Site icon ETHIO12.COM

ለትግራይ ጄኔራሎች- “አይ” ካላችሁ ግን ውርድ ከራሴ ብያለሁ

የምትከተሉት የውጊያ ስልት ያረጀና ያፈጀ ነው። የመጨረሻ ውጤቱም ትግራይን ትውልድ አልባ የሚያደርግ ነው። ለዚህ ማስረጃው ደግሞ አፋር ላይ “ክተት” ብላችሁ ልካችሁት እንደ ቅጠል ረግፎ የቀረው ወጣት ነው።

የሰው ማዕበል ስትራቴጂ በዚህ የቴክኖሎጂ ዘመን የሚያስገኘው ውጤት ኢምንት ነው። የሰው ማዕበል በአንድ ድሮን፣ በአንድ የአውሮፕላን ቦንብ ወይም በዘመናዊ አውቶማቲክ መሳሪያ ይበተናል። አፋር ላይ የሆነውም ይኸው ነው።

ባለፈው ህዳር ወር ላይ ያሰለፋችሁት ወጣት እንደ ቅጠል የረገፈው ጥንዚዛ በሚያካክሉ ድሮኖች ነው። እናንተ ደግሞ እንኳንስ ድሮንና አውሮፕላን የመግዛት አቅም ላይ ልትደርሱ ቀርቶ፣ ገና ከዱቄትና ሽሮ ዘረፋ አልወጣችሁም።

ልብ በሉ! አንድ ሚሊዮን የሰው ማዕበል እናሰልፋለን ብትሉ እንኳን፣ መንግስት የእናንተን 20 እጥፍ ማሰለፍ እንደሚችል እወቁ። እናንተ የምታሰልፉት ሃይል ከ6 ሚሊዮን ህዝብ መሃከል የሚውጣጣ ሲሆን፣ መንግስት የሚያሰልፈው ሃይል ደግሞ ከ110 ሚሊዮን መካከል እንደሚውጣጣ ትዝ ይበላችሁ። ይህንንም በተግባር እያያችሁት ነው። የህዝብ ማዕበል ስትራቴጂ እንደ እናንተ አነስተኛ የህዝብ ቁጥር ላለው ማህበረሰብ አይሰራም።

እናንተ በመራችሁት የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት የሰው ማዕበል ታክቲካችሁ ስንትና ስንት የኢትዮጵያን ወጣቶች እንደጨረሰ የምታውቁት ነው። ባለፉት 8 ወራት ብቻ በ10ሺ ዎች የሚቆጠሩ የትግራይ ልጆች እንደረገፉም ታውቃላችሁ።

ምናልባት እንደ በፊቱ እራሳችሁን መሪ፣ ሌሎችን ደግሞ ጎማ አድርገን አዲስ አበባ እንገባለን ብላችሁ ካሰባችሁ፣ ይህ እንደማይሆን የድሮ ጎማዎቻችሁን እነ ታምራት ላይኔና ያሬድ ጥበቡን ጠይቋቸው።

የኢትዮጵያ ህዝብ “ ስልጣን ከምርጫ ውጭ ወደ ውጭ” ብሏል። ከሁሉም በላይ የእናንተ የዘረኝነትና የዝርፊያ ስርዓት ተመልሶ እንዲመጣ የሚመኝ የዚህ ትውድል ሰው የለም። የታሪካችሁ እስረኛ መሆናችሁ እንኳን ገና አልተረዳችሁም። የኢትዮጵያ ህዝብ ለእናንተ የሚከፈት ልብም ኪስም የለውም። የእናንተ የማገናዘብ አቅም መሳሳት፣ የትግራይን ህዝብ በቀላሉ ሊተካው የማይችል ዋጋ እያስከፈለው እንደሆን ተረዱ።

የኢትዮጵያ መንግስት እያደረገ ካለው ዝግጅት አንጻር ሳየው፣ በትግራይ ወጣት ላይ የሚደርሰው እልቂት ያስፈራኛል። ኢትዮጵያን ለመለወጥ እገዛ ሊያደርግ ይችል የነበረው የትግራይ ወጣት በዚህ ደረጃ ህይወቱን ሲያጣ ያሳዝናል።

ትንሽም ቢሆን ማገናዘብ የምትችሉ የጦር አበጋዞች ፣ ጦራችሁን ዘቅዝቃችሁና ነጭ ጨርቃችሁን አውለብልባችሁ ብትመጡ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ማህሪ ነው ይቅር ይላችኋል።

Via Fasil yenealem

Exit mobile version