሰምቷል፡፡ በዚሁም መሰረትም ፍርድ ቤቱ እንዲከላከል የሰጠውን ብይን ተከትሎ ተከሳሹ የዐቃቤ ህግን ማስራጃዎች ማስተባበል ባለመቻሉ በተከሰሰበት ድንጋጌ ስር ጥፋተኛ በሚል የጥፋተኝነት ውሳኔ ሊተላለፍበት ችሏል፡፡

በስተመጨረሻም ግራ ቀኝ የቀረቡትን የቅጣት አስተያየቶች ከግምት አስገብቶ ፍርድ ቤቱ ተከሳሹን በ16 ዓመት ጽኑ እስራት እንዲቀጣ ወስኖበታል፡፡

Attorney general Fb

Exit mobile version