Site icon ETHIO12.COM

ስለ ቅጥረኛውና ወራሪው ትህነግ ልንገነዘባቸው የሚገቡ ቁልፍ ነጥቦች!

አባቶቻችን በርካታ ወረራዎችን በመስዋዕትነት መክተው ሀገር አስቀጥለዋል። በአንድነት ዘምተው የሀገር አንድነትን አስቀጥለዋል። ከእነ ብዙ ውጣ ውረዱ ትውልድ አንገቱን ቀና አድርጎ እንዲሄድ አድርገዋል።

በአባቶቻችን ታሪክ እየኮራን፣ ያሸነፉበትን ዕለት እየዘከርን የኖርነው የዛሬው ትውልድ አባላት ሌላ ወራሪ ገጥሞናል። ይህን ወራሪ ኃይል ታዲያ አቃልሎ ፣ እንደ አንድ ሀገራዊ ኃይል አድርጎ የመመልከት የተሳሳቱ አዝማሚያዎች ይስተዋላሉ። ከዚህ አንፃር ቅጥረኛው ወራሪና አሸባሪ የትህነግ ኃይል ልንገነዘብባቸው የሚገቡ ቁልፍ ጉዳዮች አሉ።

1) ቅጥረኛው ወራሪና አሸባሪው ትህነግ እንደ አንድ የሀገር ውስጥ ኃይል ታይቶ መመዘኑ አግባብነት የሌለውና ሊታረም የሚገባ ጉዳይ ነው። ትህነግ በየትኛውም ቅድመ ሁኔታ ተስማምቶ ለውጭ ጠላቶቻችን ቅጥረኝነት ያደረ ኃይል ነው። 6 ቀን በፈጀ ውይይት ከተለያዩ አካባቢዎች ተጠራርተው በቴሌ ኮንፈረንስ ውሳኔ ያሳለፉ የቅጥረኛው ትህነግ ተወካዮች በውሳኔያቸው ኢትዮጵያውያን በራሳቸው ገንዘብ የገነቡትን የሕዳሴ ግድብ ማስተጓጎልና ማፍረስን ጨምሮ በየትኛውም የኢትዮጵያ ጥቅም ላይ ለመደራደር አይኑን እንደማያሽ በግልፅ አስፍረዋል። ትህነግ ለሚፈፅማቸው በደሎች ይህ ነው የሚባል ትኩረት የማይሰጡት ምዕራባዊያኑ፣ ይህ ቅጥረኛ ኃይል በሀሰት የሚያቀርባቸውን መረጃዎች እውነት አስመስለው ኢትዮጵያን የሚከሷትም በዚሁ የቅጥር ስምምነታቸው መሰረት ነው።

በሕዳሴው ግድብ ጉዳይ ሲዝቱ የኖሩ ኃይሎችን ጨምሮ ኢትዮጵያ አንገቷን ቀና እንድታደርግ የማይፈልጉ የውጭ ጠላቶች ትህነግን በማገዝ የሚረባረቡት ቅጥረኛውና ወራሪው ኃይል ጥቅማቸውን የሚያስጠብቅላቸው ሁነኛ ተላላኪ ስለሆነ ነው። በመሆኑንም ትህነግ የበርካታ ፀረ
ኢትዮጵያ የውጭ ኃይሎችን ተደራራቢ አላማ አንግቦ በኢትዮጵያ ጥቅም ላይ የተነሳ ቅጥረኛ ኃይል እንጅ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ቡድን ታይቶ ከሕግ፣ ከድርድር ወዘተ አንፃር ሊወራለት የሚገባ እንዳልሆነ መታወቅ አለበት።

2) ቅጥረኛውና ወራሪው አሸባሪ ኃይል ጥላቻውን መቆጣጠር ተስኖት የላኪዎቹን ያህል እንኳን ክፋቱን ለመደበቅ አልቻለም። በሕዳሴው ግድብ ጉዳይ ተላላኪ ያደረጉትና ከግድቡ አንፃር ጥቅም ያላቸው ሀገራት በዓለም አቀፍ መድረክ ለሽፋንም የኢትዮጵያን ልማት እንደሚደግፉ ሲያስመስሉ፣ ቅጥረኛው ኃይል ግን በውሳኔው ግድቡን ስለማስተጓጎልና ስለማጥቃት ደረቱን ነፍቶ አላማዬ ነው ብሎ
ይነግረናል። ምዕራባዊያኑ ለይምሰልም በኢትዮጵያ አንድነት አንደራደርም ሲሉ፣ በተቃራኒው ቅጥረኛቸው ትህነግ ኢትዮጵያን እንደሚበትን በየቀኑ ሲነግረን የሚውል ኃይል ነው። ከንቀት የመነጨ ቢሆንም ፋሽስት ጣሊያን እንኳን “አሰለጥናቸዋለሁ” የሚል ቅስቀሳውን ይዞ ነበር የመጣው። በአንፃሩ ትህነግ “ሂሳብ አወራርዳለሁ” እያለ በይፋ እየቀሰቀሰ ይገኛል። እስካሁን ካጋጠሙን ወራሪዎችም ሆነ ከትህነግ ቀጣሪዎች በተለየ መልኩ ትህነግ ሳይደባብቅ ኢትዮጵያን ሊያጠፋ እንደወረረን እየነገረን ይገኛል። ፋሽስት ጣሊያን እኛን ያልሰለጠንን አድርጎ አሰለጥናቸዋለሁ ብሎ መጥቶ በመርዝ ጋዝ ጨፍጭፎናል። የሕዳሴውን ግድብ እንዳይሳካ የሚፈልጉ አካላት ለይምሰል የኢትዮጵያን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት እንደሚደግፉ እየተናገሩ ግድቡ እንዳይሳካ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም። ከዚህ አንፃርሲታይ የጥፋት አላማውን ለመደበቅ ያልቻለው ትህነግ ወረራ ከቀደሙት ወረራዎችም በከፋ ምን ያህል አውዳሚ እንደሆነ ለመገንዘብ አያዳግተንም።

3) ቅጥረኛው፣ ወራሪውና አሸባሪው ትህነግ ከጥላቻው ብዛት አላማውን በግልፅ እየተናገረ ብቻ ሳይሆን በተጨባጭም እየፈፀመው ይገኛል። የጭካኔውን፣ የክፋቱን፣ ቀጣሪዎቹ ጋር በተዋዋለው መሰረት ውድመት ለመፈፀም ያለውን ቁርጠኝነት ለማሳየት በአማራና በአፋር ክልሎች የፈፀማቸውን ዘግናኝ ወንጀሎች መመልከት በቂ ነው። አፋር ክልል ላይ በእሱ ወረራና ጭካኔ የተፈናቀሉ ንፁሃን ዜጎችን ላይ ዘግናኝ ሽብር ፈፅሞ ከ200 በላይ ሕይወት ቀጥፏል። ከእነዚህ መካከል ከ100 በላይ የሚሆኑት ህፃናት ናቸው። ምንም እንኳ ዓለም አቀፍ አሸባሪዎች የሚያደርጉትን የማጥቃት ሙከራ ሳይቀር የሳምንት ሰበር ዜና የሚያደርጉ ምዕራባዊያን ሚዲያዎች በሚገባው መጠን ባይዘግቡት ትህነግ የፈፀመው ጭካኔ በቅርብ ጊዜያት በአሸባሪዎች ተፈፅሞ ያላየነው ጭካኔ ነው። በወረራቸው የአማራ ክልል አካባቢዎች፣ የአእምሮ ህሙማንን፣ ህፃናትንና እናቶችን በዘግናኝ ሁኔታ ገድሏል። የኤርትራ ስደተኞች ላይ በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ሊያስጠይቀው የሚችል ወንጀልን ፈፅሟል። ይህ ህፃናት፣ የአእምሮ ህሙማን፣ ስደተኞችና ተፈናቃዮች ላይ የፈሪ ዱላውን የሚያሳርፍ ኃይል ገና እግሩ ከመርገጡ ይህን የመሰለ ጭካኔ ከፈፀመ ነገ እድል አግኝቶ የወረራ አላማው ቢሳካለት ሀገራችን የዘር ፍጅት ከተፈፀመባቸው ሀገራት ቀዳሚዋ ሊያደርጋት እንደሚችል ከወዲሁ እያስመሰከረ ይገኛል።

4) ወራሪው ኃይል ቅጥረኝነቱ ቀደም ሲልም የሚታወቅና ለሉአላዊነት ፈፅሞ ቀናኢነት የሌለው መሆኑን የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያውቀው ጉዳይ ነው። ወንድም ሕዝቦችን ካስፈጀ በኋላ የአልጀርሱ ስምምነት ላይ “ኢትዮጵያ አሸንፋለች” ብሎ በሀሰት ያስጨረሰ ኃይል ነው።

ሁለት ወንድማማች ሕዝቦች ያለቁበትን የሉአላዊነት ጉዳይ ለስልጣኑ ማስጠበቂያ በማድረግ፣ ሁለቱ ሀገራት በቁርሾ እንዲቆዩ አድርጓል።

በተመሳሳይ ሉአላዊ ግዛትን በግለሰቦች ፈቃድ በድብቅ ስምምነት አሳልፎ ለመስጠት ውስጥ ውስጡን ሲሠራ መኖሩንም ከለውጡ በኋላ ስለ ኢትዮ ሱዳን ድንበር በወጣው መረጃ የተረጋገጠ ጉዳይ ነው። ይህ ቅጥረኛ ኃይል፣ ሉዓላዊነትን አሳልፎ እየሰጠ፣ ሰንደቅ አላማን፣ ኢትዮጵያዊነትን እያዋረደ የኖረው ለመቶ አመታት ያህል ስልጣን ላይ እቆያለሁ ብሎ እያሰበ በነበረበት ወቅት ነበር። በሚፈፅማቸው ወንጀሎችና በተላላኪነቱ ምክንያት ሕዝብ አንቅሮ ሲተፋው በአደባባይ እየተናገረ ያለውን ጭፍን ጥላቻውን ይዟል። ስልጣን ላይ እቆያለሁ እያለም ለሉዓላዊነት፣ ለሀገር ክብርና አንድነት ምንም ደንታ ያልነበረው ኃይል አሁን ለይቶለት ሉአላዊነትን በይፋ አሳልፎ ስለመስጠት እየሠራ ነው። ወረራው ኢትዮጵያን በትኖ፣ ሉዓላዊነቷን አሳልፎ ለመስጠት ነው። ለዚህም ማሳያ እሱም በበኩሉ ጭካኔ የሚፈፅሙት ጋር
ሌላ የቅጥረኝነት ውል ተዋውሏል።

ሕዝብን በማፈናቀል ከወገኑ ጋር ሲነጥል የኖረው ኦነግ ሸኔ ጋር ስምምነት ፈጥሬያለሁ ብሏል። ንጹሐንን አስከሬናቸውን ቆራርጦ በአንድ ጉድጓድ በዶዘር እንዲቀበሩ ሲያደርግ የከረመው ታጣቂ ቡድን ጋር ሆኖ በቤንሻንጉል በኩል ጥቃት ከፍቷል። በተመሳሳይ የንፁህ ገበሬ ምላስ እየቆረጠ፣ ተሳፋሪና አሽከርካሪዎችን አግቶ ገንዘብ የሚቀበል፣ ገንዘብ ከሌላቸው በጭካኔ የሚያርደው በቅማንት ሕዝብ ስም የሚነግድ አሸባሪ ጋር የተላላኪነት ውል ፈፅሞ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል። የኢትዮጵያ ጠላቶች
የቀጠሩት አሸባሪው ትህነግና፣ ትህነግ የቀጠራቸው ሌሎች ጨካኝ ቡድኖች በሕዝብና በሀገር ላይ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ ለመረዳት ባለፉት ሦስት አመታት የተፈፀሙትን አሰቃቂ ሰብአዊ ግፎች ማስታወስ በቂ ነው።

5) ቅጥረኛው ትህነግ በማንፌስቶ ጠላት ብሎ የፈረጀውን የአማራ ሕዝብ፣ እንዲሁም በስልጣኔ መጡብኝ ያላቸውን ኢትዮጵያውያን ዘር እንዳይተኩ አኮላሽቷቸዋል። በጨለማ እስር ቤቶች በማጎር፣ ሴቶችን በመድፈር የኢትዮጵያን ሕዝብ ያስደነገጠ ወንጀል የፈፀመ ቡድን ነው። ይህን ሁሉ ወንጀል የፈፀመው ጥላቻውን በአደባባይ ሳይናገር ነበር። በዚህ ወቅት ጥላቻውን በአደባባይ እየተናገረ፣ ሀገር ለማፍረስና የኢትዮጵያን ጥቅሞች አሳልፎ ለመስጠት ወረራ መጀመሩን እየተናገረ ነው። ጥላቻውን የዛሬውን ያህል ሳይነግረን ስልጣን ላይ እያለ ኢትዮጵያውያን ለመስማት የቀፈፋቸውን ጭካኔ የፈፀመ ቅጥረኛና አሸባሪ ኃይል የአማራን ሕዝብ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አንገት አስደፋለሁ፣ ኢትዮጵያን አፈርሳለሁ፣ ኢትዮጵያውያንን እርስ በእርስ አፋጃቸዋለሁ ብሎ አቅዶ በፈፀመው ወረራ ቢሳካለት የህዝባችንና የሀገራችንን ሕልውና በእጅጉ የሚፈታተን የቅጥረኝነት ተግባሩን እንደሚፈፅም ከወዲሁ መታወቅ ይገባዋል።

በመሆኑም:-
ክልሎችን እንዲሁም ጎረቤት ሀገርን መውረርን እንደ ጀብዱ፣ ንፁሃንን መጨፍጨፍን እንደ ጀግንነት፣ ከአጥፊዎች ጋር መቀናጀትን እንደ ታታሪነት፣ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን ሕልውና መፈታተንን እንደ አላማ አድርጎ የተነሳውን ቅጥረኛ፣ ወራሪና አሸባሪ ኃይል ዋና ዋና ባሕሪያት፣ ዓላማና አካሄዶች በመገንዘብ በየፊናችን የሚቻለውን ሁሉ አድርገን ወረራውን በማስቆም የራሳችን፣ የሕዝባችንና የሀገራችን ሕልውና ማስጠበቅ ይገባናል። ለማሳመኛነት መልካም መልካሙን እየተናገሩ ብዙ በደል የፈፀሙብንን ወራሪዎች አሳፍረን መልሰናል።

ከቀጣሪዎቹ በባሰ በጥላቻ አብዶ፣ የጥፋት እቅዱን ሳይደብቅ እየነገረን ወረራ እየፈፀመብን ያለውን ኃይል ከእስከዛሬውም በተሻለ ወኔ፣ አንድነትና መስዋዕትነትም መክተን ድል ልናደርገው ይገባል። የተላላኪውን ትህነግ ወረራ ለመመከት በምናደርገው የትኛውም ተሳትፎ ቀደም ሲል የተጠቀሱትን ባሕሪያት ተረድተን፣ ለሌሎቹም እያስረዳን፣ ጥፋቱንም እያሰብን መሆን ይገባል። Via – Amhara media corporation

Exit mobile version