Site icon ETHIO12.COM

በእነ ቢቢሲ የሚመራው የአሸባሪው ህወሓት የሳይበር ሠራዊት ድብቅ ሴራ!

ከቅርብ ወራት ወዲህ በምስራቅ አፍሪካ እየሆነ ስላለው ነገር ብዙም ካልተሰወረው ወሳኝ እውነት መጀመር ያስፈልጋል። ከ20 ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ የመንግስት ስርዓት ውስጥ ከፍተኛ ተጽዕኖ የነበረው አሸባሪው ህወሃት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በበርካታ የዓለም ዓቀፍ ተቋማት ውስጥ ሰርገው መግባታቸውን በቅርቡ የምናያቸው ነገሮች ፍንትው አድርገው ያሳዩናል።

የክብር ስምና ዝና ያላቸው እንደ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ወይም ሂዩማን ራይትስ ዎች ያሉት መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ እንደ ቢቢሲ፣ ዘ ጋርዲያን፣ ሲኤንኤን ያሉ መገናኛ ብዙሃን እንዲሁም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት (ተመድ) ኤጀንሲዎች ጭምር የአሸባሪው ህወሃት የሳይበር ሰራዊት በመሆን ስልታዊ በሆነ መንገድ የአሸባሪውን ቡድን የተሳሳተ መረጃ ስርጭት እያሳለጡ ይገኛሉ። በርግጥ በሁሉም ደረጃ እየተካሄደ ያለው የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ የቀጠናውን ሰላም ለመመለስ የሚደረገውን ጥረት እያደናቀፈ እንደሚገኝ መገንዘብ ይቻላል።

ለምሳሌ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የተሳሳተ መረጃ ስርጭት ውስጥ የገቡት ተቋማት ሰራተኞች በአብዛኛው የአሸባሪው ህወሃት ታማኞች ሆነው እናገኛቸዋለን። በመሆኑም እጃቸው ላይ ባለው ማንኛውም የፕሮፓጋንዳ መሳሪያ ተጠቅመው የቡድኑን ተልዕኮ ለመፈጸም ወደ ኋላ አይሉም። የሳይበር ጦርነታቸውን ለማካሄድ ዋና መሳሪያ አድርገው ይጠቀሙበታል። ይህ ሁኔታ ደግሞ የአሸባሪውን ቡድን ብቻ የሚደግፍ ሚዛናዊነት የሌለው ዘመቻ ለማካሄድ እየጠቀማቸው ነው።

በተቋማቱ ውስጥ ያሉ የቡድኑ ደጋፊዎች ሪፖርት ሲያዘጋጁም ቡድኑን ሊጠቅሙ በሚችሉ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ያደርጋሉ። ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የአሸባሪው ህወሃት ወዳጆችና የጥቅም ተጋሪዎች ኤርትራውያን ስደተኞች መሆናቸውን የሚገልጽ የሐሰት ሰነድ ተዘጋጅቶላቸው በአውሮፓና አሜሪካ ጥገኝነት እንዲሰጣቸው ተደርጓል። እነዚህ በሐሰተኛ የሰነድ ማስረጃ ባህር የተሻገሩ የቡድኑ አባላት፣ ወዳጆችና ጥቅም ተጋሪዎች በጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ እየተመራ በሚገኘው የኢትዮጵያ መንግስት ላይ የተቀናጀና የተደራጀ የሐሰት ፕሮፓጋንዳ እያካሄዱ እንደሚገኙ ለአብነት መጥቀስ ይቻላል።

የዚህ ቡድን የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ዋና ዓላማ የኢትዮጵያን ሰላም መንሳትና አሸባሪው ቡድን እንደሚለው ‘ታላቋን ትግራይ’ ለማዋለድ ያለመ ነው። አሸባሪው ህወሃት መንበረ ስልጣን ላይ በነበረበት ጊዜና አሁንም በሚገኝበት የአሸባሪነት ቁመናው ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ መልካም የማይመኝ የህዝብ ጠላት መሆኑ በኢትዮጵያውያን ዘንድ በመታወቁ ቡድኑ በህዝብ ዘንድ የተተፋ ነው። አሁን የሚያደርገው መፍጨርጨርም የይስሙላ የፖለቲካ ግንባር በመፍጠር ወደ ስልጣን ተመልሶ የለመደውን የብዝበዛና የጭቆና ተግባሩን በብቸኝነት ለመፈጸም አልሞ እንደሆነም ግልጽ ነው።

ቡድኑ እራሱ በለኮሰው የጦርነት እሳት ‘ጩኸቴን ቀሙኝ’ እንዲሉ በዘመነ ስልጣኑ ባፈራቸው ወዳጆቹ፣ ድርጅቶችና መገናኛ ብዙሃን አማካኝነት የትግራይ ተወላጆች የዘር ጭፍጨፋ እየተፈጸመባቸው እንደሆነ በመግለጽ የሐሰት ነጋሪት እያስጎሰመና እየጎሰመ ይገኛል። ለአብነትም በአሸባሪው ህወሓት ታጣቂዎች አማካኝነት የተፈጸሙ ጭፍጨፋዎችን በኢትዮጵያና በኤርትራ መከላከያ ሰራዊት አማካኝነት የተፈጸመ ድርጊት አድርጎ ለማቅረብ ሲሞከር ይታያል።

በአሁኑ ወቅት ደግሞ በጦር ግንባር የሚያልቁትን የቡድኑን ታጣቂዎች አስከሬን በመሰብሰብ ቡድኑ በሚቆጣጠራቸው ቦታዎች በተዘጋጁ ስፍራዎች በመቅበር በኢትዮጵያና ኤርትራ መከላከያ ሰራዊት አማካኝነት የጅምላ ጭፍጨፋ የተፈጸመበት ስለመሆኑ ለመጮህ የሚያስችለውን ዝግጅት እያደረገ እንደሆነ ይታወቃል። ገለልተኛ የሆኑ እማኞች በሚሰጡት ምስክርነት ቡድኑ በትግራይ ክልልና በሱዳን መጠለያ ጣቢያ የጅምላ ጭፍጨፋ ተፈጸመብኝ በማለት የሚያነባው የአዞ እምባ ምንጩ ያዘጋጀው የሐሰት መረጃ እንደሆነ ይገልጻሉ። ለሁመራ ጭፍጨፋ ትርኢቱ ያዘጋጀው የሐሰት ትርክት የዚህ አንዱ ማሳያ ነው።

ለዚህ ጉዳይ ሚዲያዎቹና ተቋማቱ ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ሲያሰሙ ቆይተዋል። በተመሳሳይ ሁኔታ አሸባሪው ህወሃት በአፋርና በአማራ ክልል ለፈጸመው ግፍ ድምጽ አጥተዋል። ቡድኑ የፈጸመው ጥቃት የዜጎችን ህይወት ከመቅጠፍ ባለፈ ህጻናትና እናቶችን ጨምሮ በርካቶችን ለችግር ዳርጓል። የቡድኑ ደጋፊዎች ይህንን ሰቆቃ ማየት አልቻሉም።በዚህ ረገድ ዓለም ዓቀፍ ተቋማት የህወሃትን ግፍ ለመደበቅ ባደረጉት ጥረት በሚዛናዊነት ረገድ መውደቃቸውን ማየት ይቻላል።

የዚህ ሁሉ የሚዛናዊነት መዛባት መንስዔ ቡድኑ የማዕከላዊ መንግስትን በተቆጣጠረበት ዘመን ለሽብር ዓላማው መሳካት ገንዘብ በመክፈል ቀርጾ ያዘጋጃቸው መገናኛ ብዙሃንና ዓለም ዓቀፍ ተቋማት ናቸው። ከማዕከላዊ መንግስት በህዝባዊ ተቃውሞ ተገፍቶ የተወገደው አሸባሪ ቡድን አሁን በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በኢትዮጵጵያ ውስጥ የሽብር ድርጊቶችን ለመፈጸም የመሪነት ሚና ይጫወታል። ቡድኑ ኢትዮጵያን ለማጥፋትና በምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አለመረጋጋት እንዲፈጠር የተያዘውን ዕቅድ አንዳንድ ምዕራባውያን በግልጽና በስውር ሲደግፉ ይስተዋላል።

በተለይም ደግሞ ቡድኑ በተለያየ መንገድ ወደ አውሮፓና አሜሪካ ያስገባቸው ሃይሎች ይህንን ዕቅዱን ለማሳካት እየሰሩ እንደሚገኙ የአደባባይ ምስጢር ነው። ከዓለም የጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ጀምሮ በአውሮፓ ህብረትና በአሜሪካ የሚገኙ አንዳንድ ሹማምንቶች፣ ግለሰቦች፣ የተወሰኑ የምዕራባውያን አገሮች አምባሳደሮች፣ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሰራተኞች ወዘተ ለህወሃት የሽብር ዓላማና ዕቅድ መሳካት በስውርም ሆነ በግልጽ እየሰሩ መሆናቸውን መታዘብ ይቻላል። ይህ እርግጥ ስለመሆኑ ማንም ፍላጎቱ ያለው አካል ጥናት ሊያደርግ ይችላል።

ብዙዎቹ ከአሸባሪው ህወሃት ጋር ግንኙነት ያላቸው የዓለም ዓቀፍ ተቋማት በግልጽ ተለይተው ይታወቃሉ። ነገር ግን በተቃራኒው የሐሰት ፕሮፓጋንዳ በመክፈት ሰላም በማምጣት ረገድ ትልቅ ስራ በመስራት የሚታወቁትንና የኢትዮጵያውያንን የረጅም ግዜ ምኞትና ፍላጎት ለማሳካት በታላቅ የለውጥ ስሜት እየሰሩ ያሉትን፣ በቅርቡም በተደረገው አገራዊ ምርጫ ኢትዮጵያዊያን ዓለም አቀፉን ሴራ ተረድተው ኢትዮጵያን በመምረጥ ሽረባው ረብ የሌለው መሆኑን አሳይተዋል። ተከፋዮቹና የሴራው ተዋናዮች ግን አሁንም ለአጠቃላይ አገራዊ ብልፅግና ተስፋ የሰነቁትን የሰላም ኖቤል ተሸላሚ ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድን በተለያየ መልኩ ለመክሰስ ጥረት ሲያደርጉ ይታያል።

ሆኖም እውነታው ተቃራኒው ነው። የህወሃት አሸባሪ ቡድን እጅግ ወደ ከፋውና ዘግናኝ ወደሆነው አረመኔያዊ ጥፋት እስኪሸጋገር ድረስ ቡድኑ ወደ ሰላማዊ መስመር እንዲመጣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ በኩል ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል። እንዲያውም ህዝቡና ተፎካካሪ ፓርቲዎች እሳቸውን ሲወቅሱ የነበረው፣ የጥፋት ቡድኑ ለምን ዝም ተባለ በሚል ነበር። በአገሪቱ የተፈፀሙ ከ113 በላይ ግጭቶችን በቀጥታና በተዘዋዋሪ በመምራት ግፍ የፈፀመው ህወሓት በእርግጥም ህዝቡ በጥሞናና በአፅንኦት ሲከታተለው የነበረ በመሆኑ ዛሬ የህዝብ ጠላት ሊሆን ችሏል።ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኢትዮጵያን አንድነት በማጠናከር ለአሸባሪው ህወሃት ትንኮሳ ቦታ ባለመስጠትና ሰላማዊ አማራጭን በመከተል ቡድኑ በየቦታው የሚፈጥራቸውን ቀውሶች በመቋቋም ለውጥ አምጥተዋል።

ከኢትዮጵያ አልፎ በቀጣናው ብልጽግናን ማምጣት የሚያስችል ቀጣናዊ ትስስር ለመፍጠር ሞክረዋል። ይህንንም ከኤርትራና ከሶማሊያ ጋር የተደረሰው ስምምነት በአብነት ይጠቀሳል። አሸባሪው ቡድን በኖረበት የሐሰት ፕሮፓጋንዳ ቢቀጥልም አብዛኛው ኢትዮጵያዊ በውል ስለተገነዘበው ሽንፈቱን እየተከናነበ መጥቷል። መፃኢ እድሉም በስሙ እየነገደበት ካለው የትግራይ ክልል ህዝብ፣ በራሱ ክልሉ ህዝብ ትግል ጭምር እየተነጠለና እየጠፋ መክሰም ስለመሆኑ መላው ኢትዮጵያውያንና ትግራይ ላይ የሚሰሩ የተጋሩ ንቅናቄና የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ጥምረት ሁነኛ ማሳያ ነው።

ኢፕድ

Exit mobile version