Site icon ETHIO12.COM

ልዩ የጥንቃቄ መልዕክት ከአማራ ፓሊስ ኮሚሽን

አሸባሪው ትህነግ ሰርጎ ገቦችን በማሰማራት የሰራዊቱ ደጀን የሆነውን ህዝባችን በሥነ-ልቦና ለመጉዳት፣ እንዲሁም መረጃ በማድረስ ለሽብር ተግባሩ እየተጠቀመበት እንደሚገኝ መረጃዎች ይጠቁማሉ። በጦር ግንባር ካለው በተጨማሪ ባልወረራቸው አካባቢዎችም የጸጥታ ችግሮችን ለመፍጠር ልዩ ልዩ ጥረቶችን ሲያደርግ፣ በሕዝባችን ጥቆማና በጸጥታ ኃይላችን ክትትል በተደጋጋሚ ሊከሽፍበት ችሏል።

አሁን ባለንበት ተጨባጭ ሁኔታ፣ አካባቢያችን ከትህነግ ሰርጎ ገብ ነቅቶ መጠበቅ የሕልውና ዘመቻው አንዱ አካል ነው።

በመሆኑም፦

1) የአሸባሪው ትህነግ ሰርጎ ገብ ሰላማችን ያስከብሩልናል ብለን የምናምናቸውን የጸጥታ ኃይሎች መለዮ በመልበስ ወይንም በመመሳሰል ከቦታ ቦታ ለመንቀሳቀስ ጥረት ያደርጋል። የጸጥታ ኃይላችን በዕዝና ስምሪት የሚመራ ስለሆነ ሰርጎ ለመግባት፣ አሊያም ለማምለጥ ከሚሞክረው ኃይል የተለየ እንቅስቃሴ ያለው ነው። በመሆኑም በተለይ በገጠሩ የክልላችን ክፍል የጸጥታ ኃይሉ በዲሲፕሊንና በዕዝ ከሚያደርገው ስምሪት ውጭ በመመሳሰል የሚንቀሳቀስ ወይንም የሚያጠራጥር ጉዳይ ሲገኝ ለጸጥታ ኃይሉ ጥቆማ ማድረግ፣ የሚቻል ከሆነም ማንነቱን የሚገልጽ መረጃ (የቀበሌ መታወቂያ) በመጠየቅ ማረጋገጥ ያስፈልጋል።

2) አሸባሪው ትህነግ በሕዝብ ዘንድ የሚከበሩ ማንነቶችን በመላበስ የሚንቀሳቀስባቸው አጋጣሚዎች አሉ። ለአብነት የእምነት አባት በመምሰል፣ የምንወዳቸውን ምልክቶች (መስቀል፣ ወዘተ) በመያዝና በመጎናጸፍ እንዳይጠረጠር በአለባበስ ራሱን ለመቀየር ይሞክራል። መሰል ማህበራዊ እሴቶችን በመሳሪያነት ተጠቅሞ ያልተለመዱና አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርግ የታየን አካል ጥቆማ ማድረግ፣ ወይንም ማንነቱን ማረጋገጥ ተገቢ ነው። በተለይም በጸበል ቦታዎችና መሰል አካባቢዎች የሚኖሩ እንቅስቃሴዎችንና ጸጉረ ልውጦችን መከታተል፣ ጥርጣሬዎች ሲኖሩ በቅርበት ለሚገኙ የጸጥታ ኃይሎች ማሳወቅ የህልውና ትግሉ አካል ነው።

3) በተመሳሳይ አሸባሪው ትህነግ በተለያዩ ስራ የተሰማሩ ለፍቶ አዳሪ ወገኖቻችን ጋር በመመሳሰልም ሰርጎ ገቦችን ሊጠቀም ይችላል። ለምሳሌ ያህል ሊስትሮ፣ ደረቅ መግቦችን አዟሪ፣ ልዋጭ፣ ሎተሪ አዟሪ፣… ወዘተ መስሎ የሚንቀሳቀስባቸው አጋጣሚዎች ተፈጥረዋል። ይህ በሕዝባችን ጥቆማ፣ በጸጥታ ኃይላችን ክትትል የደረስንበት እውነታ ነው። በተለይ በእነዚህ ስራዎች የተሰማሩ ለፍቶ አደሪዎች ጋር በመተባበር የትህነግ ሰርጎ ገብ መከላከል የሕዝባችን ድርብ ኃላፊነት መሆኑን ለመጠቆም እንወዳለን።

4) የአሸባሪውና ወራሪው ትህነግ ሰርጎ ገብ ኃይል በክልላችን ውስጥ ለመግባት ከሚጠቀምባቸው ስልቶች አንዱ ወደ ሕክምና ወይንም ወደ ዘመድ ጥየቃ የሚሄድ መስሎ ሰርጎ ለመግባት ይሞክራል። በሌላ በኩል አካላቸውን አቁስለው፣ ወይንም የቆሰሉ አስመስለው፣ ያልቆሰለ አካላቸውን ጠምጥመው ታማሚ፣ የአእምሮ ህመምተኛ መስለው ለማለፍ ይሞክራሉ። በየትኛውም የክልላችን አካባቢዎች መሰል እንቅስቃሴዎችን የሚያደርጉ ጸጉረ ልውጦች ከታዩ ሕዝባችን ለሚመለከተው የጸጥታ ኃይል ጥቆማ እንዲሰጥ ጥሪ እናስተላልፋለን።

5) ለሰራዊቱ የስንቅ ዝግጅት ሲደረግ አጋዥ መስለው ለመሳተፍ ይጥራሉ። የስንቅ ዝግጅቱ በከፍተኛ ጥንቃቄ የሚካሄድ ቢሆንም በየማዕከላቱ ሕዝባችን የወትሮ ጥንቃቄ እንዳይለየው ማሳሰብ እንወዳለን።

6) በተለያዩ አውደ ውጊያዎች የአማራ ልዩ ኃይል፣ የመከላከያ ሰራዊት እንዲሁም ፋኖ መስሎ ሕዝብ እንዲሸሽ ተስፋ እያስቆረጠ ለአሸባሪውና ወራሪው ትህነግ ኃይል ቦታ ሲያስከፍቱ የተገኙ አሉ። አሁንም በግንባር አካባቢ ባሉ ቦታዎች መሰል እንቅስቃሴዎች ሊኖሩ ስለሚችሉ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል።

7) የጠላት አንደኛው መታገያ ስልት “ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው” የሚሉት የምላስ ትግል ሁኖ በመታየት ላይ ነው። የወገን ጦር መስሎ፣ የሕዝባችን አካል መስሎ፣ …በጸጥታ ኃይሉ መካከል የእርስ በርስ ጥርጣሬ በማሰራጨት የወገን ጦርን በወሬ ለመፍታት ሲባዝን ተስተውሏል። በየጊዜው በሚነዛው የሐሰት ዜና ሕዝብ ነቅሎ እንዲወጣ ሲያሴሩ፣ የተዛባ መረጃ ሲያሰራጩ የተያዙ ሰርጎ ገቦች አሉ። በተመሳሳይ የሐሰት ወሬ በማውራት ሕዝብን የሚያሸብሩ ሰርጎ ገቦችና ባንዳዎች ስላሉ መሰል እንቅስቃሴዎች ሲታዩ ሕዝባችን ለፀጥታ ኃይላችን በመጠቆም አጀንዳቸውን እንዲያከሽፍ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

ማሳሰቢያ‼️

ጥንቃቄዎቹ የሚደረጉት ትህነግ በአካልም በሥነ ልቦናም ላይ የሚፈፅማቸውን የሽብር ድርጊቶች ለማስቆም በመሆኑ ሰርጎ ገብን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት የራስን ወገን ከልክ በላይ በመጠራጥር፣ ራስን ለሽብር ማጋለጥ ተገቢ አይደለም። ጠላትን መንጥሮ ማውጣት ግን የዘወትር ግዴታችን ሊሆን ይገባል።

አካባቢያችንን ነቅተን በመጠበቅ የሕልውና ትግሉ አካል እንሁን‼️

ክተት መክት ለፍትሕ ለነጻነት‼️

ነሐሴ 09/2013 ዓ.ም

Exit mobile version